Friday, April 5, 2019

❖የአለማወቅ ጥፋት፦

አለማወቅ የደገሰው ሞት

እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን አለማወቅ የጥፋት ሁሉ ምንጭ እንደሆነ ተናግሯል፡፡ "ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል፤ አንተም እውቀትን ጠልተሃልና እኔ ካህን እንዳትሆነኝ እጠላሃለሁ፤ የአምላክህንም ሕግ ረስተሃልና እኔ ደግሞ ልጆችህን እረሳለሁ" ሆሴዕ 4:6 ሰው የሳተው ትልቅ እውቅት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡
በአዲስ ኪዳን ደግሞ ጳውሎስ እግዚአብሔርን ለማወቅ አለመፈለግ ወደ ሞት እንደሚያደርስ ተናግሯል፡፡ “እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ዓመፃ ሁሉ፥ ግፍ፥ መመኘት፥ ክፋት ሞላባቸው፤ ቅናትን፥ ነፍስ መግደልን፥ ክርክርን፥ ተንኰልን፥ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፤ የሚያሾከሹኩ፥ ሐሜተኞች፥ አምላክን የሚጠሉ፥ የሚያንገላቱ፥ ትዕቢተኞች፥ ትምክህተኞች፥ ክፋትን የሚፈላለጉ፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያስተውሉ፥ ውል የሚያፈርሱ፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ምሕረት ያጡ ናቸው፤ እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም።” ሮሜ 1፡28-32 እነዚህ የተዘረዘሩት 21 ነውሮች እግዚአብሔርን ለማወቅ ባለመውደድ ለማይረባ አእምሮ በተሰጡ ሰዎች የተሠሩ ናቸው፡፡ወገኖቼ እውቀትን መጥላት የለብንም፡፡ እውቀት ካጣን እንጠፋለን፡፡ በተለይ እግዚአብሔርን ማወቅ አስፈላጊ ነው፡፡ ውስጣችን  እግዚአብሔርን ይጠማ፤ ፊቱን እንፈልግ፤ ሳንፈልገው የፈለገንን አምላክ እንፈልገው፡፡

ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

Thursday, April 4, 2019

❖ገብርሄር፦

ጸጋን ለሰጠን መታመን፦

ገብርኄር ማለት መልካም ፥ ቸር ፥ ለጋስ ፥ ታማኝ አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ መታመንን፥ ታማኝ አገልጋይነትን፥ የመታመንን ዋጋ፥ የአለመታመንን ቅጣት ያመለከተበት ምሳሌያዊ ታሪክ እንደሚከተለው ቀርቧል በማስተዋል እናጥናው፦

  "ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደ ሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና፤ለእያንዳንዱ እንደ ዓቅሙ፥ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ወዲያው ሄደ።አምስት መክሊትም የተቀበለው ሄዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ፤ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ። አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቈፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ።ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው።አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ። ጌታ ሆይ፥ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት አለ።ጌታውም። መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።ሁለት መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት አለ።ጌታውም። መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፥ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ።ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው። አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ፥ ካልዘራሁባት እንዳጭድ ካልበተንሁባትም እንድሰበስብ ታውቃለህን? ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር፥.....እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር።ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት አሥር መክሊትም ላለው ስጡት፤ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል። የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።"ማቴ 25:14-30

ይህ ታሪክ ምን አስተማረን? ራሳችንን አሳየን? ምንድነው የተቀበልነው ? ምን ያህል አተረፍንበት ? የጸጋ ስጦታችንን እናውቃለን? ድርሻችንን ተወጥተናል ? የኛ መክሊት ለሌሎች ምን ጠቀመ? በሌሎችስ መክሊት ምን ተጠቀምን ? በመክሊታችን ሰጭውን አከበርንበት ? እግዚአብሔር እንደ አቅማችን ማትረፊያ መክሊት ሰጥቶናል፡፡ የሰጠንን መቅበር አንችልም፡፡ በተሾምንበት ነገር ታማኝ መሆን አለብን፡፡ የተቀበልን ነን የተቀበለ ደግሞ ይሰጣል የተቀበለ ሰጪውን ያከብራል የተቀበለ እንዳልተቀበለ አይኩራራም፡፡የተሰጠንን ሳንሰጥ ከሄድን እንጠየቃለን፡፡ በተሰጠን መክሊት ራሳችንን እና ሌሎችን ለእግዚአብሔር ክብር ማትረፍ አለብን፡፡ ድርሻችንን መወጣት አለብን፡፡ በአቅማችን ከሠራን በተሰጠን ከታመንን እግዚአብሔር በዚህ ደስ ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር አለመታመንን ይጠላል፡፡በተሰጠን ታምነን ማትረፍ አለብን፡፡

ከምድር የጠፋ ትልቁ ሀብት ታማኝነት ነው፡፡ሰው እንኳን ሰውን ራሱን የሚያታልልበት፥ ለራሱ እንኳ መታመን ያልቻለበት ሁኔታ አለ፡፡እግዚአብሔር ሳይሰጥ አልጠየቀም። ለጋስነቱን እያመሰገንን በተሰጠን ልክ ታምነን መሥራት አለብን፡፡በተሰጠን በተሾምንበት በጥቂቱ ከታመንን እግዚአብሔር በብዙ ይሾመናል፡፡ ገብርኄር የአገልግሎቱ ባለቤት እግዚአብሔር ከአገልጋዮች የሰጠውን አደራ ሊቀበል እንደሚመጣም ያሳያል፡፡ አገልጋይ ጌታ ወይም አሠሪ አለው፡፡ አሠሪው ሁሉንም በአቅሙ ልክ ጸጋ ሰጥቶ ነው ያሠማራው፡፡እንደሰጠን መጠን በኋላ ዋጋ ይከፍላል፡፡ ስለዚህ አገልጋይ አትራፊ መሆን አለበት፡፡ በተለይ መንጋውን ማትረፍ አለበት፡፡ታማኝ አገልጋይ ወይም እረኛ ለበጎቹ ሕይወት ዋጋ ይከፍላል፡፡ የተበተነውን ይሰበስባል፤የወደቀውን ያነሳል ያዘነውን ያጽናናል፥ የተሰበረውን ይጠግናል፤ የራሱን ጥቅም አይፈልግም፤ በጎችን ለጥቅሙ አይሰዋም፤ ግን እረኝነት እንዲህ እየሆነ አይደለም።

እረኞች ሆይ ሕዝቡ ባለቤት አለው፥ በአግባቡ ምሩ። የሾማችሁ አንድ ቀን ወደ እናንተ ይመጣል፥ ያኔ ምን ልትመልሱ እንዳላችሁ አስቡ። ቃሉ እንደሚል "ጮማውን ትበላላችሁ ጠጕሩንም ትለብሳላችሁ፥ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፤ በጎቹን ግን አታሰማሩም። የደከመውን አላጸናችሁትም የታመመውንም አላከማችሁትም የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም የባዘነውንም አልመለሳችሁትም የጠፋውንም አልፈለጋችሁትም በኃይልና በጭቈናም ገዛችኋቸው።" የሚለው እየተፈፀመ ነው፡፡ ሕዝ 34:3።

እግዚአብሔር የጠፉበትን ከእርሱ ርቀው እንዲሞቱ የተፈረደባቸውን ነፍሳት ደም ከእረኞች እጅ ይፈልጋል፡፡ ታምኖ የሚሠራ አገልጋይ ከክብር ጋር ከሽልማት ጋር ነው ወደ ጌታ ደስታ የሚገባው፡፡  ታምኖ የማይሰራ ከመንጋው ጮማውን እየበላ፣ ጠጉሩን እየለበሰ፣ አጥንቱን እየቀለጣጠመ ራሱን የሚያሰማራ እረኝነቱ( ፀጋው) ይወሰድበታል። ሌላ ታምኖ የሚሰራ ይዘጋጃል ዘካ 11:15 ። ታምኖ የጠፋውን በመፈለገ ማዳን ፣ የዳነውንም መቀለብ የበጎ ታማኝ አገልጋይ መገለጫ ነው።
     ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

Thursday, March 21, 2019

❖መጻጉዕ

 መጻጉዕ፦
( ፈዋሻችን ኢየሱስ ክርስቶስ)

መጻጉዕ የዐቢይ ጾም 4ኛ ሳምንት ነው፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተገለጠበት ዘመን የፈወሳቸውን ሕሙማን ማስረጃ በማድረግ ከፈወሳቸው ሕሙማን፥ ካነጻቸው ለምጻሞች፥ ቀን ካወጣላቸው ሰዎች፥ ከሰው ከቀላቀላቸው ግፉአን፥ ጋር በመቆም ቤዛችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የምናመሰግንበት ሳምንት ነው፡፡ ለአምልኮ የተመረጠው የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 5 ነው፡፡በወንጌሉ እንደተጻፈው ባለታሪኩ ሰውነቱ የሰለለ፤ ወደ መጠመቂያይቱ ተጋፍቶ የሚያስገባው ሰው የሌለው፤ ለብዙ ዘመናት ፈውሱን በተስፋ ሲጠብቅ የነበረ ሰው ነው፡፡ፈዋሹ ጌታ ኢየሱስ "ልትድን ትወዳለህን ? " ብሎ ጠየቀው፡፡እርሱም "ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል ብሎ መለሰለት።" ኢየሱስ ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለው።ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ። ዮሐ 5:7-12:: ክብር ለፈዋሹ!!

➊ ፈዋሽ እግዚአብሔር ነው፡፡ ሰዎች በተለያዩ ደዌዎች ሊያዙ ይችላሉ፤ ፈዋሹ ግን ሁሉን በሁሉ የሚሠራ እግዚአብሔር ነው፡፡ ፈዋሹ በነፃ የሚፈውስ፥ ጤናን የሚመልስ አምላክ ነው"እኔ ጤናህን እመልስልሃለሁ ቁስልህንም እፈውሳለሁ" ኤር 30:17፡፡ በአንድም በሌላም በብዙም በጥቂትም ያድናል፡፡እኔ ፈዋሽህ ነኝ ያለ ቁስላችንን የማይፀየፍ አምላክ ነው፡፡ፈዋሹን የጠበቀ አንድ ቀን አልጋውን ተሸክሞ መሄዱ አይቀርም፡፡በዘመናችን ከእግር ጥፍራ እስከ ራስ ፀጉር ደዌ በሁሉ ሆኗል ፣ራስ ሁሉ ለህመም ልብም ለድካም ሆኗል ስሙን እየቀያየረ ደዌ ይመጣል፤ የስጋት ምንጭም ሆኗል፤ መፍትሔው ፈዋሹ ነው። ኢየሱስ ዛሬም በስሙ፣ በቃሉ እና በመንፈሱ ይፈውሳል። "እኔ ፈዋሽህ እግዚአብሔር ነኝ" ዘጸ 15:26

➋ድኅነት የሰውን ፈቃድ ይፈልጋል፡፡ ፈውስ፣ ስጦታ እና ድኅነት የእግዚአብሔር የቸርነት ብልጽግና ፍሬዎች ናቸው፡፡እግዚአብሔር ለጥቅማችን የሆነን ነገር እንኳ አስፈቅዶ ያደርጋል፡፡ልትድን ትወዳለህ ብሎ ጠይቆ ነውና ያዳነው፡፡ጌታ ሲፈውስ ያለ ፈቃድ የፈወሳቸው በአጋንንት እስራት የተያዙትን ብቻ ነው፤ ይህን ያደረገው አእምሯቸው በሌላ አዛዥ ስለተያዘ ተናጋሪው ተከራዩ እንጂ ሕመምተኛው ስላልሆነ ነው፡፡እኛም የተያዝንበት ሕመም፥ ፈውስ ፍለጋ የወጣንበት ቁስል ይኖረናል። ፈዋሹ እግዚአብሔር ሊፈውሰን ፈቃዱ ነው፤ ምሕረቱ ግን ለሮጠ ወይም ለቀደመ ሳይሆን በእምነት ፈቃድ ለተከተለ ነው፡፡"እንግዲህ ምሕረት ለወደደ ወይም ለሮጠ አይደለም፥ ከሚምር ከእግዚአብሔር ነው እንጂ።"ሮሜ 9:16። በደዌ ሥጋ ወነፍስ ለተያዝን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ፈውስ ይሁን!!!

❖ምኩራብ


 ምኩራብ፦
~የቤትህ ቅናት...!
    (መዝ.68፥9)

የዐብይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት ምኩራብ ይባላል፡፡ይህ ሳምንት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተመቅደሱን የጎበኘበት ነው፡፡ታሪኩ በማቴዎስ እና በዮሐንስ ወንጌል ተመዝግቧል፡፡ ጌታ፣ አምላክ፣ ሕይወት እና መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ መቅደስ ሲገባ መቅደሱ ከታሰበለት ዓላማ ውጭ የንግድ ቤት ሆኖ አገኘ፡፡ እጅግ አዘነ፥ ጅራፍ አበጅቶ እንስሳትን ከመቅደሱ አወጣቸው፡፡ሰዎችን ገሰጸ፡፡ "ርግብ ሻጪዎችንም። ይህን ከዚህ ውሰዱ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት አላቸው።" (ዮሐ 2፥16)  ደቀመዛሙርቱ "የቤትህ ቅናት በላኝ" የሚለውን አሰቡ፡፡
በዚህ ታሪክ ውስጥ የምናያቸው ዋና ዋና ነጥቦች፦

1- መቅደሱ የጸሎት ቤት ነው፦
በጊዜው የነበረው መቅደስ የጸሎት ቤት ነበረ። ሰዎቹ ግን የገበያ አዳራሽ አድርገውት ነበረ። ወዳጆቼ ዛሬም ቢሆን በስሙ የተሰየሙ የጸሎት ቤቶች ለታሰበላቸው አላማ መዋል አለባቸው። ቤቱ መንፈሳዊ ነው ሥጋዊነት ሊነግስበት አይገባም፡፡ ቤቱ የዕረፍት ቤት ነው ሁከት መፍጠር ተገቢ አይደለም፡፡ ቤቱ የግለሰቦች ቤት አይደለም፤ ስለዚህ ማንም ማንንም የመንካት መብት የለውም፡፡ ቤቱ የሽፍቶች ዋሻ አይደለም፡፡ ቤቱ በንስሐ ለሚመለሱ እንጂ በዐመፅ ለሚቀጥሉት መደበቂያ አይደለም፡፡

 2- ሕያው እና ቅዱስ መቅደስ እንሁን፦
ሰውነታችን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ነው፤ (1ቆሮ 6፥19):: ስለዚህ ሰውነታችን የቅድስና መኖሪያ ብቻ ይሁን፡፡አመፅ፣ ግፍ፣ የክፋት አሳብ በውስጣችን መኖር የለበትም፡፡በእግዚአብሔር ላይ ያመጹ አጋንንት በኛ ልብ ሸፍተው ሊደበቁ አይገባም፡፡እኛ የልዑል ማደሪያ ብቻ ለመሆን መንፈሳዊ ቤት ለመሆን እንሰራ፡፡ሰውነታችን በመልካምነት አጊጦ በክርስቶስ ደም ተቀድሶ የአባቱ ቤት ይሁን፡፡ቤቱን ለታሰበለት መንፈሳዊ ዓላማ መጠቀም አለብን፡፡እግዚአብሔር ያያል፥ በቤቱ የሚሆነውን እና የምንሆነውን ያያል፡፡ "ይህስ ስሜ የተጠራበት ቤት በዓይናችሁ የሌቦች ዋሻ ሆኖአልን? እነሆ፥ እኔ አይቻለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።" (ኤርምያስ 7፥11)። ስለዚህ ራሳችንን ቅዱስ፣ ሕያው እና እግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መስዋዕት አድርገን እናቅርብ።

3- ለቤቱ እንቅና፦
ቤቱ የመንፈስ ቅዱስ ቤት ነው፡፡በዚህ ዘመን ዓይናችን እያየ ብዙ የሥላሴ ቤቶች እየፈረሱ ነው፡፡ትውልድ በሱስ ሲፈርስ፥ ተስፋ ቢስ ሆኖ ሲንከራተት፥ የአጋንንት ማደሪያ ሆኖ ሲሰቃይ፥ የትውልድ ዝንባሌ ወደ አመፃ ሲሆን እያየን ተደላድለን መቀመጣችን ለቤቱ እንደማንቀና ያሳያል፡፡ወልድ የተወለደው ቀንቶልን ነው፤ መዳናችን የተፈፀመው በእግዚብሔር ቅናት ነው፡፡ (ኢሳ. 9፥7) ኤልያስ ለእግዚአብሔር ክብር ቀንቶአል፡፡"ለሠራዊት አምላክ ለእግዚአብሔር እጅግ ቀንቻለሁ፤ የእስራኤል ልጆች ቃል ኪዳንህን ትተዋልና፥ መሠዊያዎችህንም አፍርሰዋልና፥ ነቢያትህንም በሰይፍ ገድለዋልና፤ እኔም ብቻዬን ቀርቻለሁ፤ ነፍሴንም ሊወስዱአት ይሻሉ አለ።" (1ነገሥት 19፥10)። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጅራፍ ያነሳው ለቤቱ ቀንቶ ነው፡፡በልባችን መሽገው የነበሩትን አጋንንት በደሙ ኃይል ጠራርጎ አስወጣ፥ ለአባቱ ቅዱስና ሕያው ቤት አድርጎ ሠራን፡፡እኛ በደም የተሠራን የሠው እጅ ያልሠራን የልዑል ማደሪያ ነን፡፡የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ ቤት ነን፡፡ክርስቶስ ለሞተለት የደም ዋጋ ለተከፈለለት እንቅና፡፡

4- ቅጣት ከቤቱ እንደሚጀምር እናስተውል፦ እግዚአብሔር ፈራጅ ነው፤ ከብዙ ትዕግስት በኋላ ጅራፍ ያነሳል። ያኔ ቅጣቱ የሚጀምረው ከመቅደሱ ነው ሕዝብ ጋር ከመሄዱ በፊት ባለ አደራዎቹ ከሆኑት ከአገልጋዮቹ ይጀምራል፡፡መቼ ነው የምንመለሰው ? መቼ ነው በቤቱ ተገቢ ነገር ብቻ የምናደርገው ? ንግዱ ላይ በርትተን ቢመጣስ ? ነፍሳትን እየበተኑ ገንዘብ መሰብሰብ እስከ መቼ ?
ቅጣቱ ከእኛ ይጀምራል፡፡                                       
     ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!!
===●===●===●===

Wednesday, August 22, 2018

❖በውድዋ ላይ ተደግፋ ከምድረ በዳ የምትወጣ (የምታርግ) ይህች ማን ናት?




በውድዋ ላይ ተደግፋ ከምድረ በዳ የምትወጣ (የምታርግ) ይህች ማን ናት?”
                             (መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 85)
                            **የድንግል ማርያም ትንሣኤና ዕርገት**

በክርስትና ስም ከሚጠሩ ቤተ እምነቶች በተለየ መልኩ፥ቀጥተኛ መንገድየሚል ትርጉም ያለው የኦርቶዶክስ እምነትን የሚከተሉ አብያተ ክርስቲያን ለተቀደሰው ሐዋርያዊ ትውፊት (Holy Tradition) ትልቅ ቦታ አላቸው። ቅዱስ ትውፊት የምንለው ከቅዱሳን ሐዋርያት አባቶቻችን ዘመን ጀምሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲሸጋገር የመጣውን አስተምህሮ እና ሥርዓተ አምልኮ ሲሆን፥ መጽሐፍ ቅዱስም እኛ ዘመን የደረሰው በዚሁ የተቀደሰ የትውፊት ሰንሰለት ነው። ለዚህም ነው ኦርቶዶክሳውያን አበው፦መጽሐፍ ቅዱስ፥ በተቀደሰው የትውፊት ዛፍ ላይ የበቀለ መልካም ፍሬ ነውየሚሉት።
የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን፥ በምድረ ፍልስጥኤም 5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጨረሻ አካባቢ የወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያምን በዓለ ዕረፍት ወፍልሰት ማክበር እንደጀመረች የሚጠቁሙ ታሪካዊ መረጃዎች አሉ። በዚሁ ዘመን “The Dormition and the Assumption of the body of St. Mary into Heaven” በሚል ርእስ ዙሪያ የሚያትቱ ጽሑፎች በተለያዩ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ይጻፉ እንደነበር በቅርቡ የተደረጉ ጥናቶች ያመለክታሉ።
ከነዚህ ጥናቶች መካከል ዓለም አቀፋዊ እውቅናን ያተረፈው የሚከተለው መጽሐፍ ነው፦ Stephen Shoemaker, Ancient Traditions of the Virgin Mary’s Dormition and Assumption, Oxford University Press, 2006. በፍልስጥኤም (Palestine) የተጀመረውበዓለ ዕረፍታ ወፍልሰታ ለማርያምቀስ በቀስ ወደ ምዕራቡ ዓለም ደርሶ፥ 8ኛውና 9ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዓለም አቀፋዊ በዓል ለመሆን ችሏል። ይህን በዓል ኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያን August 15 ቀን ሲያከብሩት፥ ጥንታዊውን Julian Calendar የምትከተለው ቤተ ክርስቲያናችን ደግሞ ነሐሴ 16 (August 22) ቀን በታላቅ ድምቀት ታከብረዋለች።
በውድዋ ላይ ተደግፋ ከምድረ በዳ የምትወጣ ይህች ማን ናት?” የሚለው የንጉሥ ሰሎሞን ዝማሬ፥ ሕይወቷን በሙሉ አምላኳን ያከበረች ነፍስ ከሥጋዋ ተለይታ ወደ፡ምትወደው ጌታ ስትሄድ የሚጠቀስ ጥቅስ ነው። ከዚህ በተሻለ መልኩ ግን፥ እመቤታችን ድንግል ማርያም በልጇ ኃይል ከሞት ተነሥታ፥ ንጽሕትና ቅድስት የሆነችውን ነፍሷን ውድ ልጇ በክብር ተቀብሎ ወደ መንግሥቱ ያሳረገበትን በዓል ለመዘከር ልንጠቀምበት እንችላለን። እንዲያውም የግእዙ ንባብ፦ መኑ ይእቲ ዛቲ እንተ ተዐርግ እም ገዳም አንተ ትትመረጐዝ በወልድ እኁሃ? - በውድዋ ላይ ተደግፋ ከምድረ በዳ የምታርግ ይህች ማን ናት?” ያላትን፥ ሠናይት ከመ ወርኅ፥ ወብርህት ከመ ፀሐይ - እንደ ጨረቃ የተዋበች፥ እንደ ፀሐይም የምታበራበማለት ስለሚገልጻት፥ በፈቃድ ከሚሰራው የግል ኃጢአት ነጻ ለሆነችው ለቅድስቲቷ የእመቤታችን ነፍስ ዕርገት በእጅጉ የሚስማማ አገላለጽ ነው። ይህን መጽሐፍ ቅዱሳዊ አሳብ በሥነ-ሥዕል (iconography) ለማመልከት፥ ኦርቶዶክሳዊ ሥዕል (icon) ሐዋርያት የእመቤታችንን ሥጋ ለመገነዝ አንደተሰበሰቡና ጌታ በሕፃን ልጅ አምሳል በነጭ መጎናጸፊያ የተጠቀለለችውን የብፅዕትና ቅድስት እናቱን ነፍስ ታቅፎ ያሳያል። ጌታን በሕፃንነቱ እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ታቅፈው እንደነበር፥ እርሱ ደግሞ በተራው በዕረፍቷ ቀን የእናቱን ንጽሕት ነፍስ ታቅፎ ወደ መንግሥቱ ዘላለማዊ ክብር አገባት።
በሞቱ ሞትን ድል የነሣልን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፥ ከሞት በኋላ የሚጠብቀን ትንሣኤ በኵር እንደሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጽፎልናል (1 ቆሮ1520) ይኸው ሐዋርያ ስለ ሙታን ትንሣኤ ሲጽፍ ሥጋዊ አካላችን ወደ አፈርነቱ ከተመለሰ በኋላ (በመበስበስ ከተዘራ በኋላ) መንፈሳዊ አካል ሆኖ በክብር አንደሚነሳ አስተምሮናል (1 ቆሮ 15 42-50) መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ለፍርድ ሲመጣ፥በጌታ የሚሞቱ ሙታን ብፁዓን ናቸውእንደተባለ (ራእይ 1413) በምድራዊ ኑሮአቸው ክርስቶስን ለብሰው የኖሩ የእግዚአብሔር ልጆች የክብር ትንሣኤ ይነሳሉ። ለዚህም ነው ሐዋርያው፦ክቡር ሥጋውን እንዲመስል የተዋረደውን ሥጋችንን ይለውጣል” (ፊልጵ 321) ሲል ስለሚጠብቀን ዘላለማዊ ክብር የነገረን።
እንግዲህ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን፦ወላዲተ አምላክ ማርያም ሞትን ድል ባደረገው በልጇ ኃይል ከሞት ተነስታ ወደ ልጇ መንግሥት አርጋለችብላ ስታስተምረን፥ የአምላካችን ልጆች የሆንን ሁላችን በእግዚአብሔር መንግሥት የሚጠብቀንን ክብር እመቤታችን ቀድማ አግኝታለች ማለቷ ነው። ጌታ በትንሣኤው በኵር እነደሆነን፥ ቅድስትና ብፅዕት እናቱ ደግሞ ወደ ሰማያዊው መንግሥት በመግባት ቀዳሚት (በኵር) ሆነችን። ንጉሡ ጌታችን ኢየሱስ ከመንግሥቱ የተለየበት ጊዜ ፈጽሞ እንደሌለ እናውቃለን፤ መንግሥቱ ያለው ንጉሡ ባለበት ቦታ ነውና። ሁላችን ተስፋ የምናደርገውናወደ ጌታህ ደስታ ግባ” (ማቴ 2522) የሚለው፥ በእርሱ ሕያዋን ሁነን በመንግሥቱ ለዘላለም የመኖራችን እውነታ (eschatological fulfillment) ከሁላችንም ቀድሞ ለቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ተደረገ። ከመለኮት ባህርይ ተካፋይ የሆንበትን (2 ጴጥ 14) ምስጢር (theosis - ሱታፌ አምላክ) ከእግዚአብሔር በተሰጣት የተለየ ጸጋ በንጽሕና እና በቅድስና አጊጣ በሕይወቷ እውን ስላደረገችና ከቅዱሳን መካከል በንጽሕና የሚስተካከላት ስለሌለ፥ እመቤታችን ከቅዱሳኑ ሁሉ ቀድማ ወደ መንግሥተ እግዚአብሔር ገባች ቢባል ጥያቄ ሊፈጥርብን አይገባም። ደግሞም አምላክን በድንግልና ወልዳ ላሳገደች እመቤት የሚገባት የክብር ሰማያዊ ፍጻሜ ከዚህ ውጪ ሊሆን አይችልም።
እግዚአብሔር ወልድ ከእመቤታችን የነሳው ሥጋ የእኛ ሥጋ እነደሆነ ግልጽ ነው፤ 318 የኒቂያ ጉባኤ አባቶች ስም የተደረሰው የቤተ ክርስቲያናችን ቅዳሴ፦ተዘከር ሥጋ እንተ ነሣእከ እምቅድስት ድንግል እንቲአነ ሥጋ አኮ እምሰማያት ዘአውረድከ - ከቅድስት ድንግል የነሣኸው ሥጋ የእኛ ሥጋ እነደሆነ፥ ከሰማይ ያወረድኸው እንዳይደለ አስብእንዲል (. 121) የመልአኩን ብስራትይኩነኒ በከመ ትቤለኒብላ ከተቀበለችበት ቅጽበት ጀምሮ እግዚአብሔር አብ በልጁ በኩል ያደርግ ዘንድ ላሰበው የማዳን ሥራ ድንግል ማርያምን መሣሪያ አድርጓታል። ልዑል ማደሪያውን ቀድሶ፥ቅድስተ ቅዱሳን - Holy of Holies” የተሰኘች የአንድ ልጁ ማደሪያ ትሆን ዘንድ መረጣት። ስለዚህ የድንግል ማርያም ትንሣኤና ዕርገት በዋነኝነት የሚያመለክተው፥ እነ ቅዱስ ኤፍሬም፦አንቲ ውእቱ ደብተራ እንተ ተሰመይኪ ቅድስተ ቅዱሳን . . . መቅደስ ዘይኬልሉኪ ኪሩቤልብለው ያወደሷት የጌታ ንጽሕት መቅደስ በመንግሥቱ መክበሯን ነው። ይህ የመንግሥቱ ክብር (glorification) ደግሞ የእኛም ክብር ስለሆነ በዚህ የተቀደሰ ትውፊታው አስተምህሮ ደስ ሊለን እንጂ፥ በጭራሽ ሊከፋን አይገባም።
አባቶቻችን፥ መሐሪው ጌታ እኛን የወደደበትን ዘላለማዊ ፍቅርንና ለእኛ ያደረገውን የማዳን ሥራ በመጽሐፈ ቅዳሴ፦ እንተ አፍቀርካ ለዛቲ ዘመድነ - ይህችን ባሕርያችንን የወደድሃት ሆይበማለት አድንቀዋል። እኛም ለእመቤታችን የተደረገው (ለአምላክ እናትነት መመረጧ፥ ዘላለማዊ ድንግልናዋ፥ ከፍጡራን ማንም የማይስተካከለው ቅድስናዋ፥ ከሞት ተነሥታ ማረጓ) ለድኅነታችን (ለመዳናችን) የተደረገና የእኛን ሰብዓዊ ባሕርይ ልዩ ክብር (glory) የሚያንጸባርቅ ስለሆነ በዚህ ሁሉ ደስ ይበለን፥ ሐሴትም እናድርግ። በሔዋን የተዋረደው ሰብዓዊ ባሕርያችን በዳግሚት ሔዋን (በድንግል ማርያም) ስለከበረ እንደ አባቶቻችን ትምህርት እመቤታችንን፦ትምክሕተ ኵልነ/ ትምክሕተ ዘመድነእንበላት። ይህን እውነት ሲያመሰጥር፥ በሶርያዊው ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ስም የሚጠራው የኢትዮጵያውያን አባቶቻችን አኰቴተ ቊርባን፦ወካዕበ ተማኅፀነ በማርያም እምከ እንተ ይእቲ እግዝእትነ ወትምክሕተ ዘመድነ በወሊዶተ ዚአከ - ዳግመኛም በእናትህ በማርያም ተማፅነናል፤ ይህችውም አንተን በመውለድ እመቤታችንና የባሕርያችን መመኪያ ናትይላል (. 99)
በመጨረሻም፥ ሄኖክ አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር ስላደረገ አምላኩ እንደወሰደው (ዘፍ. 524) ለአምልኮተ እግዚአብሔር ቀናዒ የነበረው ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሰረገላና በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ አንደተነጠቀ (2 ነገ. 2 11) ከመጽሐፍ ቅዱስ ያነበበ ሰው፥ የወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም ወደ መንግሥተ ሰማያት መወሰድ ጥያቄ ሊፈጥርበት አይገባም።እነሆ፥ ሰማይ ከሰማያትም በላይ ያለው ሰማይ ይይዝህ ዘንድ አይችልም” (1 ነገ. 827) የተባለለትን አምላክ፥ ድንግል ማርያም በማኅፀንዋ ተሸከመችው። ስለሆነምዳግሚት ሰማይ፥ ዳግሚት አርያም፥ ሰማይ ዲበ ምድር (በምድር ላይ ያለች ሰማይ)” ተባለች፤ ወንድሞቻችን ኦርቶዶክሳውያንም እንደ እኛ አባቶች፦ “O St. Mary, your womb is more spacious than the heavens” ብለው ዘመሩ። ስለዚህ የድንግል ማርያምን ወደ ሰማይ ማረግ (ዕርገት) እየተቃወሙ የትዕቢት ቃላትን ከመሰንዘር ይልቅ፥ ኦርቶዶክሳዊውን አስተምሕሮ በትሕትና በመማር፥ ዳግሚት ሰማይ (ድንግል ማርያም) በዕለተ እሑድ ከተፈጠረው ሰማይ ጋር ኅብረት በማድረጓ እጹብ እያልን እናድንቅ፤ ይህን ሁሉ ላደረገ አምላካችንም የከንፈራችንን ፍሬ የምስጋና መሥዋዕት አድርገን እናቅርብለት (ዕብ. 1315)
ማደሪያ መቅደሱን ያከበረ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅድስት እናቱ ጸሎትና ልመና በሰማያውያንና ምድራውያን በረከቶቹ ሁሉ ይባርከን፤ ለቅዱሳን አባቶቻችን የሰጠውን የእመቤታችንን የእናትነት ጣዕምና ፍቅር ያብዛልን።