Monday, September 25, 2023

❖በኋለኛው ዘመን፤

ከይሳኮር የሚበልጥ!


      ቀጣዩን (የሚሆነውን) የማወቅ ጉጉት በማንኛውም ሰው ውስጥ ያለ የጋራ ፍላጎት እንደ ሆነ ይስተዋላል፡፡ ምንም እንኳ ‹‹ነገ ለራሱ ይጨነቃልና፤ ለነገ አትጨነቁ፤ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል›› (ማቴ. 6፡34) ተብሎ በቅዱሱ መጽሐፋችን የተጻፈ ቢሆንም፤ ምድር ብርቱ ሠልፍ አላትና በክርስትናችንም እንዲህ የምናውቀውን ቃል መታዘዝ ጭንቅ ይሆናል፡፡ ደግሞ ቀጣዩ ምን ይሆን?፤ ኖሬ ምን ይገጥመኛል? የሚሉ ጥያቄዎች፤ ‹‹አይመጣምን ትተሽ ይመጣልን አስቢ›› አይነት አባባሎች . . ወዘተ፤ ሰው በቀጣዩ ላይ ያለው ሥጋት ከፍተኛ መሆኑን ያሳብቃሉ፡፡
      በመጽሐፍ ቅዱሳችን የመጀመሪያ ክፍል ‹‹ያዕቆብ ልጆቹን ጠርቶ እንዲህ አለ፡- በኋለኛው ዘመን የሚያገኛችሁን እንድነግራችሁ ተሰብሰቡ፡፡›› (ዘፍ. 49፡1-28) ተብሎ ተጽፎአል፡፡ የብዙዎች አባት አብርሃም፤ ሳቅ የሆነውን ይስሐቅን ወለደ፤ እርሱ ደግሞ አሰናካይ የሆነውን ያዕቆብን ወለደ፡፡ ያዕቆብ ከእርሱ ከራሱ በሆነው ብልጣ ብልጥነት ብዙ ዘመኑን የደከመ ቢሆንም በጎልማስነቱ ጊዜ ከአምላክ ጋር ታገለ፤ አልቅሶም ለመነው (ሆሴ. 11፡4)፡፡ እግዚአብሔር ያዕቆብን ስሙን ለእግዚአብሔር የሚዋጋ ሲል እስራኤል አለው፡፡ ያዕቆብ ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ወደ ማድረግ የመጣው ከስሙ መቀየር ጋር ተከትሎ ሆነ፡፡ ይህም በቀጣይ ኑሮው ላይ ግልጽ ለውጦችን አምጥቶአል፡፡

      መድኃኒታችን ኢየሱስ ለአገልግሎቱ ሾሞ፤ ታማኝ አድርጎ የቆጠረውን ሐዋርያ ጳውሎስ (1 ጢሞ. 1፡12) አስቀድሞ የነበረውን ስም በመቀየር (ሐዋ. 9)፤ ታናሽ የሚለውን የስም ፍቺ ይዞ ለጌታ ምርጥ ዕቃው ሆኗል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስምን ከተግባራዊ ባህርይ ጋርም ያያይዘዋል፡፡ በእርግጥም ዙሪያችንን አጥርተን ብናይ ስም በባህርይ ላይ ያለውን ተጽእኖ በግልጽ ልናይ እንችላለን፡፡ ሰው ዘመኑን በብዛት የሚሰማው የራሱን ስም ነውና፡፡ ወላጆች ለልጆች የስም ስያሜ ሲያወጡ፤ ልጆችም በወጣላቸው ስያሜ ሲጠሩ ማስተዋልና ለዚያ መጠንቀቅ ተገቢ ይሆናል፡፡

      ‹‹በኋለኛው ዘመን›› የሚለው ወደኋላ ያለፈውን ሳይሆን የፊቱን የሚያመለክት ጊዜ ጠቋሚ አገላለጽ ነው፡፡ በተመሳሳይ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያው ጴጥሮስ በኩል ‹‹በኋለኞች ዘመናት .  . ›› (1 ጢሞ. 4፡1) ሲል እናነባለን፡፡ ይህም ጸሐፊው ከነበረበት ዘመን የወደፊቱን የሚያሳይ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ያዕቆብ ወደ እርሱ ለተሰበሰቡት ለአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ልጆቹ፤ የሚሆነውን ነገራቸው፤ ባረካቸውም፡፡ ስለ መጀመሪያ ልጁ ሮቤል ሲናገር ‹‹ . . እንደ ውኃ የምትዋልል ነህ አለቅነት ለአንተ አይሁን . . ›› ይለዋል፡፡ በሥነ አመራርና በአስተዳደር ክህሎት ትምህርቶች ውስጥ ከመጽሐፍ ቅዱስ የሚመዘዘው አንዱ ማጣቀሻ በዚህ ስፍራ ላይ ያነበብነው ነው፡፡ ‹‹እንደ ውኃ መዋለል›› መወሰን፤ መጨከን አለመቻልን ያመለክታል፡፡ ሰው ከግል ማንነቱ ጀምሮ፤ ቤተሰብና አገር እስከ ማስተዳደር የሚያልፍባቸው ውሳኔውን የሚጠይቁ ግልጽ የኑሮ መስመሮች ውስጥ ያልፋል፡፡ አግባብ የሆኑ ውሳኔዎችን ያለ መወሰን አንዱና ትልቁ ምክንያት ደግሞ እንደ ውኃ የሚዋልለው የሰው ባህርይ ነው፡፡
      ተወዳጆች ሆይ፤ ውሳኔ ካልተሰጠባቸው ወረቀቶች ጀምሮ የውሳኔ ያለህ! የሚሉ ግንኙነቶች ምን ያህል ሊሆኑ እንደሚችሉ ጥቂት ለማሰብ ሞክሩ፡፡ ከአንዱ እጅ ወደ ሌላው እጅ ሲገላበጡ አፈር የመሰሉ ማመልከቻዎች፤ ከአንዱ አእምሮ ወደ ሌላው አእምሮ ሲመላለሱ የተረሱ ጉዳዮች፤ እንደ ውኃ በሚዋልሉ አለቅነት በማይገባቸው ሰዎች ጭምር የተበደሉ አይደሉምን?፤ የእውነት ዳኛ እግዚአብሔር (መዝ. 7፡11) ውሳኔዎቻችሁን በሚጠይቁ ነገሮቻችሁ ሁሉ ላይ መከናወንን ይስጣችሁ፡፡ ያዕቆብ እንዲሁ ለሌሎቹ ልጆቹ እየተናገረ በቁጥር 14 ይሳኮር ጋር ይደርሳል፡፡ ‹‹ይሳኮር አጥንተ ብርቱ አህያ ነው፤ በበጎች ጉረኖም መካከል ያርፋል፡፡ ዕረፍትም መልካም መሆኗን አየ፤ ምድሪቱም የለማች መሆንዋን፤ ትከሻውን ለመሸከም ዝቅ አደረገ፤ በሥራም ገበሬ ሆነ፡፡›› ይለዋል፡፡ ብርቱ፤ በበጎች መካከል ያረፈ፤ መልካም የሆነውን የተመለከተ፤ ለሸክም ዝቅ ያለ ገበሬ፤ ይሳኮር፡፡ ኦ! ይህ ምንኛ ደስ የሚል ማንነት ነው፡፡
      ስለ ይሳኮር ልጆች ደግሞ ‹‹እስራኤልም የሚገባውን ያደርግ ዘንድ ዘመኑን የሚያውቁ ጥበበኞች ሰዎች የይሳኮር ልጆች አለቆች ሁለት መቶ ነበሩ፤ ወንድሞቻቸውም ሁሉ ይታዘዙአቸው ነበር፡፡›› (1 ዜና. 12፡32) እንደተባለ፤ በዚህ ክፍል ደግሞ የሚገባውን ስለ ማድረግ፤ ዘመንን ከማወቅና ከጥበብ ጋር ይሳኮር የተነሣበትን ሁኔታ እናያለን፡፡ ከሰው ቀጣዩን የማወቅ ፍላጎት ጋር በተያያዘ አብሮ የሚታሰበው ጉዳይ ሊሆንና ሊመጣ ላለው ነገር በቂ የሆነ ኃይልና ጥበብ የማግኘት ጉዳይ ነው፡፡ በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ትክክለኛ መፍትሔ ይዞ የመገኘት ጉዳይ ለማንም የምንጊዜም አሳብ ነው፡፡
     ከመጀመሪያው ንባብ ኃይልና ትህትና፤ ከሁለተኛው ንባብ ደግሞ እውቀትና ጥበብን በዋናነት ልንመለከት እንሞክራለን፡፡ ይሳኮር ‹‹አጥንተ ብርቱ አህያ›› ተብሏል፡፡ አህያ ስድብ ሳይሆን የአህያ ስሟ ነው፡፡ እርግጫውን  ትተን ስሙን ከብርታት ጋር ማያያዝ ጥቅሱ የሚለውን በትክክል ለመረዳት አስፈላጊ ነው፡፡ ይሳኮር ተግባሩን እንደሚገባ ስለ ማድረግ፤ ወንድሞቹም እንዲሁ እንዲመላለሱ ብርቱና ኃያል ነው፡፡ ደግሞ ከኃይል ጋር ትከሻውን ለመሸከም ዝቅ ያደረገ ነበር፡፡ ኃይል በተሳሳተ መንገድ በተተረጎመባት የአሁኗ ዓለም፤ ኃይልን ከትህትና ጋር አስተባብሮ የሚገባውን በእግዚአብሔር ፊት ማድረግ መቻል በማንኛውም ዘመን የየዕለት ሁኔታዎች ውስጥ በድል የሚያሻግር ነው፡፡  
     ወደ አዲስ ኪዳን አሳብ ልውሰዳችሁ፤ ‹‹በዚህም ሥርዓት በሚመላለሱ ሁሉ ላይ በእግዚአብሔር እስራኤልም ላይ ሰላምና ምሕረት ይሁን›› (ገላ. 6፡16) ተብለናል፡፡ አሜን! ከቀደመው ኪዳን ክፍሎች ጋር ተጨማሪ የአሳብ ድልድይ ለመፍጠር ደግሞ ‹‹ዘመኑን እየዋጃችሁ በውጭ ባሉቱ ዘንድ በጥበብ ተመላለሱ›› (ቆላ. 4፡5) የሚለውን ምክር ልብ እንላለን፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ጸጋ ከሕግ፤ ከመጠን ይልቅ እንደሚበልጥ በሞገተበት መልእክቱ እውነተኞች ክርስቲያኖችን ‹‹የእግዚአብሔር እስራኤል›› ሲል ይጠራቸዋል፡፡ ነገሩ ‹‹በግልጥ አይሁዳዊ የሆነ አይሁዳዊ አይደለምና በግልጥ በሥጋ የሚደረግ መገረዝም መገረዝ አይደለምና . . ›› (ሮሜ 2፡28) እንደተባለው ነው፡፡ 
      በመጣው ዘመን እንዴት እንድንመላለስና የሚገባውን እንድናደርግ ለእግዚአብሔር እስራኤል ወንድሞቹ የሚታዘዙት ይሳኮር ወዴት አለ?ብለን መጠየቅ እንችላለን፡፡ መውጣት መግባታችንን በኃይልና በትህትና፤ ደግሞ በእውቀትና በጥበብ ይሆን ዘንድ በመካከላችን እንዲህ ያለ ማን አለ?ሰው ለራሱ እንኳ የሚበቃ ምክር ባጣበት በጽድቅ የሚመክር፤ መጨካከን የኑሮ ከፍታ በሆነበት የፍቅር ልብ የማያልቅበት፤ በዚህ ዓለም ጥበብ እሽቅድድም ብልጫ ሰው በተጠመደበት የሚበልጥ ጥበበኛ፤ የእውቀት ብዛት የተግባር ማነስ በሚታይበት በቃል በኑሮ የበረታ፤ ኃይል ለማንሣት ሳይሆን ለመጣል በሆነበት የሚያድን ኃይል፤ ትህትና እንደ መበለጥና መሞኘት በሚቆጠርበት ሁሉን የሚሸከም ማን ይሆን?
 
     ተመሳሳይ ነገሮች መሐል ልዩ የሆነ አንድ እንደሚፈልግ ሰው ኃጢአት የሰውን ታሪክ ምንም ልዩ የማይገኝበት ተመሳሳይ አድርጎታል (ሮሜ 3፡23)፡፡ ዳሩ ግን ‹‹ . . በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ›› (ዕብ. 2፡14 እና 15) ተብሎ እንደተጻፈ፤ ሰው የሌለው ሁሉ ያለው ክርስቶስ ከኃጢአት በቀር እኛን መስሎ ወደዚህ ዓለም መጥቶአል (1 ጢሞ. 1፡15)፡፡ ወንድሞች ብሎ ሊጠራን ያላፈረው (ዕብ. 2፡13)፤ ፍጹም ሰውም የሆነው ወልድ ከይሳኮር የሚበልጥልን ዘመኑን የምናውቅበትና የምንመላለስበት ጥበብ፤ ትሁትና ኃይል ነው፡፡ ስለ ትህትና ቢሆን የባሪያን መልክ የያዘ፣ ራሱን ባዶ ያደረገ፣ ራሱን ያዋረደና ለመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ነው (ፊል. 2፡7)፤ ደግሞ ስለ ኃይል ቢሆን እርሱ የኃይል ሁሉ ምንጭ ነው፡፡ ‹‹ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ›› (ፊል. 4፡13) ተብሎ እንደተጻፈ፤ በእያንዳንዱ ዘመን በመዋረድ ቢሆን በመብዛት፤ በመጥገብ ቢሆን በመራብ፤ በመብዛት ቢሆን በመጉደል ክርስቶስ ሁሉን የሚያስችል በቂ ኃይላችን ነው፡፡
      ‹‹ . . የተሰወረ የጥበብና የእውቀት መዝገብ ሁሉ በእርሱ ነውና፡፡›› (ቆላ. 2፡3) ክርስቶስ የዘመኑን መልክ የምንለይበት እውቀት፤ ለዚያም የሚሆን የኑሮ ጥበብ ነው፡፡ በዚህ ዓመት ደግሞ ምን ይሆን?በክርስቶስ ክርስቲያን ለሆኑ ጭንቀት ሊሆን አግባብ አይደለም፡፡ ለማዳን የሆነው የእግዚአብሔር ኃይል፤ ልጁ ኢየሱስ አለ (ሮሜ 1፡16፤ 1 ቆሮ. 1፡24)፤ የዋህ እና በልቡ ትሑት የሆነው የነፍሳችን ዕረፍት ከእኛ ጋር ነው (ማቴ. 11፡29)፡፡ ሰዎችን ሁሉ የሚያውቅ፤ ስለ ማንም ምስክር የማያሻው የእውቀት ጥግ ማወቃችን ነው (ዮሐ. 2፡23)፡፡ የዚህች ዓለም ጥበብ በእግዚአብሔር ፊት ሞኝነት እንደ ሆነ ግልጥ ያደረገልን ክርስቶስ ጥበባችን ነው (1 ቆሮ. 3፡18)፡፡ ስለዚህ ‹‹ . . የኃይሉ ታላቅነት ከእግዚአብሔር እንጂ ከእኛ እንዳይሆን ይህ መዝገብ በሸክላ ዕቃ ውስጥ አለን›› (2 ቆሮ. 4፡7)፡፡ 
      ‹‹ . . በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና፡፡›› (ማቴ. 18፡20) እንዳለን፤ ቤተ፡ ክርስቲያን በምድር እንደ ሕያው እግዚአብሔር መንግሥት የሚገባውን እንድታደርግ ወንድሞቹ የሚታዘዙት ክርስቶስ በመካከላቸው ነው፡፡ ዘመኑ እንደ ይሳኮር ባለው የአህያ ጉልበት አይታለፍም፤ ትከሻውን ለሸክም ዝቅ እንዳደረገው እንደ እርሱም ትህትናና ታታሪነት አይከናወንም፤ ደግሞም በዚያ እውቀት ሊታወቅና እንደዚያ ጥበብ ተጠበን ልናልፈው አንችልም፡፡ ዳሩ ግን የሚበልጠው በሰው መካከል ሰው ሆኖ መጥቶአል፡፡ ከእርሱ የሚበልጥ፤ እንደ እርሱም ያለ ወደፊት አይመጣም፡፡    

Thursday, September 16, 2021

❖ዘመኑን ዋጁ፦

ዘመኑን ዋጁ፦
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን ለሚገኙ ምእመናን መጪው ጊዜ ምን እንደሚመስል ከገለጠላቸው በኋላ አያይዞ እንዴት መኖር እንዳለባቸው መክሮአቸዋል፡፡ ስለመጪው ጊዜ ሲነግራቸው ‹‹ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና›› ብሏቸዋል፡፡
እንዴት መኖር እንዳለባቸው ሲመክራቸው ደግሞ ‹‹እንደጥበበኞች›› በጥበብ መመላለስ እንደሚገባቸው፤ ዳግመኛም ‹‹በጥንቃቄ›› እና ‹‹በመጠበቅ›› እየኖሩ ዘመኑን እንዲዋጁ አሳስቧቸዋል፡፡ (ኤፌ5፥15-16) እነዚህ ቁም ነገሮች ለጊዜው በኤፌሶን ላሉ ምእመናን ቢጻፉም ለሁላችን ምክር እና እዝናት የሚሆኑ ናቸውና በየተራ እንመለከታቸዋለን!
‹‹ቀኖቹ ክፉዎች ናቸው›› ማለት ምን ማለት ነው? የቀን ክፉ አለን? ብለን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ በእርግጥ ክፋት አስቦና ፈቅዶ በሚበድል በሰው ልጅ ዘንድ እንጂ በቀናት ዘንድ ክፋት የለም፡፡ ዕለታትን የፈጠረ እግዚአብሔር ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ደግሞ ‹‹እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉ መልካም ነው›› (1ጢሞ4 ፥ 4) ስለዚህ ዕለታት በሙሉ በተፈጥሮ አንድ ናቸው፤ እንዲሁም ሁሉም መልካም ናቸው፡፡ የዕለታት መልካቸው የሰው ልጅ ምግባር ነው፡፡ የሰው ሥራ ክፉ የሆነ እንደሆነ ዕለታትም ይከፋሉ፡፡ ሰው መልካም ሲሆን ዘመናቱ መልካም ይሆኑለታል፡፡ ሐዋርያው በዕለት አንጻር የሰውን ክፉነት ሲነግረን ‹‹ቀኖቹ ክፉዎች›› ናቸው አለን፡፡ በጸሎተ ቤተ ክርስቲያን ‹‹እግዚኦ አድኅነነ እምዕለት እኪት ወባልሃነ እምኩሉ መንሱት›› - ‹‹አቤቱ ከክፉ ቀን ከፈተናም ሁሉ ፈጽመህ አድነን፡፡›› የሚል ኃይለ ቃል እናገኛለን፡፡ አበው ካህናት ሲያሳርጉ ‹‹ከዕለት እኪት ከዘመን መንሡት ይሰውረን!›› የሚሉት እነዚህን የቅዱሳት መጻሕፍት ኃይለ ቃላት መሠረት አድርገው ነው፡፡ የሰው ልጅ ምግባር ሲከፋ ዘመናቱ ክፉዎች የሚሆኑት ዕለታት የተፈጠሩት ለሰው ልጆች ጥቅም ስለሆነ ነው፡፡ ‹‹ሰንበት ስለ ሰው ተፈጥሮአል እንጂ ሰው ስለ ሰንበት አልተፈጠረም›› እንዲል፡፡ (ማር2 ፥ 27) ሐዋርያውም ቀኖች ለሰው የተፈጠሩ መሆናቸውን በሚጠቁም ቃል ‹‹ቀኖቹ›› ማለቱን ልብ እንበል፡፡ ‹‹ቀኖቹ›› ያለው የሰው ልጅ ቀኖች ለማለት ነውና፡፡ ስለዚህ ዕለታት ለሰው ልጅ መጠቀሚያነት እስከተፈጠሩ ድረስ ሰው ሲያበላሻቸው ይበላሻሉ ማለት ነው፡፡ ሰው ምግባሩን ሲያከፋ ዕለታት እየከፉ የሚሄዱት በዚህ ምክንያት ነው፡፡ ሰው መልካም ሲሁንም ‹‹ቀኖቹ›› መልካም ይሆኑለታል፡፡
መጪው ጊዜ፦
ነቢዩ ዳንኤል እንደተናገረው ዘመን እየገፋ በሄደ ቁጥር ዕውቀት ይበዛል፡፡ ሥልጣኔም ይሰፋል፡፡ (ዳን12 ፥ 4) ይሁን እንጂ በሥነ ምግባር ደረጃ የሰው ልጆች ክፋት እየጨመረና በምድር ላይ ኃጢአት በምልዓት እየተፈጸመ ይመጣል፡፡ ስለዚህ ይህን እውነት በትንቢት መነጽር የተመለከተው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ቀኖቹ ክፉዎች ናቸው›› ማለቱ የሚገባ ነው፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከዚህ ሐሳብ ጋር የሚስማማ ነገር አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ በመጨረሻዎቹ ዘመናት እምነት በሰው ልጅ ዘንድ ጎደሎ እንደሚሆን በተጠየቅ መንገድ ‹‹ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን?›› ሲል ተናግሯል፡፡ (ሉቃ18 ፥8) እንዲሁም በሰው ልጆች መካከል ፍቅር እንደሚቀዘቅዝ ‹‹ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች፡፡›› በማለት ከነምክንያቱ አስቀምጦልናል፡፡ (ማቴ24 ፥ 12) ይህ በግልጥ የሚታይ እውነት ስለሆነ ምስክርም አያስፈልገውም፡፡ እንግዲህ በመጪዎቹ ዘመናት እምነትና ፍቅር በሰው መሃል ካልተገኙ የሰው ልጅ ለበጎ ምግባር ምን መነሻ ይኖረዋል? ከፍቅርስ የሚበልጥ ምን ምግባር ይኖረዋል? እንዲህስ ከሆነ ‹‹ቀኖቹ ክፉዎች ናቸው›› መባሉ ተገቢ አይደለምን?
ቀኖቹ ክፉዎች መሆናቸው እና የሰው ልጆች መንፈሳዊ ደረጃ እየዘቀጠ የሚሄድ መሆኑን ከራሳችን የግል ሕይወት በመነሣት መረዳት የምንችለው ነው፡፡ አብዛኞቻችን ለመንፈሳዊ ነገር ያለን ትጋት ስንጀምር እንደነበረን አይሆንልንም፡፡ ስንጀምር የነበረን ለጸሎት ማልዶ መነሣት፣ ዘወትር ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ፣ ቃለ እግዚአብሔርን በመመሰጥና በድስታ ማዳመጥ፣ ንስሐ መግባት፣ ሥጋ ወደሙ መቀበል፣ ወይም ከመንፈሳዎ ምሥጢራት ስለ መራቃችን መቆጨት ከውስጣችን ሙጥጥ ብሎ ያለቀ ይመስላል፡፡ በምትኩ ተስፋ መቁረጥ፣ ድንዛዜ ስንፍና እና ልዩ ልዩ የኃጢአት ልምምዶች ልባችንን አጣበውታል፡፡ ታዲያ በእኛ ውስጥ የምንመለከተው ይህ ሁኔታ በብዙ ሰዎች ዘንድ መኖሩን በተደጋጋሚ ስንሰማ ዘመኑ እየከፋ መምጣቱን አይነግረንምን?
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ቀኖቹ ክፉዎች ናቸው›› በማለት ብቻ አላበቃም፡፡ በሌላ ክፍል ‹‹ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንደሚመጣ ዕወቅ፡፡›› እያለ መጪው ጊዜ ምን እንደሚመስል ከነምክንያቱ ጽፏል፡፡ (2ጢሞ3.፥ 1) መጪው ጊዜ አስጨናቂ የሚሆነው ሰዎች ‹‹ራሳቸውን የሚውዱ፣ ገንዘብን የሚወዱ፣ ትምክህተኞች፣ትዕቢተኞች፣ ተሳዳቢዎች፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያመሰግኑ ፣ ቅደስና የሌላቸው፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ዕርቅን የማይሰሙ፣ ሐሜተኞች፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ጨካኞች፣ መልካም የሆነውን የማይወዱ፣ ከዳተኞች፣ ችኩሎች፣ በትዕቢት የተነፉ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ›› ሰለሚሆኑ እንደሆነ አያይዞ ይናገራል፡፡ ሐዋርያው የቀኖቹን ክፉነት ብቻ ሳይሆን እኛ ከዚህ ሁሉ ለመዳን ምን ማድረግ እንዳለብንም ጠቁሟልና ያንን ቀጥለን እንመለከታልን፡፡
1ኛ. ዘመኑን መዋጀት:-
ሐዋርያው ‹‹ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና ዘመኑን ዋጁ›› ብሎናል፡፡ ዘመንን መዋጀት ማለት ምን ማለት ነው ዘመኑን መዋጀት ማለት ዘመኑን መግዛት፣ ድል ማድረግ፣ ማሸነፍ፣ የራስ ማድረግ፣ ዘመኑን መቅደም እንጂ በዘመን አለመቀደም… ወዘተ ማለት ነው፡፡ ዘመን ዘመናት የሚባሉት የሚመጡት አዳዲስ ዓመታት ብቻ አይደሉም፡፡ ያለፈውም ጊዜ የዘመን አካል ነው፡፡ ስለዚህ ዘመንን መዋጀት ስለሚመጣው ብቻ ሳይሆን ስላለፈውም መመርመር፣ ታሪክን በሚገባ ማወቅ፣ ካለፈው መማርና ለወደፊቱ መጠንቀቅ ነው፡፡ ያለፈውን ዘመን ካልመረመርነው ዘመንን ዋጀን አይባልም፡፡ የሚመጣውን ብንዋጅ ያለፈውን ዘመን ካልዋጀን ዘመኑን ዋጀን ሊባል አይቻልም፡፡ በተጨማሪም ዘመኑን መዋጀት ማለት ዘመን ያፈራውን የቴክኖሎጂ ውጤቶች ማወቅና መጠቀም ማለት ብቻ አይደለም፡፡ ከዚህም የሚሰፋ ሐሳብ ያለው ነው፡፡
ዘመኑን መዋጀት ማለት በእያንዳንዱ ቀን ፈተናዎችን እንደየአመጣጣቸው እየለዩ መመከት ማለት ነው፡፡ የሰው ልጆች ጥንተ ጠላት ሰይጣን ዓለምን ማርኮ ለመግዛት ብዙ አሳሳች መንገዶችን ይጠቀማል፡፡ አዳምንና ሔዋንን የፈተነው አምላክነትን እንዲመኙና ዕፀ በለስን እንዲበሉ በማድረግ ነው፡፡ ኢዮብን የፈተነው ያለውን ሁሉ በማውደም እና በሽታ ላይ እንዲወድቅ በማድረግ ነው፡፡ እስራኤልን የወርቅ ጥጃ እንዲያመልኩ ስቧቸዋል፡፡ ክብር ይግባውና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዲያብሎስ ተፈትኗል፡፡ የፈተነበት መንገድ ግን ከተዘረዘሩት በእጅጉ ይለያል፡፡ ስለዚህ ሰይጣን የሚፈትነን እንደዘመናችን ስለሆነ ዘመኑን ካልዋጀን ፈተናውን ማለፍ አንችልም፡፡ስለዚህ ሐዋርያው እንደመከረን ‹‹መጠንቀቅና›› ራሳችንን ‹‹መጠበቅ›› አለብን፡፡ ‹‹መጠንቀቅ›› ካላወቅነው፤ ነገር ግን ሊሆን ይችላል ብለን ከምንገምተው ክፉ ነገር ሁሉ ራስን ለማዳን መሽቀዳደም ሲሆን ‹‹መጠበቅ›› ደግሞ ክፉ መሆኑን ከተረዳነው ነገር ሁሉ እንዳይጎዳን የምናደርገውን ጥረት ያመለክታል፡፡ (ኤፌ5፥5)
2ኛ. በጥበብ መመላለስ:-
ጥበብ ሥጋዊ እና መንፈሳዊ ተብሎ በሁለት ይመደባል፡፡ ወይም በቅዱስ ያዕቆብ ገለጻ መሠረት ሰማያዊ እና ምድራዊ ጥበብ ይባላል፡፡ (ያዕ3፥ 15-17) የመንፈሳዊ ጥበብ መነሻው ሃይማኖት ነው፡፡ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው›› ይላልና፡፡ (መዝ1)0፥0) እግዚአብሔርን መፍራት ደግሞ በሃይማኖት ይተረጎማል፡፡ ምክንያቱም በዓይነ ሥጋ ያላዩትን እግዚአብሔርን ኃጢአት ብሠራ ይፈርድብኛል ብሎ መፍራት ራሱ እምነት ነውና፡፡ ስለዚህ የጥበብ መጀመሪያ እምነት መሆኑን በዚህ እናውቃለን፡፡ እንዲህ ከሆነ በጥበብ መመላለስ ማለት ደግሞ በእምነት መመላለስ ማለት ነው፡፡
በተጨማሪም በጥበብ መመላለስ ማለት በዚህች ዓለም ማታለልና ክፉ አሠራር እንዳይያዙ በዘዴ፣ በዕውቀት፣ በማስተዋል፣ በብልሃትና በፈሊጥ መመላለስ ማለት ነው፡፡ በሃይማኖት መመላለስ ከክፉ ሁሉ ይሰውራል፡፡ እውነተኛ የልብ እምነት ክፉውን ሁሉ ይመክታል፡፡ ‹‹ዓለምንም የሚያሸንፈው እምነታችን ነው›› ተብሎ እንደተጻፈ እምነት ያለው ሰው በምንም በማንም አይሸነፍም፡፡ (1ዮሐ5፥4) ስለዚህ በዚህ ዘመን ሃይማኖታችንን ጠበቅ አድርገን መያዛችን ለአሸናፊነታችን ዋስትና ነው፡፡
3ኛ. ከክፉ መሸሽ:-
አብዛኞቻችን በጎ ዘመን ላይ ደርሰን በሰላምና በደስታ ለመኖር የምንጓጓውን ያህል ለዚህ የሚያበቃውን መስፈርት ግን ለማሟላት ስንደክም አንገኝም፡፡ ወደፊት በመልካም ለመኖር የሚጠበቅብን ነገር አለ፡፡ ለዚህም ቅዱስ ዳዊት የተናገረውን ልብ እንበል፡፡ አስቀድሞ ‹‹ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማነው? በጎንም ዘመን ለማየት የሚወደድ?›› ሲል ይጠይቃል፡፡ መቼም ለዚህ ጥያቄ እኔ እፈልጋለው ብሎ መልስ የማይሰጥ አይኖርም፡፡ ቀጥሎ ማሟላት የሚገባን ነገር መኖሩን ‹‹አንደበትህን ከክፉ ከልክል፡፡ ከንፈሮችህም ሽንገላን እንዳይናገሩ ከክፉ ሽሽ መልካምንም አድርግ ሰላምን እሻ ተከተላትም›› ሲል ይጠቁመናል፡፡ (መዝ33፥ 12-14) ስለዚህ በአጭሩ ከክፉ መሸሽና መልካም ማድረግ የወደፊት መንገዳችንን እና መጪውን ዘመን ብሩህ ያደርግልናል፡፡ መልካም አኗኗር ከውስጣችን የሚፈልቅ እንጂ በግዢ የሚገኝ ቁስ አይደለምና፡፡ ደስተኛና ሰላማዊ ኑሮ መኖር ከፈለግን ምግባራችንን እናስተካክል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹መልካም ብታደርግ ፊትህ የሚበራ አይደለምን?›› ብሎአልና፡፡ (ዘፍ4 ፥ 7) መልካም ከሠራን ፊታችን ይበራል፡፡ ዘመኑም መልካም ይሆንልናል፡፡ እንጂ መልካም አዲስ ዓመት ስለተባባልን ብቻ ዘመኑ መልካም እንደማይሆንልን እንረዳ! በጎ መመኘታችን እንደተጠበቀ ሆኑ በጎ ለመሥራት አሁኑኑ እንነሣ!
ከዕለት እኪት ከዘመን መንሡት ይሰውረን! አሜን!
መልካም አዲስ ዓመት ያድርግልን!

Monday, August 9, 2021

❖መንፈሳዊ እድገት፦

#መንፈሳዊ እድገት፦
መንፈሳዊ ዕድገት በማይታየው ቅዱስ መንፈስ የተደገፈ የሚታይ ኑሮ ነው፡፡
መንፈሳዊ ዕድገት ያመነ ሰው እምነቱን በሥራ የሚገልጥበት ሂደታዊ(ዘላቂነት ያለው) አኗኗር ነው፡፡
መንፈሳዊ ዕድገት የመንፈሳዊ ሰው የከፍታ ምስጢር ነው፡፡
መንፈሳዊ እድገት መንፈሳዊ ሰው በመንፈስ ቅዱስ በመታገዝ በመንፈስ ፍሬዎች የሚያጌጥበት የሕይወት ውበት ነው፡፡ይህ ኑሮ ሰው እንዲጠቀምበት፥ እግዚአብሔር እንዲከብርበት በመለኮት ዕቅድ ቀድሞ የታሰበ ኑሮ ነው፡፡

መንፈሳዊ ዕድገት የቅድስና መንገድ ነው፡፡
መንፈሳዊ ዕድገት በግንዱ በክርስቶስ በመሆን ፍሬ የምናፈራበት አኗኗር ነው፡፡ከግንዱ ተለይቶ ማፍራት አይቻልም፡፡"እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል።"ዮሐንስ 15:5
በመንፈሳዊ ሕይወት የገጠመን ዝለት እና ስልቹነት ከግንዱ ጋር አለመተባበር ነው፡፡በግንዱ ካልሆነ ድርቀት እንጂ እድገት አይኖረንም፡፡የመንፈሳዊ እድገት መሠረቱ በግንዱ ሆኖ ማፍራት ነው፡፡መንፈሳዊ እድገት ሰሞነኛነት አይደለም፡፡መንፈሳዊ ሕይወት የማይቋረጥ ኑሮ ነው፡፡በየጥቂቱ የሚያድግ አኗኗር ነው፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ ይህን ኑሮ በሚገባ ተርኮታል፦
"ስለዚህም ምክንያት ትጋትን ሁሉ እያሳያችሁ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፥ በበጎነትም እውቀትን፥ በእውቀትም ራስን መግዛት፥ ራስንም በመግዛት መጽናትን፥ በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰል፥ እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማችን መዋደድ፥ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ጨምሩ።" 2ጴጥ 1:5-10፡፡
እስኪ ራሳችንን እንጠይቅ መንፈሳዊ ሕይወታችን እየጨመረ ነው ወይስ እየቀነሰ ነው? በቦታ እና በሁኔታዎች አይወስንም ??? በጊዜ ሂደት አልቀነሰም ??? መንፈሳዊ ሰው በመጨመር በማብዛት እና በመብዛት ፍሬው ይገለጣል፡፡መንፈሳዊ ዕድገት ክርስቶስን ወደመምሰል የምናደርገው ጉዞ ነው፡፡

1. የመንፈሳዊ ዕድገት መሠረት፦
ሕንፃ ያለ መሠረት እንደማይመሠረት መንፈሳዊ ዕድገትም ያለ መሠረት አይወጠንም፡፡የመንፈሳዊ ሕይወት ጽኑ መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ጥሩ መሠረት ያለው ቤት ሞገድ እና ነፋስ እንደማይነቅለው በክርስቶስ ላይ ሥር ሰዶ በመታነጽ የመንፈሳዊ ዕድገት ጉዞ የወጠነ አማኝም በምንም ሁኔታ በፍጹም አይናወጽም፡፡መሠረቱ ላይ ያልተተከለ፥ ራስ በሆነው ያልተጋጠመ ይህን ክፉ ዘመን አያልፍም፥ ነፋስ አቅጣጫ ያስቀይረዋል፡፡ተወዳጆች ሆይ፦ እምነት እና አላማችንን መሠረቱ ላይ እናድርግ፡፡የሁሉም መነሻ እና መድረሻ እርሱ ነውና፡፡ "የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ።" ዕብ 12:1-2
መሠረቱ አንድ ነው፥ ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልም፡፡ "ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልምና፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"
1ኛ ቆሮንቶስ 3:11 ይህ መሠረት ላይ የቆመ ዕድገቱ አስተማማኝ ነው፥ አይንሸራተትም፥ አይሰነጠቅም፥ መከራ ወደ ኋላ አይመልሰውም፡፡ከተመሠረትን በኋላ ጸንተን በብዙ ፍሬ ለማደግ የሚከተሉትን መንፈሳዊ ተግባራት ሳናቋርጥ እናድርግ፦
1. ቃሉን መመገብ
2. ጸሎት
3. ጾም
4. መንፈሳዊ እውቀት መጨመር
5. ትጋት
6. ቅዱስ ቁርባን

1.ቃሉን መመገብ፦
በተፈጥሮ ህግ የማይመገብ ሰው ይራባል ፣ይደክማል፣ ይታመማል ፣ባለመመገቡ ከጸና ይሞታል።ቃሉን የማይመገብ ክርስትያን መንፈሳዊ ረሃብ (የፍቅር፣የትህትና ፣የበጎነት ፣የቅንነት ወዘተ… ረሃብተኛ)፣ ድካም( ለፀሎት ፣ለአገልግሎት ፣ለፆም ወዘተ… ደካማ)፣ ህመም ( ቃሉ ምንድነው ? መንፈሳዊነት ምንድነው ? ቤተክርስትያን ምንድናት ወዘተ… የሚል ህመምተኛ )፣ሞት( ያለእግዚአብሔርና ያለቃሉ የሚኖር ስም ያለው ነገር የሞተ ማንነት ያለው ይሆናል) ።
"ጌታ ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እንደ ሆነ፥ ለመዳን በእርሱ እንድታድጉ አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ።"
1ኛ ጴጥሮስ 2:2-3። እንደተባለ ቃሉ ለእድገታችን ጠቃሚ የሆነ ዋና ምግብ ነው፡፡በቃሉ በኩል እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የፈቃዱን ምስጢራት እናውቃለን፡፡ስለዚህ እንደ ፈቃዱ የሆነ እድገት ይኖረናል፡፡የቃሉ ወተት የሚያስፈልገን አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ነው፡፡ወተት አሁን ለተወለዱ ሕፃናት የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ካደጉ በኋላ ግን ብዙ አማራጭ ይኖራቸዋል፡፡መንፈሳዊ ሰው በዋናነት ሁልጊዜ የቃል ወተት ያስፈልገዋል፡፡ቃሉ የልጅነት ትዝታችን፥ የጉልምስና ትጥቃችን፥ የሽምግልና ወራት ኃይላችን ነው፡፡ቃሉ የማያስፈልግበት ጊዜ የለም፡፡ስለዚህ ሁልጊዜ የቃሉ ወይን ጠጅ የማይጎድልባቸው ማድጋዎች እንሁን፡፡ያለ ቃሉ ድጋፍ መንፈሳዊ እድገት አይከናወንም፡፡ሕፃናት ከእናታቸው የሚያገኙት ወተት ጤናማ እንደሚያደርጋቸው ሁሉ የጌታ ምክርም ጤናማ ዕድገት እንዲኖረን ያደርጋል፡፡

2. ጸሎት፦
ለምን እንጸልያለን?
-ፈቃዱን ለማወቅ ዘፍ 24:11-14
-ለማመስገን መዝ 12:6
-ወደፈተና እንዳንገባ ማቴ 26:41
-ከክፉ ለመጠበቅ ማቴ 6:13
-ዲያብሎስን ለመርታት ማቴ 17:21
እኛ መሥራት ያልቻልነውን እግዚአብሔር እንዲሠራልን የምንጠይቅበት መሳሪያ ጸሎት ይባላል፡፡ነገር ግን መጸለይ ባለመቻላችን የጸሎትን ኃይል መጠቀም አልቻልንም፡፡ባለመጸለያችን ከነችግራችን እንኖራለን።ጸሎት የሕይወታችን እንቅስቃሴ በጌታ ፈቃድ እንዲመራ ፈቃደኝነታችንን የምናሳውቅበት መንገድ ነው፡፡"ከልብ የሆነ ጸሎት ለእግዚአብሔር በጎ መዓዛ ያለው መብአ ነው" እንዳለ ቅዱስ አግናጥዮስ ጸሎት የአምልኮ መገለጫ ነው፡፡ለመንፈሳዊ ዕድገት እጅግ ቁልፍ መሳሪያ ነው፡፡ጸሎት የማይቋረጥ ድርጊት ነው፡፡ጸሎት በእኛ እና በእግዚአብሔር መካከል ያለ የግንኙነት መስመር ነው፡፡መጸለይ ካቆምን ከአገልግሎት መስጫ ክልል ውጭ እንሆናለን፡፡በብዙ ጉዳዮች ስለተያዝን የጸሎት ጊዜና አቅም አጥተናል፡፡ስለዚህ ለመጸለይ እንኳ ጸሎት ያስፈልጋል፡፡ጸሎት የመንፈስ ብልጽግና ያመጣል፤ ኃይል ያጎናጽፋል፤ በጸጋ ያሳድጋል፡፡<ጸሎት ለነፍስ ሰላምና እርጋታን ያመጣል፡፡> ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፡፡ጸሎታችን፦ በእምነት፥ በመንፈስ፥ በስሙ፤ እንደ ፈቃዱ መሆን አለበት፡፡ያለ ጸሎት የመንፈሳዊ ዓለም ተጋድሎ አይቻልም፡፡ድል የኛ እንዲሆን፥ እንድናድግ ጸሎት ያስፈልገናል፡፡ጸሎታችን ምስጋናን፥ የኃጢአት ይቅርታን፣ምልጃን እና ልምናን ማካተት አለበት፡፡ 1ጢሞ 2:13፡፡

3 ·ጾም፦
ጾም በራስ ፈቃድ ለጊዜው ከምግብ፤ ለዘላለም ከኃጢአት መከልከል ነው፡፡ጾም የክርስቲያን ሕይወት አካል ነው፡፡ ጾም የአዲሱ ሰው ኑሮ ማሳያ ነው፡፡<ጾም የሥራ መጀመሪያ ነው፡፡>ጾም ለመንፈሳዊ ዕድገት እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ጾም ስለ እግዚአብሔር ክብር የሥጋ ፍላጎትን መተው ነው፡፡በሁለቱም ኪዳናት መልካም ታሪክ ያላቸው አባቶች የጾም ሕይወት ነበራቸው፡፡ሙሴ፥ ኤልያስ፥ አስቴር፥ ዳንኤል፥ ዕዝራ ከብሉይ ኪዳን ይጠቀሳሉ፡፡በአዲስ ኪዳን ሐዋርያት እና ሌሎች ለእግዚአብሔር ያደላ ኑሮ ያላቸው በጾም ይታወቀሉ፡፡የክርስትና አርአያ ጌታችን ኢየሱስ ጾሟል፡፡የእርሱን ፍለጋ የምንከተል በጾም ላይ ጠንካራ አቋም ሊኖረን ይገባል፡፡በመብል የሠሩባት አልተጠቀሙምና፡፡ዕብ 13:9:: በመንፈሳዊ እድገት ከፍ ለማለት፥ለመንፈስ ቅዱስ አሠራር ለመመቸት ሥጋችንን መጎሰም አለብን፡፡
ለምን እንጾማለን?
-ለእግዚአብሔር ፈቃድ ራሳችንን ለማስገዛት መዝ 35:13 ዕዝ 8:21
-ለንስሐ ዮናስ 3:10
-ለአገልግሎት ጥንካሬ እና ለበረከት ማቴ 6:17-18
እንዴት እንጹም፦
-በደልን በመናዘዝ ኢሳ 58:8 ሉቃስ 18:11
-ፍትሐዊ በመሆን ኢሳ 58:3
-ራስን በመግዛት 1ቆሮ 7:5
-ሥጋን ከነመሻቱ በመስቀል ገላ 5:24
-የዲያብሎስን ማታለያ በመናቅ ማቴ 4:1-11
-ታይታ ባለመፈለግ ማቴ 6:16-18
-ሌላውን ባለመንቀፍ ሮሜ 14:41.

4 ·እውቀት፦
መንፈሳዊ እውቀት ለዕድገት ወሳኝ ነው፡፡ ለማደግ የጥበብን ደጅ ማንኳኳት አለብን፡፡እውቀት በትምህርት፣ በልምድ፣ በምንባብ፣ በጥናት እና ምርምር ይገኛል፡፡ቅዱስ አትናቴዎስ <ለእግዚአብሔር ራሱን የሰጠ ሰው ፀሐይ ንጋት ላይ ስትወጣ በእጆቹ ላይ ቅዱስ መጽሐፍ መገኘት አለበት>እንዳለ ከመጻሕፍት ጋር መዛመድ አለብን፤ መንፈሳዊ እውቀት ግን የልብ ቅንነት እና እምነት ይፈልጋል፡፡መንፈስ ቅዱስ ለሚያስተምረን ልባችን ክፍት መሆን አለበት፡፡ዕድገትን የሚያቀጭጩ ከንቱ ፍልስፍናዎችን መራቅ አለብን፡፡ብዙ ማብራሪያ የሚያገላብጥ፥ ጥንታዊ ቋንቋዎች አመሣክሮ ቃሉን የሚያጠና አማኝ በኑሮም ምስክር መሆን አለበት

5. ትጋት፦
ትጋት የፍሬ መሠረት ነው፡፡ ትጋት የመንፈሳዊ ዕድገት ትጥቅ ነው፤ ያለ ትጋት ዕድገት የለም፡፡የተሰጠንን ጸጋ እና ኃላፊነት በማክበር ለተፈጠርንበት አላማ እንድንታመን መትጋት አለብን፡፡ትጋት በስም ሳይሆን በሥራ የሚገለጽ ጥንካሬ ነው፡፡ስንፍና፥ ዳተኝነት፥ ግዴለሽነት፥ ዝለት፥ ቅምጥልነት የዕድገት ፀር ናቸውቅ.ጳውሎስ "በእምነትና በትዕግሥትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ፥ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን።"ዕብ 6:11—12፡፡መንፈሳዊ ሰው የዕድገቱ ቀጣይነት የሚረጋገጠው በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ ባለው ድጋፍ ሲሆን ትጋት የከበረ ሀብቱነው፡፡ይህ ትጋት የዘመን ሙሉ ኃይል ነው፡፡ያለ ትጋት ምንም ለውጥ አናመጣም፡፡በእምነት የተስፋ ቃል ተቀብለናል፤ በትዕግስት ለመቀበል ትጋት ትልቁ መሳሪያ ነው፡፡ሥራ ጀምረን ለመጨረስ ኃይል፥ መንፈሳዊ ኑሮ ለመቀጠል አቅም፥ ለመበልጸግ ሀብት፥ ለማሸነፍ አቅም ትጋት ነው፡፡ "ለሰው የከበረ ሀብት ትጋት ነው"ምሳ 12:27።

6· ቅዱስ ቁርባን፦
የክርስቶስ ሥጋና ደም/ ቅዱስ ቁርባን/ ሞቱን የምንመሰክርበት አንደበት ነው፡፡"ይህን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ፥ ይህንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁና።" 1ቆሮ 11:26፡፡ቅዱስ ቁርባን የኪዳን ምልክት፥ የምስክርነት ራስ፥ የኅብረት ማህተም፥ የግንኙነት መሠረት ነው፡፡ለመንፈሳዊ ዕድገት እጅግ በጣም ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ሰበብ ማብዛቱን ትተን ቁርባንን የመንፈሳዊ ሕይወታችን አካል እናድርግ፡፡መንፈሳዊ ሕይወት ቀጣይነት ያለው የክርስትና ፍሬ ነው፡፡ ክርስትና ለእግዚአብሔር የተለየ አኗኗር በመሆኑ ቃሉን በማጥናት፥ እውቀት በመጨመር፥ በጸሎት እና በጾም በመጽናት፥ መልካሙን ሁሉ በትጋት በማድረግ፥ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል አለብን፡፡
የእግዚአብሔር ሰላም ከሁላችን ጋር ይሁን !!!

Tuesday, March 2, 2021

❖አቢይ ጾም፦

የአቢይ ጾም ሦስቱ ክፍሎች፦

1. ዘወረደ (ጾመ ሕርቃል)፤ ይህም ጾሙ ከሚገባበት ሰኞ ጀምሮ እስከ እሑድ ያረስ ያለው 7 ቀን ነው።

2. የጌታ ጾም፤ ይህም ከቅድስት ሰኞ እስከ ሆሣዕና ዋዜማ ዓርብ ድረስ ያለው 40 ቀን ነው።

3. ሕማማት፤ ይህም ጌታችን በአልዓዛር ቤት ለማዕድ ከተቀመጠበት የሆሳዕና ቅዳሜ ጀምሮ እስከ ሥዑር ቅዳሜ ያለው መከራን የተቀበለበት 8 ቀን ሕማማት ነው።

ይህም 7+40+8 = 55 ቀን ማለት ነው።

«ዘወረደ» ማለት «የወረደ» ማለት ነው፡፡ አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰው አምላክ ሆነ ማለት ነው። ይህም ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳንና ፍቅሩን ሊገልጽልን ከሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም የእኛን ሥጋ መዋሐዱን የሚያዘክር፤ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን የሚያመላክት ፣ የሚታወስበት፣ የሚነገርበት የዐቢይ ጾም አንደኛው ሳምንት ነው፡፡ዮሐ.3-13፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለአዳም በገባዉ ቃልኪዳን መሰረት “ የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ልጁን ላከ” እንዳለ ሐዋርያዉ ቅዱስ ጳዉሎስ የጠፋዉን አዳም ፍለጋ ከአባቱ እሪና ሳይጎድል ሳይለይ ከሰማይ መዉረዱን የምናዘክርበት በዓል ነዉ።

ይህ ጾም የጾም መግቢያ የመጀመሪያ ሳምንት የምንጾመው ጾም ሲሆን ሕርቃል የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለአዳም “ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ በመልዕልተ መስቀል ተሰቅየ አድንኃለሁ” ብሎ ለአዳም ቃል ገባለት ፡፡ ዘፍ. ፫ ፥ ፲፭ ይህ ኪዳነ አዳም ይባላል ፡፡ የቃል ኪዳን ሁሉ መሠረት ነው ፡፡ ሁለቱን ኪዳናት (ብሉይ ወሐዲስ) በፅኑዕ ተስፋ ያስተሳሰረ የረጅም ዘመናት የድኅነት ሰንሰለት ነው ፡፡ ዘወረደ እርቀ አዳም ፤ ተስፋ አበው ፤ ትንቢተ ነቢያት ፤ ሱባኤ ካህናት መፈፀሙ ፤ ኪዳነ አዳም መሲህ መወለዱ የሚነገርበት የፍቅር አዋጅ ነው ፡፡

ዘወረደ ማለት?

 የምስጢረ ሥጋዌ ትምህርት ነው
 ዘወረደ ስንል አምላክ መጣ ፤
 ወረደ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ ፤
 በፍጹም ተዋሕዶ ሰው ሆነ ማለታችን ነው ፡፡
 ዘወረደ በአምላክ ትህትና ክብረ አዳም የሚነገርበት ነው ፡፡
 አምላክ ሰው በመሆኑ ሰው አምላክ ሆነ ፤ ከበረ ፤ ገነነ ፤ ነገሠ ፡፡
 ሕያው አምላክ ክርስቶስ በቅድስት ሞቱ ሟቹን አዳም ዘላለማዊ ሕያው አደረገው ፡፡
 አምላክ ወልደ አምላክ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ሞቶ ለአዳም ያለውን ታላቅ ፍቅር ገለጸ ፡፡
 የተጣላውን አዳምን በፈቃዱ ታረቀው ፡፡
 ጠላቶቹ ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን ፥ ይልቁንም ከታረቅን በኃላ በሕይወቱ እንድናለን ፡፡ ሮሜ. 5 ፥ ፲ ፡፡ በዚህም ትህትናን ፍቅርን አስተማረን ፡፡

የመጀመሪያ የአቢይ ጾም መግቢያ እሁድ ዘወረደ ይባላል ደግሞም ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ስያሜውም፤ በ614 ዓ.ም ኪርዮስ የተባለ የፋርስ ንጉሥ ኢየሩሳሌምን በመውረር ጥቃት አደረሰ፡፡

በዚህ ወቅት በኢየሩሳሌም ንግሥት ዕሌኒ በሠራችው ቤተመቅደስ ውስጥ ሲገባ ንግሥቷ በክብር አስቀምጣው የነበረው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል እንደ ፀሐይ ሲያበራ አገኘው፡፡ ቢነካው አቃጠለው ዲያቆናቱን አሸክሞ ሌላውን ንዋየ ቅድሳት ዘርፎ 60ሺ የሚደርሱትን አቁስሎ ገድሎ 3ሺ የሚሆኑትን ማርኮ ከተማዋንም አቃጥሎ ወደ ፋርስ ባቢሎን ይመለሳል፡፡

በዚህ ጊዜ ከጦርነቱ ያመለጡ በየዋሻው በየጉራንጉሩ ገብተው የተሸሸጉ ተሰብስበው ከ14 ዓመት በኋላ በ628 ጩኸታቸውንና የደረሰባቸውን በደል ለክርስቲየኑ የሮም ንጉሥ ሕርቃል ይነግሩታል፡፡

እርሱም ሐዋርያት ሰውን የገደለ እድሜውን በሙሉ ይጹም ስላሉ እንዴት ላድርገው አላቸው እኛ የአንተን እድሜ ተከፋፍለን እንጾማለን ብለው አንድ አንድ ሳምንት ደርሷቸው ጾሙን በሚገባ ጾመውታል፡፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልና የተማረኩ ክርስቲያኖችን ለመመለስ ሕርቃል ጦር መዝዞ በኪርዮስ ላይ ተነሳበት ድል ለሕርቃል ሆነና መስቀሉን ያለበትን አጥቶ ሲቸገር መስቀሉን ሲቀብርና ዲያቆናቱን ሲያስገድል በመስኮት ሆና ያየችው ከኢየሩሳሌም የተማረከች አንዲት ብላቴና አሳይታው አውጥቶ በልብሰ መንግሥቱ ጠቅልሎ ወደ ቁስጥንጥንያ ተመለሰ፡፡

የተማረኩት በሙሉ ነጻ ወጡ ይህን ለማሰብ ለማስታወስ በተጨማሪ በኃጢአት ላይ ድል እንድናገኝ መንፈሳዊ ጦር በውስጣችን እንዲበዛልን መስቀልህ ከምርኮ እንደተመለሰ እኛንም ከኃጢአት ምርኮ መልሰን ለሕርቃል ድል መንሳትንና በጠላቶቹ ላይ ኃይልን እንደሰጠኸው ለእኛም በኃጢአት ላይ ድል መንሳት መንፈሳዊ ኃይልን ስጠን እያልን እንጾመዋለን፡፡ በ

ጌታ ጾም ላይ እንዲጾም የሆነበት ምክንያት ጾሙ የጌታ ጾም በሚጾምበት ወቅት ላይ ስለተጾመ ቤተክርስቲያናችን አብራ ደንግጋዋለች፡፡እዚህ ላይ በዚያን ጊዜ ለሕርቃል ሕዝቡ ሱባኤ ይዞለታል፡፡ ዛሬም እኛ ለቤተክርስቲያን ያደረግነውን በማሰብ እግዚአብሔር አምላክ ለሕርቃል የሰጠውን በጠላቶቹ ላይ ድል መንሳትን ለእኛም እንዲሰጠን የምንጠይቅበት ስለሆነ የመጀመሪያውን ሳምንት በሕርቃል ሰይመን ጾሙን እንጾማለን፡፡

የእኛ ጠላት የጨለማ ገዥ የሆነው ዲያቢሎስ ነውና እሱን ደግሞ በጾም እንደምናሸንፈው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮናል፡፡

ጾም ስጋችንን ለነፍሳችን የምናስገዛበት ከፈጣሪ ጋር የምንገናኝበት የጽድቅ መንገድ ለስጋ ጤንነትም ቢሆን አስፈላጊያችን የሆነ አንዱና ዋነኛዉ የጽድቅ እቃ ጦራችን ነዉ፡፡

ሆኖም የጾም ወቅት ሲመጣ አቀበት የሚወጡ ይመስል የሚፈሩትና የሚያማርሩት ሳይሆን እንኳን መጣልን ተብሎ በጉጉት የሚናፈቅ መሆን አለበት፡፡ስለሆነም ማንኛዉም ሰዉ ጾሙን ሲጀምር የሚከተሉትን ጉዳዮች በደንብ ሊያጤናቸዉ ይገባል፡፡

የዲያብሎስን ሥራ ሊያፈርስ የተገለጠው የእግዚአብሔር ልጅም በፆም ድል ማድረግን ለእኛ አስተምሮናል። እኛምበዚህ በአብይ ፆም የለመነውና የጠየቅነው ነገር ሁሉ ከኃጢአት በስተቀር እንዲከናወንልን ፆምን ገንዘባችን እናድርግ።


ጾም ጸሎታችን የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይቀበልልን አሜን።
  ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!

Sunday, December 27, 2020

❖ ያለ ክርስቶስ የሆነ ባለ ጠግነት፦

በክርስቶስና ያለ ክርስቶስ የሆነ ባለ ጠግነት፦

1ኛ/ ራዕይ 2:9፦ "መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ ነገር ግን ባለ ጠጋ ነህ።
2ኛ/ ራዕይ 3:17፦ "ሀብታም ነኝና ባለ ጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም የምትል ስለ ሆንህ ጎስቋላና ምስኪንም ድሀም ዕውርም የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ•••"

እግዚአብሔር ባለ ጠጋ የሆነ አምላክ ነው። ከእርሱ ባለ ጠግነት የተነሳ በጎ ስጦታውንና በረከቱን ለሚወዱትና ለሚፈሩት ይሰጣል። በዓለም ብዙ ባለጠግነት አለ። የዚህ ዓለም ባለጠግነት ከንቱ ነው። በባለጠግነቱም ብዛት ነፍሱ ሊያድን የሚችልና የእግዚአብሔርን መንግስት ሊወርስ የሚችል የለም።
(ማቴ 16:26 በማር 10:25)
ሁለት ዓይነት ባለጠግነት በአማኞች ዘንድ እናገኛለን፦
የመጀመሪያው ባለጠግነት በሰምርኔስ አማኞች የተገለጠ ነው። እነዚህ አማኞች በታላቅ መከራና በጥልቅ ድህነት ውሰጥ ሆነው ፍፁም መከራን እየተቀበሉ እሰከ ሞት ድረስ ይታመኑ ዘንድ የበረቱ ናቸው።ምንም መከራ ቢያገኙ ድህነት ቢፈትናቸውም እግዚአብሔር ግን ባለ ጠጎች ናችሁ ይላቸዋል።

ይህ ባለጠግነት፦
1ኛ/ የእምነት ባለጠግነት ነው።መከራና ድህነትን ተቋቁመው በእምነት እግዚአብሔርን እየመሰሉ በፅድቅ የሚኖርበት ነው። "እግዚአብሔር በእምነት ባለ ጠጎች እንዲሆኑ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን መንግስት እንዲወርሱ የዚህ ዓለም ድሆች አልመረጠምን?(ያዕ 2:5)

2ኛ/ መንፈሳዊ በሆኑ ነገሮች ሁሉ ያለ ባለጠግነት ነው።አማኞች የመንፈሳዊ ፀጋ ተካፋዮች ናቸው። ክርስቶስ እሰኪ መጣ ድረስ አንድም የፀጋ ስጦታ አይገድልም። "በነገር ሁሉ በቃልም ሁሉ በእውትም ሁሉ በእርሱ ባለ ጠጎች እንድትሆኑ ተደርጎችኋልና።(1ኛ ቆሮ 1:6)
በክርስቶስ የሆነ ባለ ጠግነት ስጦታ ነው።በእርሱ•••••ተደርገችኋል በማለት የሰውን ሰራና ልፋት ፋይዳ ቢስ ያደርገዋል።

3ኛ/ በማያልፍ በበጎ ስራ ያለ ባለጠግነት ነው።አማኞች በኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል ቤዛነት የፀጋ ሰራ የዳኑ ናቸው። እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካም ስራ በጎ ስራ በእነርሱ ይገለጣል። "በሕያው እግዚአብሔር እንጂ በሚያልፍ ባለጠግነት ተስፋ እንዳያደርጉ,,,,,,,በበጎ ስራ ባለጠጎች እንዲሆኑ ሊረዱና ሊያካፍሉም የተዘጋጁ እንዲሆኑ ምከራቸው። (1ኛ ጢም 6:17-19)
እነዚህ ባለ ጠግነቶች በስምርኔስ አማኞች ታይተዋል።በዓለም ድሆች ሲሆኑ በመንፈሳዊ ነገር ብዙዎችን ባለ ጠጎች የሚያደርጉ ናቸው።2ኛ ቆሮ 6:8 ስለዚህ እግዚአብሔር በስጦታው በአማኞች በሚታየው ደስ ይለዋል።

ሁለተኛው ባለጠግነት ግን አማኞች ነን እያሉ በባለጠግነት አቆጥቁጠው ክርስቶስን ከቤቱ ወደ ደጅ የሚያወጡ ናቸው።

ይህ እግዚአብሔር ደስ አያሰኝም። በሎዶቅያ የታየው ይህ ነው።አንዳች አያስፈልገንም ባለጠጎች ነን በማለት ራስ የሆነውን ክርስቶስ አሰወጡ።ከደጅ ቆሞ ባለጠጋው ደጃቸውን ያንኳኳል። "እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ ። (ራዕ• 3:20)
ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ ከየትኛው ባለጠግነት ዘንድ ነን? እግዚአብሔር ደስ ከሚያሰኘው በእምነት በመንፈሳዊና በበጎ ስራ የሆነ ባለጠግነት? ወይስ ክርስቶስን ወደ ውጭ የሚያደርግ የዚህ ዓለም ባለጠግነት?
ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን!!

Thursday, September 17, 2020

❖ቤተክርስቲያንና አዲስ ዓመት፦


መለወጥ የሌለበት፣ ጸንቶ የሚኖረው እግዚአብሔር ዘመናትን ያፈራርቃል።

ዳንኤል፦ "ጊዜያትንና ዘመናትን ይለውጣል፤.."እንዳለው( ዳን 2፥2) ትናንትን በዛሬ ተክቶ፥ ዛሬን ደግሞ በነገ ያስረጃል፡፡ በጊዜ ዑደትም ውስጥ ብዙ ዓመታት አልፈው ብዙ አዲስ ዓመታት መጥተዋል፡፡ ይህ ሁሉ ቢሆንም እግዚአብሔር በባሕሪው ነበር፤ አለ ይኖራልም።

ዓመታት ሂደው ዓመታት ቢመጡም በእግዚአብሔር ዘንድ በየዓመቱ የሚቀያየር ሀሳብ የሚለዋወጥ አጀንዳ ፈጽም የለም፡፡ ዘላለማዊው እግዚአብሔር በዘላለም እቅዱ መሰረት ሁሉን ያከናውናል። በዕቅዱም መሰረት ይኼው በክርስቶስ ኢየሱስ በልጁ የመስቀል ስራ ሰዎችን ወደራሱ እያቀረበ ነው። በየዘመኑም ይኼን ለማድረግ ይተጋል። ይኼን ሃሳቡንም ለመደምደም በዘመን ፍጻሜ በክርስቶስ ኢየሱስ በሰማይም በምድርም ያለውን ሁሉ ሊጠቀልል አቅዷል። (ኤፌ 1፥10)።

ታዲያ ዘመናት ሲፈራረቁ ሁሉ ነገር ወደ እግዚአብሔር የዘመን ፍጻሜ ዕቅዱ ይፈጥናል። በዚህ መፈራረቅ ውስጥም ለዕቅዱ የወሰናቸው የመረጣቸው በተወሰነላቸው ዘመን እና ቦታ ሁነው ወደልጁ መንግስት ይፈልሳሉ። ለዚያም ነው የዘመናት መፈራረቅ ሰው የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ ዕቅዱን የሚከውንበት እንደሆነ እንዲያስተውል ዕድል የሚሰጥ እንዲሁም በልጁ የሠራውን እንዲያምን፣ እንዲያደንቅ እና መግቦቱንም እንዳይረሳ ያደርጋል የምንለው።

የሰው ልጆች አሮጌ የተባለው ዓመት አልፎ አዲስ ዓመት ሲመጣ እና ከዚህ ጋር በማያያዝ በማቀዳቸው ሕይወታቸው እንደሚለወጥ ያስባሉ ። በእርግጥ የዓመታት መለዋወጥ የሰውን ሕይወት ይለውጣልን? በመሠረቱ ሰዎች ብዙ ነገሮችን ማቀዳቸው ክፉ አይደለም። ለስጋዊ ኑሯቸው ሊጠቅም ይችላል። ነገር ግን ሕይወታቸውን ሊለውጥ አይችልም። የሰውን ሕይወት የጌታ ኢየሱስ የመስቀሉ ስራ እንጂ የሚለዋወጥ ዓመትም ይሁን ይኼን ተከትሎ ሰዎች የሚያቅዱት ዕቅድ አይለውጠውም፡፡

ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ የመስቀል ስራ አምነው ዳግመኛ የተወለዱትን ብልቶቿን ሁሉ የመንፈሳዊ ሕይወት መለወጥ መሻሻልና ማደግ መስራት አለባት፡፡ ይኼን ተግባራዊ ለማድረግም የአሮጌውን ሰው ባህሪ አውልቀው አዲሱን ሰው መልበስ እንዲችሉ በቃሉ አማኞችን ልታንጽ ያስፈልጋል፡፡

ለዚያም ነው ቅዱስ ጳውሎስ፦ «ፊተኛ ኑሯችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ። በአእምሯችሁ መንፈስ ታደሱ፤ ለእውነትም ለሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ።» የሚለው። (ኤፌ 4፥22-24)።

በእርግጥ የአዲሱ ሰው ማንነት በውስጣችን አለ። ጳውሎስ በመልክቱ፦ «አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር ገፍፋችሁታልና፤ የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል እውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታልና» ብሏል። (ቆላ 3፥10)። ነገር ግን ይህ የአዲሱ ሰው ባህርይ ሊገለጥ ሊታይ ይገባል። ይህም ባህርይ ፍቅር፣ ጽድቅ፣ ቅድስና በአጠቃላይ እግዚአብሔርን መምሰል ነው። ቤተክርስቲያን ይኼን ስታደርግ እንደቃሉ በዓለም እንደ ብርሃን ትታያለች።
ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን!!!

Saturday, September 12, 2020

❖የባሕረ ሐሳብ ቊጥር፦

በአብ ስም አምነን አብን ወላዲ ብለን በወልድ ስም አምነን ወልድን ተወላዲ ብለን በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን መንፈስ ቅዱስን ሠራጺ ብለን ምንም ለአጠይቆ አካላት ሦስት ስላልነ በባሕርይ በሕልውና አንድ አምላክ ብለን አምነን ጸሎቱ ልመናው በረከቱ ክብሩ ይደርብንና የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ድሜጥሮስ የተናገረውን የባሕረ ሐሳብ ቊጥር መጽሐፍን በእግዚአብሔር አጋዥነት እንጀምራለን፡፡


💥 እግዚአብሔር እንደዛሬው ኹሉ አንድነቱ ሦስትነቱን ሳይጠቀልለው ሦስትነቱ አንድነቱን ሳይከፍለው በአንድነት በሦስትነት ሳለ ክብሩ በብቻው እንደቀረ ዐውቆ ዓለምን ልፍጠር ብሎ አሰበ፤ አስቦም አልቀረ ሰውና መላእክትን ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ የቀረውን ፍጥረት ግን ለአንክሮ ለተዘክሮ ለምግበ ሥጋ ለምግበ ነፍስ ፈጠረ። 

    “ወኲሉ ዘተፈጥረ ለመፍቅደ ነባብያን ቦ እምኔሆሙ ለምህሮ ወቦ እምኔሆሙ ለተገብሮ፤ ወእንዘ ኢየኀድግ ርእሶ ዘእንበለ ሰማዕት፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘንተ እምአፍአ ብከ ሰማዕት ወመምህር ዘይመርሐከ ኀበ ዝንቱ፤ ወዘኢያስተርኢ እግዚአብሔር እምፍጥረተ ዓለም ይትዐወቅ በፍጥረቱ” እንዲል።


💥 እግዚአብሔርስ የፈጠረው ፍጥረት እያንዳንዱ ቢቈጠር ፍጡር ተናግሮ ባልፈጸመውም ነበር፤ እየወገን እየወገኑ ግን ብዙውን አንድ ብዙውን አንድ እያሉ ቢቈጥሩ ከእሑድ እስከ ዐርብ የፈጠረው ሥነ ፍጥረት 22 ነው፡፡ እስከዚኽ አርዕስት ነው፤ ይኽንንም በሥነ ፍጥረት ይመለከቷል። 

የፀሓይ ጥንታት ሦስት የጨረቃን ዐምስት የሚል ነውና፤ ይኽ ዓለም የተፈጠረበት ዕለተ እሑድ ጥንተ ዕለት፤ አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፀዋት የተፈጠሩበት ዕለተ ሠሉስ ጥንተ ቀመር፤ ብርሃናት የተፈጠሩበት ዕለተ ረቡዕ ጥንተ ዮን ይባላል፤ “እሑድ ወሠሉስ ወረቡዕ ዘውእቶሙ ሠለስቱ ጥንታት” እንዲል


💥 ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ዘመን ቢቈጠር በፀሓይ 7513 ዘመን፤  በጨረቃ 7743 ዘመን ከ7 ወር ከ16 ዕለት ነው፡፡ 


💥 ከልደተ ክርስቶስ አስቀድሞ የነበረው በፀሓይ 5500 ዘመን፤ በጨረቃ 5668 ዘመን ከ10 ወር ከ9 ዕለት ነው፤ ይኽም  ዓመተ ኩነኔ፣ ዓመተ ፍዳ ይባላል፡፡


💥 ከልደተ ክርስቶስ ወዲኽ ያለው ግን በፀሓይ 2013 ዘመን፤ በጨረቃ 2074 ከ9 ወር ከ7 ዕለት ነው።  ይኽ ዓመተ ሥጋዌ፣ ዓመተ ምሕረት ይባላል፤ መላው ዓመተ ዓለም ነው፤ ዓመተ ዓለም ባለው ዓመተ ምሕረት የሚል ይገኛል፤ ጊዮርጊስ ወልደ አሚድም ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት ብሎ ተርጒሞታል፤ ስለምን ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት አለው ቢሉ? ሰው በዚኽ ዓለም ሳለ ኀጢአት ሠርቶ ንስሓ ቢገባ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረት የሚያገኝበት ስለኾነ ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት ብሎ ተርጒሞታል “በዕለት ኅሪት እሰምዐከ ወበዕለተ መድኀኒት እረድአከ ወናሁ ይእዜ ዕለት ኅሪት ወናሁ ዮም ዕለተ አድኅኖት” እንዲል፡፡


💥 ለዚኹም መሥፈሪያ ሰባት አዕዋዳት አሉት፤ ምንና ምን ቢሉ? ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ፀሓይ፣ ዐውደ ማኅተም፣ ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡ ከሊኹም ሦስቱ በዕለት አራቱ በዓመት ይቈጠራሉ፤ በዕለት የሚቈጠሩት ሦስቱ ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት ናቸው፤ በዓመት የሚቈጠሩ አራቱ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ፀሓይ፣ ዐውደ ማኅተም፣ ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡ ዐውደ ዕለት ከእሑድ እስከ ቀዳሚት ያሉ ሰባት ዕለታት ናቸው፤ እሊኽም አውራኅን ለማስገኘት በሰባት በሰባት ሲመላለሱ ይኖራሉ “እስመ ኊልቊ ሳብዕ ፍጹም ውእቱ በኀበ ዕብራውያን ” እንዲል። 


💥 ዐውደ ወርኅ በፀሐይ ዘወትር ፴ በጨረቃ አንድ ጊዜ 29፤ አንድ ጊዜ ፴ ይኾናል፤ እሊኽም ዓመታትን ለማግኘት በ፴ በ፴ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡


💥 ዐውደ ዓመት በፀሓይ 365 ዕለት በጨረቃ 354 ዕለት ነው፤ በፀሓይማ ምነው 365 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልኢት፤ በጨረቃ 354 ዕለት ከ22 ኬክሮስ ከ1 ካልዒት ከ37 ሣልሲት ከ52 ራብዒት ከ48 ኀምሲት አይደለውም ቢሉ “ወበውስተ ውሁድኒ ንብል አልቦ ወኢአሐዱ” እንዲል መጽሐፍ ትርፍን  ትቶ ጐደሎን  መልቶ መቊጠር ልማድ ነውና ፷ ካልመላ ብሎ እንዲኽ አለ እንጂ ቊጥሩስ አለ።  “እስመ ልማደ መጽሐፍ ይነግር ኊልቈ ምሉዓ ወፍጹመ ወየኀድግ ዘተርፈ ወይዌስክ ዲበ ሕፀፅ ካልዐ” እንዲል፤  ዕለታትን አዕዋድ አላቸው አውራኅን የሚያስገኙ ስለኾነ፤ አውራኅን አዕዋድ አላቸው ዓመታትን የሚያስገኙ ስለኾነ።  “ወበከመ ይትወለዳ አውራኅ እምዕለታት ወዓመታት እምአውራኅ ከማሁ ይትወለዳ አዕምሮታት እመከራት ወእምግባራት እንዲል፡፡


💥 ዐውደ አበቅቴ 19 ዓመት ነው።  በዚኽም  ፀሓይና ጨረቃ መንገዳቸውን ፈጽመው በተፈጠሩበት ኆኅት ይገናኙበታል፤ ሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ መምህራነ ወንጌል ሐዋርያት፣ ሊቀ ጳጳሳት ዲሜጥሮስ ከ፳ው አንድ ቀመር አንድ ተረፈ ቀመር፤ ከ፵ው ኹለት ቀመር ኹለት ተረፈ ቀመር፤ ከ፷ው 3 ቀመር 3ት ተረፈ ቀመር፤ ከ፹ው 4 ቀመር 4ት ተረፈ ቀመር፤ ከ፻ው 5ቀመር 5ት ተረፈ ቀመር እያላችኊ ቊጠሩ ማለታቸው ከዚኽ የተነሣ ነው።  “ወእምዘተርፈከ እምዐሠርቱ ወተሰዓቱ ተአትት እምኔሁ አሐደ ዓመተ እስመ ለዛቲኒ ዐሠርቱ ወተሰዓቱ ሙሴ ገብራ በጥበበ እግዚአብሔር ዘይገብሩ ባቲ ፍሥሐ አይሁድኒ ወክርስቲያንኒ” እንዲል። 


💥 ዐውደ ፀሓይ 28 ዓመት ነው፤ በዚኽ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፤ ዕለቱ ረቡዕ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ነው፤ ረቡዕ ማቴዎስ እንዲል፤ ዕለትን ፀሓይ አለው “ወበትእዛዝከ ይቀውም ዕለት” እንዲል፤ ወንጌላዊዉን ፀሓይ አለው “አንትሙ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም” ካለው አንዱ ርሱ ነውና፤ በሰንጠረዥ ፀ፣ ደ ይላል፤ ዐውደ ፀሓይ ማለት ነው፡፡


💥 ዐውደ ማኅተም 76 ዘመን ነው፤ በዚኽ አበቅቴ ወንጌላዊ ይገናኙበታል፤ አበቅቴው 18 ወንጌላዊዉ ዮሐንስ ነው፤ ማኅተም አለው አበቅቴው ለአበቅቴ ወንጌላዊዉ ለወንጌላዊው ፍጻሜ ነውና፡፡ ዐውደ ቀመር 532 ዘመን ነው፤ በዚኽ ዕለት፣ ወንጌላዊ፣ አበቅቴ እሊኽ 3ቱ ይገናኙበታል፤ ዕለቱ ሠሉስ፣ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ነው፤ ሠሉስ ማቴዎስ እንዲል አበቅቴው አልቦ ነው “ጥንቱ ለቀመር ዕለተ ሠሉስ ወንጌላዊ ማቴዎስ ወፍጻሜሁ ዕለተ ሰኑይ ወንጌላዊ ዮሐንስ” እንዲል።


💥 በዐውደ ፀሓይ ቦታ ዐውደ ማኅተም፤ በዐውደ ማኅተም ቦታ ዐውደ ፀሓይ የሚል ይገኛል፤ ከኹለቱ አንዱ ቢታጣ አንዱ ከቀመር ገብቶ ይቈጠራል፤ ቀመርን ለሦስቱ ስም በሰጡ ጊዜ ዐውደ ቀመር ዐቢይ ቀመር፤ ዐውደ ማኅተም ማዕከላዊ ቀመር፤ ዐውደ አበቅቴ ንዑስ ቀመር ይባላል፤ ዐቢይ ቀመር መደቡ 14 ቊጥሩ 532፣532፤ ማዕከላዊ ቀመር መደቡ 6 ቊጥሩ 76፣76፤ ንዑስ ቀመር መደቡ 3 ቊጥሩ 19፣19 ነው፡፡


💥 ከዚኽም ዓመተ አበቅቴን ለማግኘት 7513 ዘመን በዐቢይ ቀመር ቢቀምሩ 532፤ 532 የተፈጸመለት 14 ዐቢይ ቀመር፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኾኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡ 


💥 መላውንም በማእከላዊ ቀመርም ቢቀምሩ 76፤ 76 የተፈጸመለት 98 ማእከላዊ ቀመር 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኹኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡ 


💥 በዐውደ ፀሓይም ቢቀምሩ 28፤ 28 የተፈጸመለት 266 ዐውደ ፀሓይ፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኾኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡ 


💥 መላውንም በንዑስ ቀመር ቢቀምሩ 19፤ 19 የተፈጸመለት 395 ንዑስ ቀመር ኹኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡


💥 7513ኙን ዘመን በቀመረ ዐረብም ቢቀምሩ 228፤ 228 የተፈጸመለት 32 ቀመረ ዐረብ፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 11 ንዑስ ቀመር ኹኖ 8 ዓመት ይተርፋል፤ ስመ አቅማር ብዙ ነው አይቶ መተው ነው፤ አሐደ አዕትት ለዘመን እንዲል ስለተጀመረ ተቈጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ ብሎ ከ8ቱ አንዱን ቢያትቱ 7 ይተርፋል፤ 7 ወንበር (ዓመተ አበቅቴ)ወጣ ይሏል በዘመነ ማቴዎስ።

💥 አበቅቴን ለማግኘት ከ7ቱ ዓመተ አበቅቴ 11 ቢሄዱ፤ 77 ይኾናል፤ 60ውን በ2 ፴ ቢገድፉት 17 ይተርፋል፤ 17 አበቅቴ ወጣ በዘመነ ማቴዎስ፡፡ 


💥 መጥቅዕንም ለማግኘት ከ7ቱ ዓመተ አበቅቴ 19 ዕለት ቢሄዱ 133 ይኾናል፤ 120ውን በ4 ፴ ቢገድፉት 13 ይቀራል፤ 13 መጥቅዕ ወጣ በዘመነ ማቴዎስ፡፡ 


💥 13 መጥቅዕና 17ት አበቅቴ ፴ ይኾናሉ እንጂ ከ፴ አይወጡም ከ፴ አይወርዱም፤ “ዓዲ መጥቅዕ ወአበቅቴ ክልኤሆሙ እመ ይበዝኁ ወእመ ይውኅዱ ኢየዐርጉ እም፴ ወኢይወርዱ እም፴ ወባሕቱ ወትረ ይከውኑ ፴” እንዲል። 

            

💥 ከዚኽም በዘመኑ የኾኑ አጽዋማትና በዓላትን ይናገሯል፤ መጥቅዕ 13 ነው።  መጥቅዕ ቢያንስ በጥቅምት ይውላልና፤ ጥቅምት እሑድ ይብታል፤ ከእሑድ እስከ እሑድ 8፤ ሰኞ 9፤ ማግሰኞ 10፤ ረቡዕ 11፤ ኀሙስ 12፤ ዐርብ 13፤ በዐለ መጥቅዕ ጥቅምት 13 ዐርብ ቀን ይውላል፤ የዐርብ ተውሳክ 2፤ 2 እና 13= 15 መባጃ ሐመር ይገኛል፤ በጥቅምት ሳኒታ የካቲት ሰኞ ይብታል፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 8፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 15፡፡ የካቲት 15 ሰኞ ነነዌ ይውላል፡፡


♦ የዐቢይ ጾም ተውሳክ 14፤ 14 ና 15 =29፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 8፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 15፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 22፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 29 የካቲት 29 ቀን ዐቢይ ጾም፡፡


♦ የደብረ ዘይት ተውሳክ 11፤ 11 ና 15= 26፤ መጋቢት ረቡዕ ይብታል፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 8፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 15፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 22፤ ኀሙስ 23፤ ዐርብ 24፤ ቅዳሜ 25፤ እሑድ 26፤ መጋቢት 26 ቀን ደብረ ዘይት፡፡


♦ የሆሳእና ተውሳክ 2፤ 2 እና 15=17፤ ሚያዝያ ዐርብ ይብታል፡፡ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 15፤ ቅዳሜ 16፤ እሑድ 17 ይብታል፡፡ ሚያዝያ 17 ሆሳዕና 


♦ የስቅለት ተውሳክ 7፤ 7 እና 15=22፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 15፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 22፡፡ ሚያዝያ 22 ስቅለት፡፡ 


♦ የትንሣኤ ተውሳክ 9፤ 9 እና 15= 24፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 15፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 22፤ ቅዳሜ 23፤ እሑድ 24፡፡ ሚያዝያ 24 ትንሣኤ 


♦ የርክብ ተውሳክ 3፤ 3 እና 15=18፤ ግንቦት እሑድ ይብታል፤ እሑድ እስከ እሑድ 8፤ እሑድ እስከ እሑድ 15፤ ሰኞ 16፤ ማግሰኞ 17፤ ረቡዕ 18፤ ግንቦት 18 ርክበ ካህናት፡፡


♦ የዕርገት ተውሳክ 18፤ 18 እና 15= 33፤ ፴ውን ገድፎ 3 ይቀራል፤ ሠኔ ማክሰኞ ይብታል፤ ማክሰኞ 1፤ ረቡዕ 2፤ ኀሙስ 3፤ ሠኔ 3 ዕርገት፡፡


♦ የጰራቅሊጦስ ተውሳክ 28፤ 28 እና 15= 43፤ ፴ውን ገድፎ 13 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ረቡዕ 9፤ ኀሙስ 10፤ ዐርብ 11፤ ቅዳሜ 12፤ እሑድ 13፤ ሠኔ 13 በዓለ ጰራቅሊጦስ፡፡


♦ የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ 29፤ 29 እና 15=44፤ ፴ውን ገድፎ 14 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ማግሰኞ እስከ ሰኞ 14፤ ሠኔ 14 ጾመ ሐዋርያት፡፡ 


♦ የጾመ  ድኅነት ተውሳክ 1፤ 1 ና 15= 16፤ ማክሰኞ እስከ ማክሰኞ 8፤ ማክሰኞ እስከ ማክሰኞ 15፤ ረቡዕ 16፤ ሠኔ 16 ጾመ ድኅነት ይውላል፡፡


💥 ዓመተ ወንጌላዊን ከዚኽ ይናገሯል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዓመተ ወንጌላዊ ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ ለእመ ተርፈ አሐዱ ማቴዎስ ወክልኤቱ ማርቆስ ወሠለስቱ ሉቃስ ወለእመ ዐረየ ክፍል ዮሐንስ እንዲል፤ ዓመተ ወንጌላዊን ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ አንድ ቢተርፍ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ መኾኑ፤ ኹለት ቢተርፍ ማርቆስ፤ ሦስት ቢተርፍ ሉቃስ ቢተካከል  መኾኑን በዚኽ ይታወቃል፤ 7513 ዘመን ለአራቱ ወንጌላውያን ቢያካፍሉ 1878 ደርሷቸው 1 ይተርፋል፤ 1 ቢተርፍ ማቴዎስ ያለው ይኽ ነው፤ ዛሬ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ መኾኑ በዚኽ ታውቋል፡፡


💥 ጥንተ ዮንንም ከዚኽ ይናገሯል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ጥንተ ዮን ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ ወትዌስክ ቦቱ መጠነ ራብዒት ወትገድፎ በበሱባኤ ወዘተርፈከ እምሱባኤ ተአትት እምኔሁ አሐደ ዓመተ ወእምዝ ይከውን ጥንተ ዮን እንዲል፤ ጥንተ ዮንንም ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ 5ኛ መጠነ ራብዒት 6ኛ ጳጉሜንን አክሎ በሱባዔ ገድፎ ከሱባዔ የተረፈውን አንዱን አትቶ 1 ቢተርፍ ጥንተ ዮን ረቡዕ መኾኑን መስከረም ረቡዕ መባቱን፤ 2ት ቢተርፍ ኀሙስ፤ 3 ቢተርፍ ዐርብ፤ 4 ቢተርፍ ቀዳሚት፤ 5 ቢተርፍ እሑድ፤ 6 ቢተርፍ ሰኞ፤ 7 ቢተርፍ ማግሰኞ መኾኑ በዚኽ ይታወቃል፡፡ አከፋፈል እንዳለፈው።


💥 7513 ዘመን ለአራቱ ወንጌላውያን ቢያካፍሉ 1878 ደርሷቸው 1 ይተርፋል፤ ይኽን በሱባዔ ይገድፏል፤ ከሺው 300 ነሥቶ 700 ግዱፍ፤ ከ800ው አንዱን መቶ ነሥቶ 700 ግዱፍ፤ 400 ይተርል፤ ከ100ው 2፤ ከ400ው 8፤ ከ8ቱ አንድ፤ ከዚያም 1 እና 78= 79 ይኾናል፤ ከ79ኙ 70ውን በ11 ሱባዔ ቢገድፉ 2 ይተርፋል፡፡


💥 ከአንዱ ወንጌላዊ 2 ከ4ቱ ወንጌላውያን 8፤ መጠነ ራብዒት፤ 6ኛ ጳጉሜን 1878 ዕለት ትኾናለች፤ ርሷ በዕለት፤ ወንጌላዊ በዓመት ይተካከላሉና ግድፈት እንዳለፈው፤ መጠነ ራብዒት  2= 10፤ ከዓመተ ወንጌላዊ የተረፈ 1 ና 10= 11 ይኾናል፤ ከ11ዱ 7ቱን በአንድ ሱባዔ ቢገድፉ 4 ይተርፋል፤ አሐደ አዕትት ለዘመን እንዲል ስለተዠመረ ተቈጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ ብሎ ከ4ቱ አንዱን ቢያትቱ 3 ይተርፋል፤ 3 ቢተርፍ ዐርብ ያለው ይኽ ነው፤ የዐርብ ጥንተ ዮን 3 ነውና፡፡ ጥንተ ዮንም ማለት ጥንተ ፀሓይ፤ ጥንተ ጨረቃ፤ ጥንተ ከዋክብት ማለት ነው፤ ጥንተ ዮን ብሂል ጥንተ ተፈጥሮቶሙ ለፀሓይ፤ ወወርኅ ወከዋክብት እንዲል፡፡


💥 ዕለተ ቀመርንም ለማወቅ ለጥንተ ዮን ከወጣው አንዱን ሳያትቱ በሱባዔ ገድፎ 1 ቢተርፍ ማግሰኞ መኾኑ፤ 2 ቢተርፍ ረቡዕ፤ 3 ቢተርፍ ኀሙስ፤ 4 ቢተርፍ ዐርብ፤ 5 ቢተርፍ ቀዳሚት፤ 6 ቢተርፍ እሑድ፤ 7 ቢተርፍ ሰኞ መኾኑ በዚኽ ይታወቃል፤ ለጥንተ ዮን የወጣው 4 ነው፤ 4 ቢተርፍ ዐርብ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ቀመርም ማለት ቀመር የተዠመረበት ዕለት ማለት ነው፤ ቀመር የተዠመረው ማግሰኞ ነውና፡፡


💥 ዕለተ ዮሐንስንም ከዚኽ ይናገሩታል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዕለተ ዮሐንስ ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ፤ ወትዌስክ ቦቱ መጠነ ራብዒት፤ ወክልዔተ ዕለተ ጠቢባን ወትገድፎ በበሱባዔ ወዘተርፈከ እምሱባዔ ኢተአትት አሐደ ዓመተ፤ ወእምዝ ይከውን ዕለተ ዮሐንስ እንዲል ዕለተ ዮሐንስን ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ፤ 5ኛ መጠነ ራብዒት፤ 6ኛ ጳጉሜንን አክሎ 7ኛ 2ት ዕለተ ጠቢባንን ጨምሮ በሱባዔ ገድፎ ከሱባዔ የተረፈውን አንዱን ሳያትቱ አንድ ቢተርፍ ዕለተ ዮሐንስ እሑድ መኾኑ፤ 2 ቢተርፍ ሰኞ፤ 3 ቢተርፍ ማግሰኞ፤ 4 ቢተርፍ ረቡዕ፤ 5 ቢተርፍ ኀሙስ፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ፤ 7 ቢተርፍ ቀዳሚት መኾኑ በዚኽ ይታወቃል።


💥 ለጥንተ ዮን የወጣ 4 እና 2 ዕለተ ጠቢባን= 6 ይተርፋል፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ዮሐንስም ማለት አሻቅቦ ወደ ላይ እስከ ፍጥረተ ዓለም፤ አቈልቊሎ ወደ ታች እስከ ምጽአተ ክርስቶስ ቢቈጥሩ ለወንጌላዊዉ ዮሐንስ የሚደርሰው ቀን ማለት ነው፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘኀለፈ ይመርሐከ ዝንቱ እስከ ፍጥረተ ዓለም ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘይመጽእ ያበጽሐከ ዝንቱ እስከ ምጽአተ ክርስቶስ እንዲል፤ አንድም ሠርቀ ቲቶን ዕለተ ዮሐንስ ይለዋል፤ ቲቶ የተባለው መስከረም ነው፤ የመጥምቁ ዮሐንስ በዓል የሚውልበት ቀን ማለት ነው፤ ርዕሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ እንዲል፡፡


💥 ዕለተ በዓል ዘኀለፈ ዕለተ በዓል ዘይመጽእ የእሑድ አሚሩ ሰንበተ ክርስቲያንን ለማወቅ በዘመኑ የወጣውን ጥንተ ዮን፤ ሠርቀ መዓልት፤ 2 ዕለተ ጠቢባን በየወሩ የሚገኘውን አጽፈ ወርኅ እሊኽን 4ቱን አንድ አድርጎ ቈጥሮ በሱባዔ ገድፎ 1 ቢተርፍ እሑድ አሚሩ፤ 2 ቢተርፍ ሰኞ ሰኑዩ፤ 3 ቢተርፍ ማግሰኞ ሠሉሱ፤ 4 ቢተርፍ ረቡዕ ረቡዑ፤ 5 ቢተርፍ ኀሙስ ኀሙሱ፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ሰዱሱ፤ 7 ቢተርፍ ቀዳሚት ሰቡዑ፤ 8 ቢተርፍ በሱባዔ ገድፎ እሑድ አሚሩ የሚያሰኘው ይኽ ነው፡፡ 


💥 አጽፈ ወርኅም ማለት የወርኁ ከወርኅ የሚደረብ ማለት ነው፤ ይኽስ ከምን ይገኛል ቢሉ? ወሩን በሱባዔ ቢገድፉ 4 ሱባዔ ኾኖ 2 ይተርፋል፤ የወርኁ 2 የዓመቱ 24፤ እንዲኽ ግን ስለኾነ ለመስከረም አጽፈ ወርኅ የለውም በጥንተ ዮን፤ በሠርቀ መዐልት በኹለት ዕለተ ጠቢባን ይቈጠራል፤ በእሊኽ በ3ቱ ይቈጠራል፤ ጥንተ ዮን 3፤ ሠርቀ መዐልት 1=4፤ ኹለት ዕለተ ጠቢባን 2፤ 6 ይኾናል፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ሰዱሱ ያለው ይኽ ነው። 


💥 ዕለተ ጠቢባንም ማለት ጠቢባን ሥላሴ ይኽነን ዓለም የፈጠሩበት፤ ጠቢባን መላእክት ሥላሴን የሚያመሰግኑበት ቀን ማለት ነው፤ (ዬ) ጠቢባን ሥላሴ ይኽነን ዓለም ከእሑድ እስከ ዐርብ ፈጥረዋል፤ ጠቢባን መላእክት ሥላሴን ዘወትር ያመሰግናሉ ብሎ የቊጥር መጽሐፍን የተማሩ መምህራን ዕለተ ሰንበትን፤ 6ቱ ዕለታትን፤ ያለፉትን የሚመጡትን በዓላት የሚያውቁባቸው የሚያሳውቁባቸው ማለት ነው፤ ዕለተ ጠቢባንም የተባሉ እሑድና ሰኞ ናቸው፤ ከቀመር ገብተው አልተቈጠሩም፡፡


💥 ዕለተ ምርያ አዕዋዲትንም ለማወቅ የፀሓይ ዐውደ ዓመት 365 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ነው፤ ይኽነን በሱባዔ ቢገድፉት 52 ሱባዔ ኾኖ 1 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ይተርፋል፤ ይኽቺውም አንድ ዕለት የተባለችው ዐምስተኛዪቱ ጳጒሜን ናት፤ ዕለተ ምርያ አዕዋዲት ይላታል፤ ዕለተ ምርያ ማለት ዕለተ መድኀኒት ማለት ነው፤ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበትን ቀን የምታሳውቅ ማለት ነው፤ ርሷ በዋለች ልደት ይውላልና፤ አዕዋዲትም አላት ዘመኑን የምታዘዋውር የምታለዋውጥ ማለት ነው፤ እሑድ የዋለውን ሰኞ፤ ሰኞ የዋለውን ማግሰኞ እንዲውል የምታደርግ ርሷ ናትና፡፡


💥 መጠነ ራብዒት 6ኛ ጳጉሜንም ለማወቅ የአንዱ ዓመት ኬክሮስ 15፤ የ2 ዓመቱ 30፤ የ4 ዓመቱ 60 ኬክሮስ ነው፤ 60ው ኬክሮስ 1 ዕለት ይኾናል፤ ይኽቺውም በሉቃስ መጨረሻ ዮሐንስን ተጠግታ የምትውል ስድስተኛዪቱ ጳጉሜን ናት፤ መጠነ ራብዒት፣ ሠግረ ዮሐንስ ይላታል፤ መጠነ ራብዒት አላት ርሷ በዕለት ወንጌላዊ በዓመት ይተካከላሉና፤ ሠግረ ዮሐንስም አላት ዮሐንስ ተራምዶ የሚውልባት ስለኾነ፡፡


💥 ዕሪና መዓልትና ዕሪና ሌሊትን ሰባተኛዪቱን ጳጉሜን ለማወቅ የአንዱ ዓመት ካልዒት 6፤ የ5ቱ ዓመት 30፤ የ10ሩ ዓመት 60 ይኾናል፤ 60ው ካልዒት 1 ኬክሮስ ይኾናል፤ የ100ው ዓመት 10 ኬክሮስ፤ የ600 ዓመት 60 ኬክሮስ፤ 60ው ኬክሮስ አንድ ዕለት ይኾናል፤ ይኽቺውም ሰባተኛዪቱ ጳጉሜን ናት፤ ዓለም በተፈጠረ በ600 ዘመን ዕሪና መዓልት ዕሪና ሌሊት ኾኗል፤ ዓለም ከተፈጠረ ዠምሮ እስከ ዛሬ ድረስ 12 ዕሪና መዓልት 12 ዕሪና ሌሊት ኾኖ 13ኛው ከተዠመረ 313 ኾኖ በዘመነ ማቴዎስ ይኸውም ሊመላ 287 ይቀራል፡፡

ከዚኽ በኋላ እንዲኽ ብሎ ባሕረ ሐሳብ አውጪው እንዲኽ ብሎ አሥርቆት ያውጣ፡፡


💥 በዘንዜከር ሐሳባተ ሕጉ ወትእዛዙ ለእግዚእነ ወአምላክነ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዘ ሀሎነ በዘመነ ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ዘመነ ማርቆስ ዜናዊ፤ ወንጌላዊ አለው ማቴዎስን ባለዘመን ነውና፤ ዜናዊ አለው ማርቆስን የሚመጣ ነውና ወረኛ ንጉሥ እንዲሉ፡፡ በሰብዐ ወኀምስቱ ምእት ዐሡሩ ወሠሉሱ ዓመተ ዓለም፡፡ በኀምሳ ወኀምስቱ ምዕት ዓመተ ዓለም፤ በዕሥራ ምዕት ዐሡሩ ወሠሉሱ ዓመተ ምሕረት፤ ሠረቀ ለነ ወርኀ መስከረም ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ወርኀ ጥቅምት በሰላመ እግዚአብሔር አሜን፤ አበቅቴ 17 ሠርቀ መዓልት 1፤ ሕጸጽ 1= 19፤ ዐሡሩ ወተሱዑ ሠርቀ ሌሊት፤ ዕሥራ ወሡሉሱ ሠርቀ ወርኅ፤ አሚሩ ሠርቀ መዓልት፤ ሰዱሱ ሠርቀ ዕለት፤ ዮም በዛቲ ዕለት ዘአቅረብነ ለከ አምኀ ስብሐት ያዐርጉ ለነ መላእክት ተወከፍ ለነ እግዚአ ስብሐት። 

             ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!