Friday, June 5, 2020

❖ዘመኑን ማወቅ፦

   ዘመኑን ማወቅ፦
          (ሮሜ 13:11-14)

"ከእንቅልፍ የምትነሡበት ሰዓት አሁን እንደ ደረሰ ዘመኑን እወቁ፤ ካመንንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቦአልና። ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ። በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን፤" (ሮሜ 13:11-13)

ሰላም ለእናንተ ይሁን። ጳውሎስ በወንጌል ስለተገለጠው የእግዚአብሔር ጽድቅ በሚያወራበት በሮሜ መልዕክት ውስጥ ሰው እንዴት እንደሚጸድቅ፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ጽድቅ በተለያየ አቅጣጫ ሲገለጥ ምን እንደሚመስል ዘግቧል። በዚህ በመረጥነው ክፍልም ዘመንን ስለማወቅ ይነግረናል። እኛም በሚከተሉት ሁለት ንዑስ ርዕስ ከፍለን እንመለከታለን።

1. ዘመኑ ምንድነው?፣

ዘመንን ማወቅ ታላቅ ጥበብ ነው። ዘመንን ማወቅ ጥቅም እንደነበረው የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ይነግረናል። ለምሳሌ ዳዊት የእስራኤልና የይሁዳ ንጉሥ ከሆነ በኋላ እስራኤል የሚገባውን ያደርግ ዘንድ ዘመኑን የሚያውቁ ሁለት መቶ ከይሳኮር ልጆች አለቆች ነበሩ። (1ዜና 12:32።) 

ዛሬም በአዲስ ኪዳን ዘመንን ማወቅ የሚገባውን እናደርግ ዘንድ አስፈላጊ ነገር ነው። ዘመንን ያለማወቅ ችግር የክርስትናችንን ሩጫ እንደሚገባ እንዳንሮጥ መሰናክል ከሚሆኑብን ነገሮች አንዱ እና ዋናው  ነው።

 መቼም ዘመኑ የተገለባበጠበት፥ ዘመኑንም  ማስተዋል የተሳነው ክርስቲያን እንደዚህ ዘመን የበዛ አይመስልም። 

ጳውሎስ በዚህ መልዕክቱ ዘመኑን እወቁ የሚለን ከእኛ አንጻር ነው። ዘመኑ ለእኛ ለአማኞች ምንድነው? ዘመኑስ ምን ዓይነት ነው? ይኼን ያላስተዋለ አማኝ ብዙ ነገሩን ይስታል። እግዚአብሔር አብ ከታላቅ ምሕረቱ የተነሳ በልጁ ወንጌል ለጠራን በክርስቶስ የመስቀል ሥራ አምነን ለዳንን ለእኛ ለአማኞች ዘመኑ ምንድነው? ዘመኑን ማወቅ ካለብን በእርግጥም ለእኛ ለአማኞች ዘመኑ ከእንቅልፍ የምንነሳበት ሰዓት ነው ይለናል።

ከእንቅልፍ መነሳት ማለት ምንድነው?

ይኼን ለማብራራት ጳውሎስ እንዲህ ይለናል። "ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል"። 

 የሌሊትን ማለፍ እና የቀንን መቅረብ ሁኔታ በአትኩሮት ስናጤን በርግጥም ጳውሎስ ምን ሊለን እንደፈለገ ይገባናል። ጳውሎስ በዚህ ክፍል ሦስት የተለያዩ ጊዜዎችን ይነግረናል። ጊዜዎቹም ሌሊት፥ ቀን እና በሌሊትና በቀን መካከል ያለ ከእንቅልፍ የምንነሳበት ጊዜ ነው። ሌሊቱ የሚለው በክርስቶስ ከማመናችን በፊት የነበረውን በጨለማ ወይም በኃጢአት የነበርንበት ጊዜ ነው። ቀን የሚለው ደግሞ የክርስቶስ መምጣትና ከዚያ በኋላ ያለውን የዘላለም ዘመንን ነው። ሦስተኛው ደግም ከእንቅልፍ የምንሳበትን ወቅት ነው።

በእርግጥ ከእንቅልፍ የመነሻ ጊዜ በአሁኑ የሰለጠነው ዓለም የተለወጠ ቢሆንም ያኔ እዚያ መልክቱ የተጻፈበትን ዘመን ስንመረምር ሰዎች ከእንቅልፋቸው የሚነሱት ከሌሉቱ 10:30 ጀምሮ እስከ 11:30 ባለው ውስጥ እንደሆነ ታሪካዊ ዳራዎች ያመለክታሉ። በእርግጥ አሁንም ራቅ ወዳሉ የገጠር የሃገራችን ክፍሎች ስንሄድ ሰዎች ከእንቅልፋቸው የሚነሱት ከላይ በጠቀስኩት የሰዓት ክልል ውስጥ ነው።

ይኼ ከእንቅልፍ የመነሻ ጊዜ የእኛን ከጨለማ ማለትም ከኃጢአት ባርነት ወጥተን አሁን በእምነት በክርስቶስ ድነን ያለንበትን ጊዜ ይወክላል።  አዎ!  አሁን በክርስቶስ አምነን ከዚያ ከጨለማ ከሌሊቱ ጊዜ ወጥተናል። 

መጽሐፍም "ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን.." ይለናል። (1ጴጥ 2:9።)  በጌታም ብርሃን ሁነናል ነገር ግን እንደዚህ የሮሜ ክፍል አውድ ወደሙሉ ቀን ወይም ሙሉ ብርሃን ገና አልደረስንም። ወገግታው ላይ ነን።  ለዚያም ነው "ቀኑ" ተብሎ የጠራውን የክርስቶስን ዳግመኛ መገለጥ "ቀኑ ቀርቧል" የሚለን ጳውሎስ።

2. ለምንድነው ዘመኑን እንድናውቅ የተፈለገው?

ጳውሎስ ለምንድነው ዘመኑን እንዲያውቁ ወይም እንድናውቅ የፈለገው ለሚለው ጥያቄ  መልሱ ለዘመኑ እንደሚገባ እንድንኖር ነው። ዘመኑን አውቀናል እርሱም ከእንቅልፍ መነሻ ነው። 

ከእንቅልፉ የሚነሳ ሰው ደግሞ የሌሊት ልብሱን አውልቆ የቀኑን ልብስ ይለብሳል። ለዚያም ነው ጳውሎስ "ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ፤ " የሚለን። 

ሌሊቱ ስላለፈ ቀኑ ስለቀረበ የሌሊቱን ልብስ ማለትም የጨለማን ሥራ በማውለቅ የቀን ልብስ መልበስ አለብን። 

እኛም ሌሊቱ(በክርስቶስ ከማመናችን በፊት የነበረው ጊዜ) አልፎ ከእንቅልፍ የምንነሳበት ጊዜ ላይ ነን። "ቀኑ" ማለትም የክርስቶስን ምጻት ከፊት ለፊታችን ቀርቧል። ታዲያ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር ልንለብስ ይገባል። 

ጳውሎስም "በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን፤" ይለናል። ይልቁንም ካመንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን እየቀረበ ስለሆነ (የስጋ ትሥሳኤ) ኢየሱስን ልንለብስ ይገባል። 
ኢየሱስን መልበስ ሲባል  የኢየሱስን ባህሪ ፍቅርን፣ ጽድቅን፣ ቅድስናን..በሕይወታችን መግለጥ ነው።

Monday, June 1, 2020

❖የመዳን ወንጌል እና የተስፋው መንፈስ፦


«እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፣ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል ሰምታችሁ፣ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፣ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤»ብሏል /ኤፌ.1፡13/፡፡

1. ሰው ሁሉ ኃጢአተኛ ነው፦

ለሞት በሚያደርስ በሽታ እንደተያዙ የማያውቁ ሕሙማን ወደ ሐኪም ዘንድ ሄደው ለመታከምም ሆነ መድኃኒት ለማግኘት እንደማይንቀሳቀሱ ሁሉ ኃጢአተኛ መሆናቸውንና ኃጢአትም ዘላለማዊ ሞትን የሚያስከትል መሆኑን የማያውቁ ብዙ ሰዎች ስለመዳን መንገድ ለመረዳት ፍላጐት ላይኖራቸው ወይም ጊዜ ላይሰጡ ይችላሉ፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ግን ማንኛውም ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ እንደሚከተለው ይናገራል፡፡

«ሁሉ ዐመፁ በአንድነትም ረከሱ፤ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም እንኳ የለም»/መዝ.13፡3/፡፡

«ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፤ አስተዋይም የለም፤ እግዚአብሔርንም የሚፈልግ የለም፤ ሁሉ ተሳስተዋል፤ በአንድነትም የማይጠቅሙ ሆነዋል፤ ቸርነት የሚያደርግ የለም፤ አንድ ስንኳ የለም»/ሮሜ.3፡11-12/፡፡

«... ልዩነት የለምና፤ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና፤ የእግዚአብሔርም ክብር ጐድሏቸዋል»/ሮሜ.3፡22-23/፡፡

ከእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንደምንረዳው ማንኛውም ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ ነው፡፡ ሰው ሁሉ ኃጢአተኛ ሊሆን የቻለውም በኃጢአት ከወደቀው ከአንድ ሰው ማለትም ከአዳም የተወለደ በመሆኑ ነው፡፡ ኃጢአት ወደ ዓለም የገባውም በዚሁ በመጀመሪያው ሰው በኩል ነው፤ አዳም የተሰጠውን ትእዛዝ ቢተላለፍ ሞትን እንደሚሞት አስቀድሞ ተነግሮት ነበር /ዘፍ.2፡16-17/፡፡ ስለሆነም ትእዛዙን በተላለፈ ጊዜ ኃጢአት ወደ ዓለም ከመግባቱም ሌላ በኃጢአት ምክንያት የተፈረደው የሞት ፍርድ ለሰው ሁሉ ሊደርስ ችሏል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ይህን ሲናገር «ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በኃጢአትም ሞት፤ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ» ይላል /ሮሜ.5፡12/፡፡ ስለዚህ ማንኛውም ሰው በኃጢአት ከወደቀው ከመጀመሪያው ሰው ስለተወለደ ኃጢአተኛ ከመሆኑም ሌላ የሞት ፍርድ የተፈረደበትም ነው፡፡ ሆኖም እግዚአብሔር ለሰዎች ካለው ፍቅር የተነሣ ሰዎች ከዚህ ዘላለማዊ ፍርድ ይድኑ ዘንድ አንድ ልጁን አዳኝ አድርጎ ወደ ዓለም ልኳል፡፡

2. የእግዚአብሔር ፍቅር፦

እግዚአብሔር ጻድቅ ከመሆኑ አንጻር በኃጢአት ላይ የሚፈርድ እውነተኛ ፈራጅ የመሆኑን ያህል ኃጢአተኞችን ለማዳን የሚወድ የፍቅር አምላክም ነው፤ ይህ ፍቅሩ የተገለጠውም አንድ ልጁን ለእኛ በመስጠቱ ነው፤ መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ሲገልጽ «በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፤ ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና» ይላል /ዮሐ.3፡16-17/፡፡ ስለዚህ ኃጢአተኝነቱን ያወቀና በፍርድ ሥር እንዳለ የተረዳ አንድ ሰው ተስፋ ቈርጦ ከእግዚአብሔር ከመራቅ ይልቅ እግዚአብሔር ልጁን እስከመስጠት ድረስ እንደወደደው ሊገነዘብ ይገባል፡፡

ስለዚህይ አሁን ያለነው በምንም ሁኔታ ውስጥ ቢሆን እግዚአብሔር ልጁን ስለ እኛ ለሞት አሳልፎ እስኪሰጥ ድረስ የወደደን  መሆኑን ልናውቅ ይገባናል፡፡ 

ክርስቶስ በመስቀል ላይ የሞተው ሞት ይህን የእግዚአብሔርን ፍቅር ያስረዳል፤ መጽሐፍ ቅዱስ ይህን ሲናገር፦  «ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና፡፡ ስለ ጻድቅ የሚሞት በጭንቅ ይገኛልና፤ ስለቸር ሰው ግን ሊሞት እንኳ የሚደፍር ምናልባት ይገኝ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቷልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል» ይላል /ሮሜ.5፡6-8/፡፡ 

እግዚአብሔር ይህን ያህል እኛን  ኃጢአተኞቹን የሚወደን  ከሆነ እኛ ደግሞ እርሱ የሚያቀርብልንን የፍቅር ጥሪ ልንቀበል ይገባናል፡፡ 

እርሱ የሚጠራን እኛን ከዘላለም ጥፋት ለማዳን ነው፡፡ ስለዚህ የቀረበልንን የፍቅር ጥሪ ብንቀበል ለዘላለም የምንድነው እኛው ራሳችን ነን፡፡

3. የኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት፦

ሰው ከኃጢአትና ከዘላለም ሞት እንዲድን እግዚአብሔር ያዘጋጀው የመዳን መንገድ አንድ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው።  /ዮሐ.14፡6/፡፡ 

ኢየሱስ የሚለው የጌታችን ስም ትርጉምም አዳኝ ማለት ነው፡፡ በማቴ.1፡21 ላይ፦  «እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ» የሚለው ቃል ይህንን ያስረዳል። 

 እርሱ ወደ ዓለም የመጣበት ዋነኛ ዓላማም ሰውን ለማዳን እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ሲያስረዳ፦  «የሰው ልጅ የጠፋውን ለማዳን መጥቷልና /ማቴ.18፡11፤ ሉቃ.19፡10/፤ እንዲሁም፦  «ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው» /1ጢሞ.1፡15/ ይላል፡፡

 ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣበትን ይህንን ሰውን የማዳን ዓላማ ለመፈጸም እስከሞት ድረስ ታዝዟል፤ እርሱ በመስቀል ላይ የሞተው የሁላችንን ኃጢአት ተሸክሞና የሁላችን ምትክ ሆኖ ነው፤ «... እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ» /1ጴጥ.2፡24/ «አንዱ ስለሁሉ ሞተ፤ እንግዲያስ ሁሉ ሞቱ» /2ቆሮ.5፡14/ የሚሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ንባቦች ይህን ያረጋግጣሉ። 

 እርሱ ኃጢአት የሌለበት በመሆኑ ስለኃጢአተኞች መሞትና ኃጢአተኞችን ማዳን ተችሎታል፤ ኃጢአት ያለበት ማንም ቢሆን ይህን ማድረግ አልተቻለውም፡፡ ስለዚህ በሰማይም ሆነ በምድር ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አዳኝ የለም፤ መጽሐፍ ቅዱስ ከእርሱ በቀር ሌላ አዳኝ እንደሌለ አስረግጦ ሲናገር «መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና» ይላል /የሐ.ሥ.4፡12/፡፡ 

ከኃጢአተኝነታቸው የተነሣ በሞት ፍርሃት ውስጥ ለሚኖሩት ሁሉ ይህን የኢየሱስ ክርስቶስን ብቸኛ አዳኝነት መስማት ታላቅ የምስራች ነው፡፡ ይህም «የመዳን ወንጌል» ይባላል፡፡ 

ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች ሲጽፍ «እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፣ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል ሰምታችሁ፣ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፣ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤» ብሏል /ኤፌ.1፡13/፡፡ ይህም ቃል የመዳን ወንጌልን ተቀብለው በክርስቶስ ያመኑት ሁሉ የዘላለም መዳንን ከማግኘታቸውም በላይ በመንፈስ ቅዱስ መታተማቸውንም የሚያረጋግጥ ነው፡፡

መዳንንም  የምናገኘው በተሰተን ጸጋ ነው እንጂ መልካም ሥራን በመሥራታችን አይደለም። 
መጽሐፍ ቅዱስ ይህን በተመለከተ ሲናገር፦

 «ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለጠጋ ስለሆነ፣ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወትን ሰጠን፤ በጸጋ ድናችኋልና፣.. .. ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም» /ኤፌ.2፡4-9/ ይላል፡፡ 

እንዲሁም በሌላ ስፍራ «ነገር ግን የመድኃኒታችን የእግዚአብሔር ቸርነትና ሰውን መውደዱ በተገለጠ ጊዜ፣ እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፣ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለነበረው ሥራ አይደለም፤ ያን መንፈስም በጸጋው ጸድቀን በዘላለም ሕይወት ተስፋ ወራሾች እንድንሆን፣ በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ አትርፎ አፈሰሰው፡፡ ቃሉ የታመነ ነው» የሚል ቃል እናነባለን /ቲቶ3፡4-7/፡፡ 

ስለሆነም መዳን በጸጋ እንጂ በሥራ እንዳልሆነ ከእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባቦች ልንገነዘብ እንችላለን፡፡ መልካም ሥራ በኢየሱስ ክርስቶስ አምነን ከመዳናችን የተነሣ የምንሠራው ነው እንጂ መዳንን ለማግኘት የምንሠራው አይደለም፡፡ ሆኖም ከዳንን በኋላ መልካም ሥራን በመሥራት መዳናችን ይገልጣል፡፡ 

በኤፌ.2፡10 ላይ «እኛ ፍጥረቱ ነንና እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን» ተብሎ በተጻፈው ቃል መልካም ሥራ በክርስቶስ አዲስ ፍጥረት የመሆናችን ውጤት መሆኑን መረዳት ትችላለህ፡፡ ስለዚህ ሰው ሊድን የሚችለው በእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ መሆኑን ልናውቅ ይገባናል፡፡ ከእኛ  የሚፈለገው ኃጢአተኝነታችንን በማመን ንስሐ መግባትና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ብቻ ነው፡፡ ይህንንም ለማድረግ ጊዜ ሳናጠፋ አሁኑኑ ልንወስ ይገባናል፡፡ 

መጽሐፍ ቅዱስ «እነሆ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ የመዳን ቀን አሁን ነው» ይላልና /2ቆሮ.6፡2/፡፡

በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መሰብሰብ፦

ስለጌታችን ስለኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት ሰምተው በእርሱ ያመኑና የዳኑ ሰዎች ከማያምኑት ተለይተው  በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መሰብሰብ አለባቸው፡፡ 

ጌታችን በስሙ ስለመሰብሰብ ሲናገር፦  «ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ እኔ በመካከላቸው እሆናለሁና» ብሏል /ማቴ.18፡20/፡፡ 

ከማያምኑት ተለይተው በኢየሱስ ስም የሚሰበሰቡትን እግዚአብሔር በዚያ ስፍራ ይቀበላቸዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ከማያምኑት ስለመለየት በሚናገርበት ክፍል ውስጥ «ስለዚህም ጌታ፡- ከመካከላቸው ውጡና የተለያችሁ ሁኑ ርኵሱንም አትንኩ» ይላል፤ ሁሉን የሚገዛ ጌታ እኔም እቀበላችኋለሁ ለእናንተም አባት እሆናለሁ፤ እናንተም ለእኔ ወንድ ልጆችና ሴት ልጆች ትሆናላችሁ ይላል፡፡» በማለት ይናገራል /2ቆሮ.6፡17-18/፡፡ እንዲሁም በዕብ.13፡13 ላይ «እንግዲህ ነቀፌታውን እየተሸከምን ወደ እርሱ ወደ ሰፈሩ ውጭ እንውጣ» በማለት የአማኞች ስፍራ የት እንደሆነ በግልጽ ይነግረናል፡፡ 

ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም «እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ» በማለት ሰዎችን ወደ ራሱ ይጠራል /ማቴ.11፡28/፡፡

  ውዳሴና አምልኮት የዘላለምን ሕይወት ለሰጠን ለነፍሳችን እረኛና ጠባቂው ክርስቶስ ይሁን!!!

Sunday, May 31, 2020

❖በልዑል መጠጊያ የሚኖር፦

ይህ የመዝሙር ክፍል አማኞች እምነታቸውን በእግዚአብሔር ላይ በመጣል ምን ያህል ዋስትና እንዳላቸው የሚያሳይ ነው። እግዚአብሔር በአደጋዎች ሁል መጠጊያችን እንደሚሆን፣ ከዚህም የተነሣ መንፈሳዊና ሥጋዊ አደጋ ሲመጣ ቀድመን የእግዚአብሔርን ጥበቃ ልንፈልግ እንድምንችል የሚረጋግጥ ስንኝ ነው።

በእግዚአብሔር ለተወደድን ይኸውም ራሳችንን ለልዑል እግዚአብሔር ፈቃድና ጥበቃ አሳልፈን ለምንሰጥ፣ በእግዚአብሔር ሀልዎት ዕለት ዕለት ለመኖር ለምንፈልግ እጅግ ዋስትና ይሰጣል። 

 "በእጁ ጥላ ሰወረኝ፤ የተወለወለ ፍላጻ አደረገኝ፤ በሰገባውም ውስጥ ሸሸገኝ"።እንዳለው ነብዪ (ኢሳ 49፥2) እግዚአብሔር የእውነት መደበቂያችን ነው። ተሸጉጠን ክፉውን የምናሳልፍበት ምሽጋችን።

የዚህን መዝሙር ስንኞችን ሲያነብ ከነችግሩና መከራው አንብቦ የሚጨርስ ማነው? ስትጀምር የነበረው አደጋ ወይም መከራ ሁሉ ቁጥር አንድ ጋር አብቅቶ ሌላ ርዕስ ውስጥ ትገባላችሁ። እስኪ ከፋፍለን የእግዚአብሔርን ጥበቃ እንቃኘው

1) መዝሙሩ 91፥1-2 ፦
'' በልዑል መጠጊያ የሚኖር ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ ያድራል።እግዚአብሔርን። አንተ መታመኛዬ ነህ እለዋለሁ፤ አምላኬና መሸሸጊያዬ ነው፥ በእርሱም እታመናለሁ። ''

ከሁሉ በላይ የሆነውንና የኃይሉን አምላክ መጠጊያው አድርጎ የሚኖር ሰው የሕይወቱ ዋስትና የሚያስተማምን በመሆኑ እግዚአብሔር መጠጊያዬና ምሽጌ የምተማመንበት ፈጣሪዬም ነው ብሎ ይመሰክራል።
   =} ምሳሌ:- አንድ ህፃን አባቱ እቅፍ ውስጥ ሆኖ ወደ ላይ እየወረወረ ሲያጫውተው ከሚተማመነው በላይ አደጋ ውስጥ ሆነን በእግዚአብሔር መተማመን። ይህንንም በእምነት መመስክር ያጋጠመን አደጋ ከእኛ ያሸሸዋል።

2) መዝሙር 91፥3-4፦
'' እርሱ ከአዳኝ ወጥመድ ከሚያስደነግጥም ነገር ያድንሃልና። በላባዎቹ ይጋርድሃል፥ በክንፎቹም በታች ትተማመናለህ፤ እውነት እንደ ጋሻ ይከብብሃል። ''

እግዚአብሔር ሕዝቡን ከጠላት ይጠብቃል፣ በላባዎቹ ይጋርዳቸዋል፣ ጋሻ እና መከታ ይሆናቸዋል። ለእርሱ የአደጋውም ሆነ የችግሩ ግዝፈት እኛን ከመጠበቅ አያስቀረውም።
   =} አባባል:- ለእግዚአብሔር የችግርህን መጠን ከምትነግረው ይልቅ የእግዚአብሔርን ታላቅነት ለችግርህ ንገረው። የተባለውም ለዚህ ነው።

3) መዝሙር 91፥5-6፦
'' ከሌሊት ግርማ፥ በቀን ከሚበርር ፍላጻ፥ በጨለማ ከሚሄድ ክፉ ነገር፥ ከአደጋና ከቀትር ጋኔን አትፈራም። ''

የእግዚአብሔር እንክብካቤ ጽኑና በቂ ነው ምክንያቱም ጥበቃው የተመሰረተው በማንነቱ ላይ ስለሆነ። እርሱ ሲጠብቅ ቀን አይል ሌሊት አይል ሁልጊዜ ነው። በጊዜ አይወሰን በስፍራም እንዲሁ በመዞር የተደረገ ጥላ የለበትምና። የእግዚአብሔር ጥበቃ በቀንና በሌሊት እንደ ሆነ ተፈጥሮአዊ በሆኑ ምክንያቶች ከሚመጣ ፍርሀትና ድንጋጤ ይጠብቀናል።
=} ሰባኪው:- እንኳን ሌሊት ተኝተን አይደለም ቆመንም አይተን ከምናልፈው አደጋ ሳናየው ጠብቆን ያሳለፈን እጅግ ብዙ ነው። ተውት ያስተዋልነውን!!!

4) መዝሙር 91፥7፦

'' በአጠገብህ ሺህ በቀኝህም አሥር ሺህ ይወድቃሉ፤ ወደ አንተ ግን አይቀርብም። ''

እርሱ በምድር ላይ በሚሆኑ ነገሮች ሁሉ ላይ ሙሉ ሥልጣን ስላለው ለጥበቃው ወሰን የለውም። እንክብካቤውና ጥበቃው የእግዚአብሔርን ታላቅነት ለማሳየት ሺህ እና አሥር ሺህ በማለት ይገልፀዋል። እግዚአብሔርን የሚያልፍ ችግር የለም።
   =} መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪክ:- ሕዝያስ እንዳጽናናቸው
(መጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልዕ 32፥7-8 ) ጽኑ፥ አይዞአችሁ፤ ከእኛም ጋር ያለው ከእርሱ ጋር ካለው ይበልጣልና ከአሦር ንጉሥና ከእርሱ ጋር ካለው ጭፍራ ሁሉ አትፍሩ፥ አትደንግጡም። ከእርሱ ጋር የሥጋ ክንድ ነው፤ ከእኛ ጋር ያለው ግን የሚረዳንና የሚዋጋልን አምላካችን እግዚአብሔር ነው ብሎ አጸናናቸው። ሕዝቡም በይሁዳ ንጉሥ በሕዝቅያስ ቃል ተጽናና።

5) መዝሙር 91፥8፦
'' በዓይኖችህ ብቻ ትመለከታለህ፥ የኃጥኣንንም ብድራት ታያለህ። ''

ጻድቃን የእግዚአብሔርን ማዳን በእምነት ዐይን ማየታቸው ይበለጥ እንዲበረቱ ያደርጋቸዋል እግዚአብሔር ጻድቃንን ለመጠበቅና ለመባረክ ቃል ገብቷል ጻድቃን የእግዚአብሔርን ፍትሕና ታማኝነት እንዲሁም የክፉዎችን መቀጣት በዐይናቸው ይመለከታሉ።
=} አመለካከት:- ሰው በሚያየው ሳይሆን በሚያምነው ይኖራልና።

6) መዝሙር 91፥9-10፦
'' አቤቱ፥ አንተ ተስፋዬ ነህና፤ ልዑልን መጠጊያህ አደረግህ። ክፉ ነገር ወደ አንተ አይቀርብም፥ መቅሠፍትም ወደ ቤትህ አይገባም። ''

ልዑሉን መጠጊያችን በማድረግ የጥበብን መንገድ እንድንከተል ያበረታታል እርሱ መጠጊያችን ነው በምድር ላይ የሚሆነው ማንኛውም ነገር በእርሱ ቁጥጥር ሥር ነው ክፉ ነገር ወይም መቅሠፍት ቢሆን ያል እርሱ ፈቃድ አይሆንምና።
=} ሂሳባዊ ቀመር:- ይጠጌ አይነኬ (asymptote)፤ ቅርብ ቢመስልህም፣ ሊነካ የቀረበ ቢመስልም ሁሉን ማድረግ በሚቻለው ሀሳቡም ይከለከል ዘንድ ከቶ በማይቸለው ተአምር አድራጊነት ሳይነካህ ያልፋል። ይታከክሃል አይነካህም ይቀርብሃል አይደርስብህም ይመጣብሃል አያገኝህም።

7) መዝሙር 91፥11-13፦
'' በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ። ''

እግዚአብሔር እኛን አማኞችን በምንሄድበት ሁሉ ይጠብቁን ዘንድ መላእክቱን ያዛቸዋል። መላእክቱ እኛን ከአደጋ ለማስመለጥ እንዲጠብቁን ዘወትር እንዲታደጉን በተጠንቀቅ በዙሪያችን አሉ። እግዚአብሔር በልጆቹ ላይ ብዙ ነገር እንዲደርስ ሊፈቅድ ይችላል ይሁንና አንድም ኅይል ከእግዚአብሔር ቁጥጥር ውጭ አንዳልሆነ ያውቃሉ።

8) መዝሙር 91፥14፦
'' በእኔ ተማምኖአልና አስጥለዋለሁ፤ ስሜንም አውቆአልና እጋርደዋለሁ። ''

እግዚአብሔር እርሱን ለሚወዱት እና ስሙም ለሚያውቁ ሁሉ የማዳኑን ንግር ያበሰረበት ክፍል ነው። መውደድ የሚለው ቃል እግዚአብሔርን ከልብ መናፈቅንና መሻትን ይሆንላቸዋል።
=} የጌታ ቃል:- ዶሮ ጫጩቶቿን በክንፎቿ በታች እንደምትሰበሰብ እንዴት ይልቅ እርሱ እንደሚጋርደን።

9) መዝሙር 91፥15፦
'' ይጠራኛል እመልስለትማለሁ፥ በመከራውም ጊዜ ከእርሱ ጋራ እሆናለሁ፤ አድነዋለሁ አከብረውማለሁ። ''

ይህ ቃል የአማኝ የድምፅ ብክነትን የሚባል ነገር እንደሌለ ያሳያል። ሲጣር ደመና አይከለክለውም፣ የፀሐይ ግርዶሽ አይዘውም፣ ንፋስ አይወስደውም፣ ዝናብ አይመልሰውም። አቤት የሚል ብቻ ሳይሆን በመከራ የማይተወን አብሮን የሚሆን ደግሞም የሚያድነን ጌታ አለ።

10) መዝሙር 91፥16፦
'' ረጅምን ዕድሜ አጠግበዋለሁ፥ ማዳኔንም አሳየዋለሁ። ''

ሐዋርያው ጳውሎስ እጅግ ሲገረም ''እንግዲህ ምን እንላለን'' ይላል ደግሞስ ምንስ ይባላል እኔም ከምናገር እጅህን አፍህ ላይ ጫን ይለኛል። ይህ ሁሉ ጥበቃ ለእኔና ለአናንተ ነው። እውን ከዚህ የቀረበ ደግሞም ህያው የሆነ ነገር ምን አለ?
      እግዚአብሄር ይክበር ይመስገን!!!

Wednesday, May 27, 2020

❖እንደምወድህ አንተ ታውቃለህ፦

  እንደምወድህ አንተ ታውቃለህ፦
        (ዮሐ 21፡17)
የክርስቶስ በጥብርያዶስ መገለጽ ሦስተኛው መገለጥ ነው። ጥብርያዶስ በባህር አጠገብ ያለ ቦታ ነው። ባህሩም የጥብርያዶስ ባህር ተብሎ ይጠራል። ክርስቶስ ዓሳ እያጠመዱ ሳሉ ተገልጾላቸዋል። 

በዚህች ሌሊት እነ ጴጥሮስ ምንም ዓሣ አልያዙም አለመያዛቸው የጌታ ፍቃድ አለመሆኑን ያስረዳል። ሰውን እንጅ ዓሣን እንደማያጠምድ አስቀድሞ የተናገራቸውን መዘንጋታቸው በዝህች ሌሊት ድካማቸው ከንቱ እንዲሆን ሆኗል። 

ያለ ጌታ ፍቃድ የሚሰራ ሥራና የሚደከም ድካም ውጤት እንደሌለው እንዲረዱ አድርጎአቸዋል። ሌሊት ያልተያዘው ዓሣ በንጋት በጌታ ቃል መረባቸውን ወደ ባህር በጣሉ ጊዜ ብዙ ዓሣ ተይዞአል። 

ይህም የጌታ ቃል ሁሉን እንደሚያደርግና ማድረግም እንደሚችል። እንዲያምኑ ረድቶአቸዋል። መታዘዛቸው ብዙ ዓሣ ለማግኘታቸው ዋነኛ ነው። ተስፋም አልቆረጡም። ሌሊቱን ሁሉ አልያዝንም ብለው መረባችንን አንጥልም አላሉምና። 

ጌታ መሆኑን ያወቁት ከታዘዙት በኋላ ነው በመታዘዛቸው ብዙ ዓሳ ሲያዝላቸው ነው። መታዘዝ የተሰወረውን ይገልጻል ያጡትንም ያስገኛል። 

ወደ ወደቡ ወይም ከባህሩ ከወጡ በኋላ የተጠበሰ ዓሳና የተዘጋጀ እንጀራ፤ የነደደ እሳት አግኝተዋል። ይህ ሁሉ ያልደከሙበት ነው፤ ታዘዙ በመታዘዝ የሰሩት ውጤታማ ሁነላቸው። የተዘጋጀ እንጀራና ዓሳ አገኙ።

ምስጢሩ ለሐዋርያነት ታዘው ዓለምን ሲያስተምሩ ሰውን እንደ ዓሳ ይስበስባሉ። በጌታ የተዘጋጀ ስማያዊ ጸጋንም ያገኛሉ። 

ተዘጋጅቶ የተገኘው እንጀራና ዓሳው እግዚአሔር የሚሰጠውን ጸጋ ያመለክታል።

ጴጥሮስን ትወደኛለህን? ብሎ ሦስት ጊዜ ጠይቆታል። እንደሚወደውም ባረጋገጠ ጊዜ በጎቼን፤ግልገሎቼን፤ጠበቶቼን ጠብቅ ብሎታል።  ጴጥሮስ የጌታን ፍቅር መግለጽ ያለበት እነዚህን በመጠበቅ ነው። ከዚህ የበለጠ ፍቅርም እንደማይኖር ደጋግሞ በመጠየቅና ከወደድከኝ ጠብቅ በማለት አስረድቶታል። በወደደው ልክ ምዕመናኑን መጠበቅ እንዳለበት ተረድቷል። 

ክርስቶስ ለጴጥሮስ ሲናገር ሽማግሌና ጎልማሳ ብሎታል። በጎልማሳነቱም ጊዜ የወደደውን የሚሰራበት ነበር ይህ ማለት ስሜቱን ተከትሎ ይኖር ነበር ማለት ነው። ሽምግልናው ግን የመንፈስ ቅዱስን ፈቃድ ተከትሎ እንደሚሄድ ያስረዳል። 

ሽምግልና በአእምሮና በእውቀት በመንፈስ ቅዱስም ማደጉ ነው። ትጥቁም የመንፈስ ቅዱስ ነው። ሌላ ያስታጥቅሃል ወደ ማትወደውም ትሄዳለህ ተብሎአል። የማይወደውን ሞትና መከራ ለመቀበል እግጁ መሆኑን ያስረዳል። 
           ክብር ለስሙ ይሁን!!!

❖አርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፤ ወነበረ በየማነ አቡሁ፦

አርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፤ ወነበረ በየማነ አቡሁ፦
       (ጸሎተ ሃይማኖት አንቀጽ 7)

    ዓለምን በሞቱ ና በትንሳኤው በፍቅሩና በኀይሉ ማርኮ ዐረገ። 

ስለዚህ፦ ወደ ላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን ማረከ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ ይላል።
ሰይጣንን የማረከው በሃያልነቱ ነው።
ከእርሱ ይልቅ የሚበረታ መጥቶ ሲያሸንፈው ግን፥ ታምኖበት የነበረውን ጋሻና ጦር ይወስድበታል ምርኮውንም ያካፍላል።    (ሉቃ 11፥22) 

ሰይጣን የሚታመንበት የክፋትና የጥላቻ ጋሻና ጦር ነበረው። በሁሉም ላይ በፍቅሩ መልቶ ለመኖር ከሰማይ ወረደ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ደግሞ ያው ነው። ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ደግሞ ያው ነው ። (ኤፌ 4፥8-10)
በዓለም ላይ ሃይሎ የነበረውን ሰይጣንን አስሮታል። ተቆጣጥሮት የነበረውን ሁሉ ወስዶበታል። 

"ወይስ ሰው አስቀድሞ ኃይለኛውን ሳያስር ወደ ኃይለኛው ቤት ገብቶ እቃውን ሊነጥቀው እንዴት ይችላል? ከዚያም ወዲያ ቤቱን ይበዘብዛል።" (ማቴ 12 .29 )

ጌታችን እንደተናገረው ኀይለኛው ባይታሰር ኖሮ ተቆጣጥሮት የነበረውን ሁሉ መማረክ አይችልም ነበር በኀጢአታችን ላይ በርትቶ የነበረው ታስሯል ።ጌታችን ድል አድርጎ ወደ ሰማይ ዐረገ በእግዚአብሔርም ቀኝ ተቀመጠ። ዳግማኛም ይመጣል።
          ለርሱ ከዘላለም እስከ ዘላለም ክብር ይሁን!!!

Saturday, June 15, 2019

❖መንፈስ ቅዱስ፦

መንፈስ ቅዱስ ማን ነው?

፩. መንፈስ ቅዱስ ማን ነው?

  ☞ ከሦስቱ የሥላሴ አካላት አንዱ አካል ነው፡፡

  ☞ የማይጨበጥ፤የማይታይ አካል ያለው መንፈስ ነው፡፡

  ☞ የሰረፀው (የወጣው) ከአብ ነው።

  ☞ ከአብ ከወልድ ጋር እኩል ምስጋና አምልኮ ይገባዋል

  ☞ እግዚአብሔር (አምላክ) ነው፡፡

  ☞ የአብ የወልድ እስትንፋስ (ሕይወት)ነው፡፡

  ☞ በነቢያትና በሐዋርያት አድሮ የተናገረ፥ሕይወትንም ያቀና : ምድርን ለክብሩ ያስጌጠ ነው፡፡

፪. የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌዎች ምን ምን ናቸው? ርግብ፣ እሳት፣ ውኃ፣ ዘይትና ነፋስ ናቸው። 

☞  ርግብ የዋህ ናት፡ መንፈስ ቅዱስም የዋህና ቂም የማያውቅ ነው፡፡ ርግብ በኖህ ዘመን የጥፋት ውኃ መድረቁን  ያወጀች  የሰላም ምልክት ናት፤ መንፈስ ቅዱስም ክርስቶስ ሲጠመቅ የኃጢአት ባሕር መድረቁን በርግብ ምሳሌ ወርዶ የሰበከ የሰላም ጌታ ነው።

☞  እሳት ያበስላል፡ መንፈስ ቅዱስ ሕፃን የሆነውን አእምሮ በጥበብ ያጎለምሳል፡፡ እሳት የከበረ ማዕድንን ከአፈር ይለያል፥ መንፈስ ቅዱስም አምኖ የከበረውን ፡ ካላመነው ይለያል፡፡

☞  ውኃ ያነፃል፥ መንፈስ ቅዱስ ይቀድሳል፡፡

☞  ነፋስ፣ ነፍስና መንፈስ የሚወጡበት የግሪክ ቃል ኒዩማ የሚል ሲሆን ከነፋስ- ነፍስ፤ ከነፍስ- መንፈስ ይረቃል። ነፋስ በእንቅስቃሴው እንደሚታወቅ መንፈስ ቅዱስም በሥራው ይታወቃል፡፡

❖  በብሉይ ኪዳን የመብራት ዘይት ነበረ፥ በየዕለቱ በመቅረዙ ይጨመራል፡፡ ይህ የመብራቱ አለመጥፋት የመንፈስ ቅዱስን መኖር ያመለክታል፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ ለቅርፅ አልባዋ መሬት ውበት ያፈሰሰ፥ ውኆችን ለፍጥረት ጥቅም የቀደሰ ጌታ ነው፡፡ "ምድርም ባዶ ነበረች፥ አንዳችም አልነበረባትም፤ ጨለማም በጥልቁ ላይ ነበረ፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በውኃ ላይ ሰፍፎ ነበር።" ኦሪት ዘፍጥረት 1:2።

❖  መንፈስ ቅዱስ መሳፍንትን በምስፍና፥ ነገሥታትን በንግሥና፥ ካህናትን በክህነት ጸጋ፥ ነቢያትን በሀብተ ትንቢት፥ ዘማርያንን በዝማሬ ጸጋ፥ ፈዋሾችን በሀብተ ፈውስ ......የሾመ...ጸጋ የሰጠና ጸጋን ያደላደለ ቅዱስ መንፈስ ነው፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ ቅድስት ኤልሳቤጥ ለድንግል ማርያም የሆነላትን እንድትረዳ አደረባት፡፡ ድንግል ማርያም በድንግልና እንድትወልድ ሁሉን አስቻላት፡፡ በክርስቶስ አገልግሎት ነበረ፡፡ ክርስቶስ ከማረጉ በፊት ስለ መንፈስ ቅዱስ መምጣት ተናግሯል፡፡

☞   "አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።" የዮሐንስ ወንጌል 14:26

☞  "እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ። እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤ ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ነው፤ ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው። የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ፥ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም። ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል።" ዮሐንስ 16:7-15::

☞   " ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤" የዮሐንስ 15:26።

☞  " ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል፤እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ።" ዮሐንስ 14:15-16::

❖  በመጽሐፍ ቅዱስ አንዱ መንፈስ ቅዱስ በአደራረጉ ምክንያት:- 

    ☞  የእውቀት መንፈስ፣ 

    ☞  የጥበብ መንፈስ፣ 

    ☞  የኃይል መንፈስ፣ 

    ☞  የእውነት መንፈስ፣ 

    ☞  የመገለጥ መንፈስ፣ ...ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በክርስቶስ አገለግሎት የነበረው ሱታፌ እንዳለ ሆኖ በክርስቶስ ትምህርት እንዴት እንደተገለጠ ከላይ ባሉት ጥቅሶች አይተናል፡፡ በክርስቶስ ትምህርት አጽናኝ(ጰራቅሊጦስ)፣ የእውነት መንፈስ እና ሁሉን የሚነግር መምህር ተብሏል፡፡ የሚመጣው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው፡፡ የሚመጣበት አላማ ስለ ክርስቶስ ለመመስከር ነው፡፡ ስለዚህ በክርስቶስ የማያምኑትን ይወቅሳል፤ የዲያብሎስን መጣል ይናገራል፤ ጽድቅ ወደ አብ በሄደው በክርስቶስ እንደሆነ ይመሰክራል፤ የቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ ይመራል፤ ምእመናንን ያጽናናል፤ ለበጉ ሠርግ ያዘጋጃል፤ አገልጋዮችን ያሰማራል፡፡ 

❖  ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባረገ በአስረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስ ወደ ዓለም መጣ፤ በጽርሐ ጽዮን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የተወለደችውን የክብርት ቤተክርስቲያን ልደት በእሳት ላንቃ በዓለም ቋንቋ አከበረ፡፡ ሐዋርያትን ለእውነት አስጨከነ፤ ምስጢር እና ብዙ ቋንቋዎች ገለጠላቸው፡፡ በጉዞቸው ሁሉ አብሮ ነበረ፡፡ ዛሬም የቤተክርስቲያን አገለግሎት ሕይወት መንፈስ ቅዱስ ነውና ክብር ለመንፈስ ቅዱስ!!

❖  ላመነ ሰው ጥምቀት የሚፈጸመው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነው፡፡ ይህም የክርስቶስ ትእዛዝ ነው፡፡ ማቴ 28:19:: በጥቅሉ ያለ መንፈስ ቅዱስ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን አይፈጽሙም፡፡ የምስጢራቱ አፈጻጸም ሥርዓት የሚመራው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ 

በመግቢያዬ እንደጻፍኩት ቤተክርስቲያን ስለ መንፈስ ቅዱስ ጠንካራ አቋም አላት፦ "ማህየዊ በሚሆን በአንድ ጌታ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን፤ እርሱም ከአብ የሰረፀ ነው፡፡ በነቢያት እና በሐዋርያት ተናግሯል፡፡ ከአብ ከወልድ ጋር ምስጋና ይገባዋል።" ጸሎተ ሃይማኖት አንቀጽ ፰.

መንፈስ ቅዱስ፦

☞  ሕይወት ሰጭ፤ ጥበብ ገላጭ መንፈስ ነው፡፡

☞  የጸጋ ምንጭ እና አደላዳይ ነው፡፡

☞  ለበጎ ሥራ ቀስቃሽ፤ከኃጢአት እንድንወጣ ወቃሽ ነው

☞  ልብን አይቶ የሚሾም፤ ትሁታንን የሚያከብር ቅዱስ መንፈስ ነው፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ኃይል ነው፡፡ ብርታት የሆነን እርሱ ነው፡፡ ስንደክም ያግዘናል፡፡ እንዴት መጸለይ እንዳለብን ያስተምረናል(ሮሜ 8:26-27)፥ እንዴት ማምለክ እንዳለብን ይመራናል፥ ከዚያ ጸሎታችንን ይሰማል፤ አምልኮችንን ይቀበላል፡፡

❖  የመንፈስ ቅዱስ ነገር ለፍጥረታዊው ሰው ሞኝነት ነው፡፡ "ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፤ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ሆነ ሊያውቀው አይችልም።" 1ቆሮንቶስ 2:14። የመንፈስ ቅዱስ ጉዳይ በእምነት መንፈስ እንጂ በሥጋ አይመረመርም፡፡ የጰራቅሊጦስ የተቀበልነው ይህን የእውነት መንፈስ ነው፡፡ "እኛ ግን ከእግዚአብሔር እንዲያው የተሰጠንን እናውቅ ዘንድ ከእግዚአብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንም።" 1ቆሮንቶስ 2:12።

❖  መንፈስ ቅዱስ በፍጥረታዊ ሰው አይኖርም፡፡ እንዲያውም የክርስቶስ መንፈስ የሌለው የክርስቶስ ወገን አይደለም፡፡ "የክርስቶስ መንፈስ የሌለው ከሆነ ግን ይኸው የእርሱ ወገን አይደለም።" ሮሜ 8:9።

❖  ምክር፣ ጥበብ፣ ምስጢር፣ ትንቢት፣ ፈውስ፣ ዝማሬ፣ ሹመት፣ ኃይል .... ከመንፈስ ቅዱስ ይሰጣሉ፡፡ ደስታ፣ ፍቅር፣ እምነት፣ የዋሃት፣ ራስን መግዛት፣ ትዕግስት፤ በጎነት፣ ቸርነትና ሰላም የመንፈስ ፍሬ ናቸው፡፡ ገላ 5:23:: 

❖  መንፈስ ቅዱስ ከምንተነፍሰው አየር በላይ ያስፈልገናል፡፡ በሥራችን ዐመፃ የመንፈስ ቅዱስን አሠራር ልንቃወም እንችላለን፡፡ "መንፈስን አታጥፉ፤" 1ተሰሎንቄ 5:19። ንጉሥ ዳዊት በበደለ ጊዜ ይህ አጋዥ፣ አስተማሪ፣ መሪ እና አጽናኝ መንፈስ እንዳይወስድበት ለመነ፡፡ "ከፊትህ አትጣለኝ፥ ቅዱስ መንፈስህንም ከእኔ ላይ አትውሰድብኝ።" መዝሙረ ዳዊት 51:11።

❖  መንፈስ ቅዱስ ከተለየን ሕይወት፣ ሰላም፣ ዕረፍት፣ መንፈሳዊነት ... የንስሐ ጸጸት...ይለዩናል፡፡ ስለዚህ "ለቤዛም ቀን የታተማችሁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ። መራርነትና ንዴት ቁጣም ጩኸትም መሳደብም ሁሉ ከክፋት ሁሉ ጋር ከእናንተ ዘንድ ይወገድ። እርስ በርሳችሁም ቸሮችና ርኅሩኆች ሁኑ፥ እግዚአብሔርም ደግሞ በክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ ይቅር ተባባሉ።" ኤፌ 4:30-32:: የሥጋ ሥራ ከመንፈስ አላማ ያወጣል፡፡ የሥጋ አሠራር መንፈስ ቅዱስን ይቃወማል፡፡ ደስታ የሰጠን ሀዘን ሊቀበል አይችልም፡፡ ባናከብረው ደስታ የምናጣው እኛ ነን፡፡ " ለአሠራሩ እንመች፡፡ በኖህ ዘመን ርግቧ በመጀመሪያው ጉዞዋ ማረፊያ አጥታ እንደተንከራተተች መንፈስ ቅዱስም ለአሠራሩ የሚመች ሰው አጥቶ በዙሪያችን አለ።" ለአሠራሩ እንመች፡፡ እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ አደረሰን፡፡ ስለመንፈስ ቅዱስ አንብቡ ፥ ዘምሩ፡፡ 

 ለመንፈስ ቅዱስ ክብርና ምስጋና ይገባል!!! 

Sunday, June 9, 2019

❖የጠፋው ልጅ፦

✞📖የጠፋው ልጅና የእግዚአብሔር ፍቅር!

    💌በአዲስ ኪዳን ውስጥ ከተዘገቡልን ድንቅ ምሳሌዎች አንዱ የጠፋው ልጅ ምሳሌ ነው። የጠፋውን ልጅ ታሪክ ስናነብ በእንባ እንሞላለን። ጽድቅ ሳለ ኩነኔ፣ ዕረፍት ሳለ ሁከትን መርጦ ለሚቅበዘበዘው የሰው ልጅ የፍቅር ዕንባ እንድናፈስ ያደርገናል። ከሁሉ በላይ ግን የጠፋው ልጅ አባት ፍቅር በዕንባ እንድንታጠብ ያደርገናል። ወደ እርሱ አንድ እርምጃ ሲመጡ አስር እርምጃ ወደ ጠፉት የሚመጣ፣ ሂሳብ ለመተሳሰብ የማይሻ፣ ተበደልኩ ሳይሆን ተጎዳችሁ ብሎ የሚያለቅስ ፣ ከነ ቆሻሻ የሚያቅፍ ፣ ልብስን ታሪክን የሚለውጥ ያ አባት ፍቅሩ ያስለቅሳል።

    📝 የጠፋው ልጅ ታሪክ የፈጠራ ድርሰት ወይም የሩቅ ዘመን ሀቅ አይደለም። የጠፋው ልጅ እኛ ነን። ወይ ጠፍተን እየተጎዳን ነው አሊያም የተገኘን ነን። በጠፋው ልጅ ታሪክ ላይ ደርበን ከመጻፍ ውጭ የግርጌ ማስታወሻ መያዝ አንችልም። የታሪካችን ማስታወሻ ምውትነት ነው። ለዚህ ነው ሐዋርያው፦ "በበደላችሁና በኃጢያታችሁ ሙታን ነበራችሁ" የሚለወ(ኤፌ.2፥1)።  ሞትን በነበር ያስቀረልን የሕይወት ራስ የሆነው ክርስቶስ ነው። የተፈቀረው ይህ ምውት ማንነት ነው። ምውትን ማን ይቀርበዋል? ቅድም ስንዳብሰው ቆይተን ሲሞት ሬሳው ብለን እንሸሸዋለን። እኛን የወደደ ቡሩክ ነው!

   "የጠፋው ልጅ ነበርኩ እጅግ ቀበዝባዛ፣
    የነፍሴ መድኃኒት ኢየሱስ ሆነኝ ቤዛ"
እያልን ከመዘመር ውጭ ሌላ ቃል የለንም።

     📝ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ስለ መጥፋት በብዙ ይጽፋል። የሉቃስ ወንጌል መሪ ጥቅስም፦ "የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአልና" የሚል ነው(ሉቃ.19:10)።  ሉቃስ ይባስ ብሎ ስለ ጠፋው ኢየሱስ ጽፏል(ሉቃ.2:41-51)።  ያለ ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ቀን መጓዝ እርሱን ለማግኘት ሦስት ቀን ያንከራትተታል። መጸለይን፣ ኅብረት ማድረግን ለአንድ ቀን መተው ሰላሙን ለመመለስ ሦስት ቀን ይፈጃል።

💌ወንጌላዊው ሉቃስ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣበትን ዓላማ ሲገልጥ፦ "የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቷልና" ብሏል(ሉቃ.19:20)። ታዲያ በምዕራፍ 15 ላይ ስለ ጠፊዎች ወይም ስለ ጠፉ ወገኖች በሙሉነት ይተርካል።  የጠፋው በግ፣ የጠፋው ድሪም(ገንዘብ)፣ የጠፋው ልጅ።
የጠፋው በግ በደጅ፣ የጠፋው ድሪም በቤት፣ የጠፋው ልጅ በሩቅ አገር ነው። የጠፋው በግ በሞኝነት፣ የጠፋው ድሪም አለሁ እያለ በመሞት፣ የጠፋው ልጅ በምርጫ ነው። የጠፋው በግ አለማውያንን ይመለከታል። ባለ ማወቅና በሞኝነት ጠፍተዋል። መመለሻውን አጥተው የሚንከራተቱ ምስኪኖች ናቸው። የጠፋው ድሪም ግን ያለሁት እዚሁ ነው ብሎ መጥፋቱን ማወቅና ማሳወቅ አይችልም። የጠፋውም በደጅ ሳይሆን በቤት ውስጥ ነው። በእግዚአብሔር ቤት የጠፉ፣ አለን እያሉ ተበልተው ያለቁትን አገልጋዮችና ምዕመናንን ይመለከታል።

   "በአደባባይ ቆሜ ስምህን ከመስበክ
     መጀመሪያ ልቤ ለፍቅርህ ይንበርከክ
     ከአገልግሎት በፊት አንተን ልወቅህ
     መሥዋዕት ከማቅረብ ልታዘዝልህ"
ማለት ይሻላል።

     📖የጠፋው ልጅ የጌታን ሰላም ቀምሶ ፣ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተካፍሎ፣ በሰላሙ አርፎ የነበረ ምዕመንን ይገልጣል። ይህ ምዕመን ግን ትንሹ ሰላምን ዕረፍት ለዘላለም የሚኖር መስሎት በቃኝ ብሎ ሄዷል። ጸጋም ያልቃል። ጸጋው ቀጣይ የሚሆነው ባለጸጋውን ጌታ ስንይዝ ብቻ ነው። የጠፋው ልጅ እኛው ነን።

   📝 ሉቃስ ትረካውን በድንቅ ይጀምራል።

" እንዲህም አለ፦ አንድ ሰው ሁለት ልጆች ነበሩት። ከእነርሱም ታናሹ አባቱን፦ አባቴ ሆይ፥ ከገንዘብህ የሚደርሰኝን ክፍል ስጠኝ አለው። ገንዘቡንም አካፈላቸው። ከጥቂት ቀንም በኋላ ታናሹ ልጅ ገንዘቡን ሁሉ ሰብስቦ ወደ ሩቅ አገር ሄደ፥ ከዚያም እያባከነ ገንዘቡን በተነ"
በማለት ይተርካል(ሉቃ.15:11-13)።

     💌ሁለት ልጆች ያሉት አባት እግዚአብሔር ነው። የመጀመሪያው ልጅ አይሁዳውያንን ይወክላል። የመጀመሪያዎቹ እድምተኞች፣ ደግሞም በኩር ፍሬ ናቸው። ሁለተኛው ልጅ ከአይሁድ ውጪ ያሉትን አማንያንን ያመለክታል። ሁለቱም ልጆች የየራሳቸው ጠባይ ቢኖራቸውም ለአባታቸው ግን አልተመቹትም። እንደ እርሱ አልሆኑም ታናሹ ልጅ አባቱን ሳይሆን ንብረቱን የሚወድ ነበር፣ ከዚያም ኮብልሎ የባከነ ነው። ታላቁ ደግሞ ንብረቱን ተካፍሏል፣ ግን በቤት ውስጥ ይኖራል። የቤት ውስጥ አቁሳይ ነው። ኋላ ወንድሙ ሲመለስም ደስተኛ አልነበረም። የወንድም ፍቅር የለውም። ግን በቤት የሚኖር ደግሞም ትጉህ ሠራተኛ ነው።  ፍቅር የሌለው ትጉህ ነው። የአባቱ ቤት ለእርሱ መሥሪያ ቤት ነው። ታናሹ ልጅ የተካፈለው ገንዘብ ምንድነው? ሰላም፣ ደስታ፣ ጸጋ፣ በረከት ነው። ከአባቱ ጋር ይኖር የነበረው ለእነዚህ ጉዳዮች ነው። እነርሱንም ተቀብሎ ቢኖር አባቱ አይከፋውም ነበር። ይባስ ብሎ ነጥቆት ሄደ።

       📖ሉቃስ ትረካውን ቀጠለ፦
" ሁሉንም ከከሰረ በኋላ በዚያች አገር ጽኑ ራብ ሆነ፥ እርሱም ይጨነቅ ጀመር። ሄዶም ከዚያች አገር ሰዎች ከአንዱ ጋር ተዳበለ፥ እርሱም እሪያ ሊያሰማራ ወደ ሜዳ ሰደደው። እሪያዎችም ከሚበሉት አሰር ሊጠግብ ይመኝ ነበር፥ የሚሰጠውም አልነበረም።"(ሉቃ.15:14-16)

        📝ያ የጠፋው ልጅ የከሰረው አንዳንድ ነገሮችን አይደለም ሁሉንም ነገሮች ነው። ከእግዚአብሔር ስንርቅ ሁሉም ነገር ይከዳናል። ያለን ሁሉ የሚኖረን ከእግዚአብሔር ጋር ሳለን ብቻ ነው። የጠፋው ልጅ ቤተኛ ከሚሆንበት ኑሮ ወጥቶ ተዳበለ። የኮበለለ ምዕመን ኑሮው የደባል ነው። ደባል፦ ነጻነቱ የተገደበ፣ የማይፈልገውን ለማየት የተዳረገ፣ ጸጥታ የሌለው፣ ስድብ የሚጠግብ፣ የማይመለከተውን በግድ የሚያስተናግድ ነው። የጠፋው ልጅ ከራቡ የተነሣ የእርያ እረኛ ሆነ። እርያ ለአይሁዳውያን ርኩስ ነው። በረከሰ ተግባር ላይ ተሰማራ። ከእርያ ምግብም ለመጥገብ ይመኝ ነበር፣ ግን አልሆነለትም። የእርያ ምግብ እርያን እንጂ ሰውን አያጠግብም። የእሪያው ምግብ መጠጥ፣ ሲስ....ነው። መጠጥ፣ ዘፈን....ለዓለማውያን ይደልል ይሆናል፣ እውነትን ቀምሶ ለነበረ ግን በፍጹም አይሆንም። ማደንዘዣው እርሱ ላይ አልሰራ አለ። ዓለማውያን ኃጢያት ሠርተው የሚያገኙትን ጊዜያዊ ሣቅ ፣ ጊዜያዊ መዘናጋት እንኳ ማግኘት አቃተው። አካሉ ኃጢያት ስፍራ ልቡ ግን አባቱ ቤት ሆነ። እየጠጣ ያለቅሳል፣ ሱስ ላይ ተቀምጦ ዝማሬው፣ ቅዳሴው ይሰማዋል።

  " ወደ ልቡም ተመልሶ እንዲህ አለ፦ እንጀራ የሚተርፋቸው የአባቴ ሞያተኞች ስንት ናቸው? እኔ ግን ከዚህ በራብ እጠፋለሁ። ተነሥቼም ወደ አባቴ እሄዳለሁና፦ አባቴ ሆይ፥ በሰማይና በፊትህ በደልሁ፥ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም፤ ከሞያተኞችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ።" (ሉቃ.15:17-19)።

    💌ወደ ወደ ልቡ ሲመለስ የአባቱ ቤትና ክብሩ ታየው። እንኳን ልጅ ባሪያም የሚጠግብበት በረከት ታወሰው። የንስሐ መንስ ገዛው።  አባቱ ተራ አባት አይደለም። ሰማይን የሚገዛ ነው። ደግሞም ያየዋል። "በፊትህ በደልሁ" እለዋለሁ አለ። በእግዚአብሔር ቤት ትንሹን ድርሻ ናፈቀ። ትንሹም ትልቅ ነውና።

   📖ሉቃስም ቀጠለ፦

"ተነሥቶም ወደ አባቱ መጣ። እርሱም ገና ሩቅ ሳለ አባቱ አየውና አዘነለት፥ ሮጦም አንገቱን አቀፈውና ሳመው። ልጁም፦ አባቴ ሆይ፥ በሰማይና በፊትህ በደልሁ፥ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም አለው። አባቱ ግን ባሪያዎቹን አለ፦ ፈጥናችሁ ከሁሉ የተሻለ ልብስ አምጡና አልብሱት፥ ለእጁ ቀለበት ለእግሩም ጫማ ስጡ፤ የሰባውን ፊሪዳ አምጥታችሁ እረዱት፥ እንብላም ደስም ይበለን፤ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም። ደስም ይላቸው ጀመር።" (ሉቃ.15፥20-24)

      📝አባቱ ልጁን የተለየው በግድ ነው። ልቡ አላረፈም። ማዶ ማዶ እያየ ይጠብቀው ነበር። እስኪደርስ አላስቻለውም፣ መንገድ አጋምሶ ተቀበለው። አልተጸየፈውም፣ ከነ ቆሻሻው አቅፎ ሳመው። አልተበሳጨበትም አዘነለት። ልብሱን ቀየረለት፣ ታሪኩን ለወጠለት። ቀለበት አደረገለት፣ ቃልኪዳኑን አደሰለት። ፍሪዳ ሠዋለት አምልኮ ተጀመረ። ታላቅም ደስታ ሆነ።

     📖ሞት በሕይወት ፣ መጥፋት በመገኘት የሚተካው በመመለስ ነው። የሚፈርድብን ሳይሆን የሚምረን አባት ነው። ዛሬም ማዶ ማዶ እያየ ይጠብቀናል። ሉቃስ የጌታችንን ንግግር መጻፍ ይቀጥላል። በጠፋው ልጅ መገኘት ትክለኛ ወይም ኗሪ ነኝ የሚለው ልጅ ተበሳጨ። አባቱ ግን መልስ ሰጠ(ሉቃ.15፥25-32)።

     💌ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት የአባትና የልጅ ግንኙነት ነው። እርሱም አፍቃሪ አባታችን ነው። ስለ እኛ የሚቆጭ፣ በርህራሄ የሚቀበለን፣ ልብሳችንን የሚለውጥልን፣ ቃልኪዳንን ሊያድስልንና እንዴት መኖር እንዳለብን የሚመክረን አባት እርሱ ነው! እግዚአብሔር ዛሬም የፍቅር እጆቹን ዘርግቶ "ልጄ ሆይ" ና ይላል!
     መመለስ ይሁንልን!!!