Tuesday, April 7, 2026

❖ሕማማት፦

ሕማማተ ክርስቶስ፡ በጌታችን ኢየሱስ ላይ የተሸረበው ሴራ።
በአራቱ ወንጌላውያን ሐተታ።
*** ማቴዎስ 26:1-5***
" ኢየሱስም እነዚህን ቃላት ሁሉ ጨርሶ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ አለ፦ "ከሁለት ቀን በኋላ ፋሲካ እንደሚሆን ታውቃላችሁ፥ የሰው ልጅም ሊሰቀል አልፎ ይሰጣል።" በዚያን ጊዜ የካህናት አለቆች የሕዝብ ሽማግሌዎችም ቀያፋ በሚባለው በሊቀ ካህናቱ ግቢ ተሰበሰቡ፤ ኢየሱስንም በተንኰል ይዘው ሊገድሉት ተማከሩ፤ ነገር ግን በሕዝቡ ዘንድ ሁከት እንዳይነሣ "በበዓል አይሁን" አሉ።
ቅዱስ ማቴዎስ የሕማማቱን ታሪክ የሚጀምረው ጌታችን ኢየሱስ ሊፈጸሙ ባሉት ክስተቶች ላይ ሙሉ ቁጥጥር እንዳለው በማጉላት ነው። ጌታችን ኢየሱስ ስለሚመጣው መያዙና መሰቀሉ ለደቀ መዛሙርቱ መመሪያ ይሰጣቸዋል። ይህ ስለ ሕማማቱ ከተናገራቸው አራት ተከታታይ ትንቢቶች (ማቴ= 16:21፤ 17:22-23፤ 20:18-19) የመጨረሻው ሲሆን፣ ይህም ሕማማቱ የኢየሱስ ሕይወትና ተልዕኮ ዋና አካል መሆኑን ያሳያል።
"ኢየሱስም እነዚህን ቃላት ሁሉ ጨርሶ" የሚለው የመክፈቻ ሐረግ፣ ማቴዎስ በወንጌሉ ውስጥ ዋና ዋና ሽግግሮችን ለመለየት የሚጠቀምበት ነው። ይህም የወንጌሉ ዋና መዋቅር የሆኑትን አምስቱን ታላላቅ ንግግሮች ማጠቃለያ ያመለክታል ( ማቴ=7:28፤ 11:1፤ 13:53፤ 19:1 እንመልከት)።
ቅዱስ ማቴዎስ እዚህ ጋር "ሁሉ" የሚለውን ቃል የጨመረው፣ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን የማስተማር አገልግሎቱን አሁን ማጠናቀቁን ለማመልከት ነው። የኢየሱስ የመጨረሻ ንግግር ስለ ብሉይ ኪዳን ዘመን ፍጻሜ የተናገረው የምጽአት ትምህርት (ማቴ 24-25) ነበር።
ይህ ሽግግር የጌታችን የኢየሱስን የትምህርት አገልግሎት ከሕማማቱ ጋር ያገናኘዋል፤ እንዲሁም በምጽአት ( በ70 ዓ/ም በኢየሩሳሌም ላይ ለፍርድ የሚመጣበት ወቅት) ትምህርቱ ላይ የተገለጸውን የከበረውን የሰው ልጅ፣ ሕማማትን ሊቀበል ካለው መከራ የሰው ልጅ ጋር ጎን ለጎን ያነጻጽረዋል።
ቅዱስ ማቴዎስ በፋሲካ በዓልና በኢየሱስ ሞት መካከል ያለውን ግንኙነት በግልጽ ያሳያል። ይህንን ንጽጽር በጌታችን ኢየሱስ ትንቢት ውስጥ በማስቀመጥ፣ ወንጌላዊው ግንኙነቱ በአጋጣሚ ሳይሆን የእግዚአብሔር ዕቅድ አካል መሆኑን ያሳያል። የኢየሱስ ሞትና በመጨረሻው እራት የሚታሰበው መታሰቢያው፣ ለአዲሱ የእግዚአብሔር ሕዝብ እውነተኛው የፋሲካ መሥዋዕት ነው።
የዚህ ድርብ ትዕይንት ሁለተኛ አጋማሽ የጌታችን ኢየሱስን ግልጽ እውቀትና ዝግጁነት፣ ከሴራ አጋዥዎቹ ምስጢራዊነትና ተንኰል ጋር ያነጻጽረዋል። የአይሁድ መሪዎች በጌታችን ኢየሱስ ሕፃንነት ጊዜ ሕይወቱን ለማጥፋት በሄሮድስ ዙሪያ እንደተሰበሰቡ ሁሉ (ማቴ=2:4)፣ አሁንም ጌታችን ኢየሱስን ለመግደል ከሊቀ ካህናቱ ጋር ይማከራሉ። የሊቀ ካህናቱን ስም ቀያፋ ብሎ የጠቀሰው ማቴዎስ ብቻ ነው። ምንም እንኳ መሪዎቹ ብዙ የመንፈሳዊ ተጓዦች ሁከት ሊያስነሱ ይችላሉ በሚል ፍርሃት በፋሲካ በዓል ወቅት ላለማሰር ቢወስኑም፣ የኢየሱስ ትንቢታዊ ቃል ግን ጊዜው የማይቀር መሆኑን አረጋግጧል።
*** ማርቆስ 14:1-2***
በጌታችን ኢየሱስ ላይ የተሸረበው ሴራ፡ በቅዱስ ማርቆስ ወንጌል ሐተታ።
ከሁለት ቀን በኋላ ፋሲካና የቅዱስ በዓል ነበረ። የካህናት አለቆችና ጻፎችም እንዴት አድርገው በተንኰል እንደሚይዙትና እንደሚገድሉት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን የሕዝብ ሁከት እንዳይሆን "በበዓል አይሁን" ይሉ ነበር።
ቅዱስ ማርቆስ የሕማማቱን ታሪክ የሚጀምረው እነዚህን የመጨረሻ ክስተቶች ከአይሁድ የፋሲካ በዓል አውድ ጋር በማያያዝ ነው። በየዓመቱ ፋሲካ የሚከበረው እስራኤላውያን ከባርነት ወደ ነፃነት የወጡበትን ቤዛነት ለማስታወስ ነበር። እንደ ሁሉም የአይሁድ በዓላት፣ ፋሲካም የሚጀምረው ፀሐይ ስትጠልቅ ነበር። በዓሉ ከመጀመሩ በፊት ባለው ከሰዓት በኋላ፣ የፋሲካው በግ በቤተ መቅደስ ውስጥ ይሰዋል።
በዚያ ምሽት በሚደረገው የፋሲካ እራት፣ የዘፀአት (ከግብፅ መውጣት) ክስተቶች ይተረካሉ፣ ይታሰባሉም። ከግብፅ በችኮላ መውጣታቸውንና በበረሃ የተቀበሉትን መከራ ለማስታወስ፣ ለእራቱና ከዚያ በኋላ ላሉት ሰባት ቀናት የሚበላው እርሾ የሌለበት እንጀራ (ቅዱስ) ብቻ ነበር።
ፋሲካ ከሐሙስ ፀሐይ መግቢያ እስከ ዓርብ ፀሐይ መግቢያ ድረስ የሚከበር በመሆኑ፣ በማርቆስ የዘመን አቆጣጠር መሠረት በጌታችን ኢየሱስ ላይ የታሰበው ሴራ የጀመረው ረቡዕ ዕለት ነው።
ማርቆስ በወንጌሉ ውስጥ የካህናት አለቆችንና ጻፎችን ደጋግሞ ይጠቅሳል። ጻፎች በዚያ ዘመን የነበሩ የሕግ ባለሙያዎችና የሃይማኖት ሊቃውንት ነበሩ። ኢየሱስ ከእነርሱ ጋር የነበረው ግጭት ከወንጌሉ መጀመሪያ (ማር= 1:22) ጀምሮ እያደገ መጥቶ በሕማማቱ ወቅት ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል። የካህናት አለቆች ደግሞ በኢየሩሳሌም ለነበሩት ሊቃነ ካህናት እንደ አማካሪ ያገለግሉ ነበር። ኢየሱስ ስለ ሕማማቱ በተናገራቸው ትንቢቶች ውስጥ እነርሱን መጥቀስ ጀምሮ ነበር (ማር=8:31)።
በወንጌሉ ሁለተኛ አጋማሽ ላይ፣ ጌታችን ኢየሱስ የሃይማኖት መሪዎቹ ለሞት አሳልፈው እንደሚሰጡት ዘወትር ይተነብይ ነበር። የአይሁድ ሃይማኖት መሪዎቹ ጌታችን ኢየሱስ በሕዝቡ ላይ ያለውን ተጽዕኖ በመፍራት በበዓሉ ወቅት ላለማሰር ወስነው ነበር። ሆኖም፣ ሁኔታው በእነርሱ ቁጥጥር ሥር አልነበረም፤ ጌታችን ኢየሱስም በትክክል እስራኤል የነፃነት በዓሏን በሚያከብሩበት ዕለት ይሞታል።
*** ሉቃስ 22:1-6***
በጌታችን ኢየሱስ ላይ የተሸረበው ሴራ
ፋሲካ የሚባለው የቅዱስ በዓልም ቀረበ። የካህናት አለቆችና ጻፎችም ሕዝቡን ይፈሩ ነበርና እንዴት አድርገው እንዲገድሉት ይፈልጉ ነበር። ከአሥራ ሁለቱም ቍጥር አንዱ በነበረው የአስቆሮቱ በሚባለው በይሁዳ ሰይጣን ገባበት፤ ሄዶም እንዴት አድርጎ አሳልፎ እንዲሰጣቸው ከካህናት አለቆችና ከሰራዊት አለቆች ጋር ተነጋገረ። እነርሱም ደስ አላቸው፥ ብርም ሊሰጡት ተስማሙ። እሺም አለ፥ ሕዝብ በሌለበት አሳልፎ የሚሰጥበትን አመቺ ጊዜ ይፈልግ ነበር።
እንደሌሎቹ ወንጌላውያን ሁሉ፣ ቅዱስ ሉቃስም የሕማማቱን ታሪክ መቼት በፋሲካ በዓል ወቅት ያደርገዋል። በመጀመሪያ ለየቅል የነበሩት የፋሲካ እና የቅዱስ (እርሾ የሌለበት እንጀራ) በዓላት አሁን እንደ አንድ በዓል ይከበራሉ። ቅዱስ ሉቃስ የጌታችን ኢየሱስን ሕማማት እንደ አዲስ የነፃነት (የቤዛነት) ክስተት እንዲረዱት አንባቢዎቹን አዘጋጅቷቸዋል። በደብረ ታቦር (በተራራው ላይ) ጌታችን፡ ኢየሱስ በተለወጠ ጊዜ፣ ሙሴና ኤልያስ ኢየሱስ በኢየሩሳሌም ሊፈጽመው ስላለው "መውጣቱ" (ዘጸአት) ተነጋግረው ነበር (ሉቃ=9:30)።
ቅዱስ ሉቃስ ጌታችን ኢየሱስን ለማጥፋት በተሸረበው ሴራ ውስጥ አዲስ ተዋናይን ያስተዋውቃል። ከካህናት አለቆች፣ ከጻፎችና ከይሁዳ በተጨማሪ ስለ ሰይጣን ሚና ይናገራል። ይሁዳ በሴራው ውስጥ ያለው ተሳትፎ ሰይጣን በእርሱ ውስጥ በመግባቱ እንደሆነ ተገልጿል። ሰይጣን እዚህ ጋር የሚኖረው ሚና በምድረ በዳ በነበረው ፈተና ወቅት ተዘጋጅቶ ነበር። ዲያብሎስ በፈተናው ከወደቀ በኋላ፣ "እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ" ( ሉቃ=4:13) ተብሎ ነበር።
አሁን ሕማማቱ ሰይጣን ጌታችን ኢየሱስንና ተከታዮቹን ለማጥቃት የሚያገኘው አመቺ ጊዜ ሆኗል። የሐዋርያትን ተልዕኮ "ሰይጣን እንደ መብረቅ ከሰማይ ሲወድቅ" (ሉቃ=10:18) በማለት የገለጸው ሉቃስ፣ አሁን የሕማማቱን ታሪክ ኢየሱስ ከክፉ ኃይላት ጋር የሚያደርገው ታላቅ ፍልሚያ አድርጎ ያቀርበዋል።
ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ፡ አይሁድ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የሸረቡትን ሴራ፡ ሳይገልጽ፡ የሕማማቱን ታሪክ ከታሰረበት ቀን ከረቡዕ ይጀምራል።

No comments:

Post a Comment