Sunday, June 9, 2019

❖የጠፋው ልጅ፦

✞📖የጠፋው ልጅና የእግዚአብሔር ፍቅር!

    💌በአዲስ ኪዳን ውስጥ ከተዘገቡልን ድንቅ ምሳሌዎች አንዱ የጠፋው ልጅ ምሳሌ ነው። የጠፋውን ልጅ ታሪክ ስናነብ በእንባ እንሞላለን። ጽድቅ ሳለ ኩነኔ፣ ዕረፍት ሳለ ሁከትን መርጦ ለሚቅበዘበዘው የሰው ልጅ የፍቅር ዕንባ እንድናፈስ ያደርገናል። ከሁሉ በላይ ግን የጠፋው ልጅ አባት ፍቅር በዕንባ እንድንታጠብ ያደርገናል። ወደ እርሱ አንድ እርምጃ ሲመጡ አስር እርምጃ ወደ ጠፉት የሚመጣ፣ ሂሳብ ለመተሳሰብ የማይሻ፣ ተበደልኩ ሳይሆን ተጎዳችሁ ብሎ የሚያለቅስ ፣ ከነ ቆሻሻ የሚያቅፍ ፣ ልብስን ታሪክን የሚለውጥ ያ አባት ፍቅሩ ያስለቅሳል።

    📝 የጠፋው ልጅ ታሪክ የፈጠራ ድርሰት ወይም የሩቅ ዘመን ሀቅ አይደለም። የጠፋው ልጅ እኛ ነን። ወይ ጠፍተን እየተጎዳን ነው አሊያም የተገኘን ነን። በጠፋው ልጅ ታሪክ ላይ ደርበን ከመጻፍ ውጭ የግርጌ ማስታወሻ መያዝ አንችልም። የታሪካችን ማስታወሻ ምውትነት ነው። ለዚህ ነው ሐዋርያው፦ "በበደላችሁና በኃጢያታችሁ ሙታን ነበራችሁ" የሚለወ(ኤፌ.2፥1)።  ሞትን በነበር ያስቀረልን የሕይወት ራስ የሆነው ክርስቶስ ነው። የተፈቀረው ይህ ምውት ማንነት ነው። ምውትን ማን ይቀርበዋል? ቅድም ስንዳብሰው ቆይተን ሲሞት ሬሳው ብለን እንሸሸዋለን። እኛን የወደደ ቡሩክ ነው!

   "የጠፋው ልጅ ነበርኩ እጅግ ቀበዝባዛ፣
    የነፍሴ መድኃኒት ኢየሱስ ሆነኝ ቤዛ"
እያልን ከመዘመር ውጭ ሌላ ቃል የለንም።

     📝ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ስለ መጥፋት በብዙ ይጽፋል። የሉቃስ ወንጌል መሪ ጥቅስም፦ "የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአልና" የሚል ነው(ሉቃ.19:10)።  ሉቃስ ይባስ ብሎ ስለ ጠፋው ኢየሱስ ጽፏል(ሉቃ.2:41-51)።  ያለ ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ቀን መጓዝ እርሱን ለማግኘት ሦስት ቀን ያንከራትተታል። መጸለይን፣ ኅብረት ማድረግን ለአንድ ቀን መተው ሰላሙን ለመመለስ ሦስት ቀን ይፈጃል።

💌ወንጌላዊው ሉቃስ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣበትን ዓላማ ሲገልጥ፦ "የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቷልና" ብሏል(ሉቃ.19:20)። ታዲያ በምዕራፍ 15 ላይ ስለ ጠፊዎች ወይም ስለ ጠፉ ወገኖች በሙሉነት ይተርካል።  የጠፋው በግ፣ የጠፋው ድሪም(ገንዘብ)፣ የጠፋው ልጅ።
የጠፋው በግ በደጅ፣ የጠፋው ድሪም በቤት፣ የጠፋው ልጅ በሩቅ አገር ነው። የጠፋው በግ በሞኝነት፣ የጠፋው ድሪም አለሁ እያለ በመሞት፣ የጠፋው ልጅ በምርጫ ነው። የጠፋው በግ አለማውያንን ይመለከታል። ባለ ማወቅና በሞኝነት ጠፍተዋል። መመለሻውን አጥተው የሚንከራተቱ ምስኪኖች ናቸው። የጠፋው ድሪም ግን ያለሁት እዚሁ ነው ብሎ መጥፋቱን ማወቅና ማሳወቅ አይችልም። የጠፋውም በደጅ ሳይሆን በቤት ውስጥ ነው። በእግዚአብሔር ቤት የጠፉ፣ አለን እያሉ ተበልተው ያለቁትን አገልጋዮችና ምዕመናንን ይመለከታል።

   "በአደባባይ ቆሜ ስምህን ከመስበክ
     መጀመሪያ ልቤ ለፍቅርህ ይንበርከክ
     ከአገልግሎት በፊት አንተን ልወቅህ
     መሥዋዕት ከማቅረብ ልታዘዝልህ"
ማለት ይሻላል።

     📖የጠፋው ልጅ የጌታን ሰላም ቀምሶ ፣ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተካፍሎ፣ በሰላሙ አርፎ የነበረ ምዕመንን ይገልጣል። ይህ ምዕመን ግን ትንሹ ሰላምን ዕረፍት ለዘላለም የሚኖር መስሎት በቃኝ ብሎ ሄዷል። ጸጋም ያልቃል። ጸጋው ቀጣይ የሚሆነው ባለጸጋውን ጌታ ስንይዝ ብቻ ነው። የጠፋው ልጅ እኛው ነን።

   📝 ሉቃስ ትረካውን በድንቅ ይጀምራል።

" እንዲህም አለ፦ አንድ ሰው ሁለት ልጆች ነበሩት። ከእነርሱም ታናሹ አባቱን፦ አባቴ ሆይ፥ ከገንዘብህ የሚደርሰኝን ክፍል ስጠኝ አለው። ገንዘቡንም አካፈላቸው። ከጥቂት ቀንም በኋላ ታናሹ ልጅ ገንዘቡን ሁሉ ሰብስቦ ወደ ሩቅ አገር ሄደ፥ ከዚያም እያባከነ ገንዘቡን በተነ"
በማለት ይተርካል(ሉቃ.15:11-13)።

     💌ሁለት ልጆች ያሉት አባት እግዚአብሔር ነው። የመጀመሪያው ልጅ አይሁዳውያንን ይወክላል። የመጀመሪያዎቹ እድምተኞች፣ ደግሞም በኩር ፍሬ ናቸው። ሁለተኛው ልጅ ከአይሁድ ውጪ ያሉትን አማንያንን ያመለክታል። ሁለቱም ልጆች የየራሳቸው ጠባይ ቢኖራቸውም ለአባታቸው ግን አልተመቹትም። እንደ እርሱ አልሆኑም ታናሹ ልጅ አባቱን ሳይሆን ንብረቱን የሚወድ ነበር፣ ከዚያም ኮብልሎ የባከነ ነው። ታላቁ ደግሞ ንብረቱን ተካፍሏል፣ ግን በቤት ውስጥ ይኖራል። የቤት ውስጥ አቁሳይ ነው። ኋላ ወንድሙ ሲመለስም ደስተኛ አልነበረም። የወንድም ፍቅር የለውም። ግን በቤት የሚኖር ደግሞም ትጉህ ሠራተኛ ነው።  ፍቅር የሌለው ትጉህ ነው። የአባቱ ቤት ለእርሱ መሥሪያ ቤት ነው። ታናሹ ልጅ የተካፈለው ገንዘብ ምንድነው? ሰላም፣ ደስታ፣ ጸጋ፣ በረከት ነው። ከአባቱ ጋር ይኖር የነበረው ለእነዚህ ጉዳዮች ነው። እነርሱንም ተቀብሎ ቢኖር አባቱ አይከፋውም ነበር። ይባስ ብሎ ነጥቆት ሄደ።

       📖ሉቃስ ትረካውን ቀጠለ፦
" ሁሉንም ከከሰረ በኋላ በዚያች አገር ጽኑ ራብ ሆነ፥ እርሱም ይጨነቅ ጀመር። ሄዶም ከዚያች አገር ሰዎች ከአንዱ ጋር ተዳበለ፥ እርሱም እሪያ ሊያሰማራ ወደ ሜዳ ሰደደው። እሪያዎችም ከሚበሉት አሰር ሊጠግብ ይመኝ ነበር፥ የሚሰጠውም አልነበረም።"(ሉቃ.15:14-16)

        📝ያ የጠፋው ልጅ የከሰረው አንዳንድ ነገሮችን አይደለም ሁሉንም ነገሮች ነው። ከእግዚአብሔር ስንርቅ ሁሉም ነገር ይከዳናል። ያለን ሁሉ የሚኖረን ከእግዚአብሔር ጋር ሳለን ብቻ ነው። የጠፋው ልጅ ቤተኛ ከሚሆንበት ኑሮ ወጥቶ ተዳበለ። የኮበለለ ምዕመን ኑሮው የደባል ነው። ደባል፦ ነጻነቱ የተገደበ፣ የማይፈልገውን ለማየት የተዳረገ፣ ጸጥታ የሌለው፣ ስድብ የሚጠግብ፣ የማይመለከተውን በግድ የሚያስተናግድ ነው። የጠፋው ልጅ ከራቡ የተነሣ የእርያ እረኛ ሆነ። እርያ ለአይሁዳውያን ርኩስ ነው። በረከሰ ተግባር ላይ ተሰማራ። ከእርያ ምግብም ለመጥገብ ይመኝ ነበር፣ ግን አልሆነለትም። የእርያ ምግብ እርያን እንጂ ሰውን አያጠግብም። የእሪያው ምግብ መጠጥ፣ ሲስ....ነው። መጠጥ፣ ዘፈን....ለዓለማውያን ይደልል ይሆናል፣ እውነትን ቀምሶ ለነበረ ግን በፍጹም አይሆንም። ማደንዘዣው እርሱ ላይ አልሰራ አለ። ዓለማውያን ኃጢያት ሠርተው የሚያገኙትን ጊዜያዊ ሣቅ ፣ ጊዜያዊ መዘናጋት እንኳ ማግኘት አቃተው። አካሉ ኃጢያት ስፍራ ልቡ ግን አባቱ ቤት ሆነ። እየጠጣ ያለቅሳል፣ ሱስ ላይ ተቀምጦ ዝማሬው፣ ቅዳሴው ይሰማዋል።

  " ወደ ልቡም ተመልሶ እንዲህ አለ፦ እንጀራ የሚተርፋቸው የአባቴ ሞያተኞች ስንት ናቸው? እኔ ግን ከዚህ በራብ እጠፋለሁ። ተነሥቼም ወደ አባቴ እሄዳለሁና፦ አባቴ ሆይ፥ በሰማይና በፊትህ በደልሁ፥ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም፤ ከሞያተኞችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ።" (ሉቃ.15:17-19)።

    💌ወደ ወደ ልቡ ሲመለስ የአባቱ ቤትና ክብሩ ታየው። እንኳን ልጅ ባሪያም የሚጠግብበት በረከት ታወሰው። የንስሐ መንስ ገዛው።  አባቱ ተራ አባት አይደለም። ሰማይን የሚገዛ ነው። ደግሞም ያየዋል። "በፊትህ በደልሁ" እለዋለሁ አለ። በእግዚአብሔር ቤት ትንሹን ድርሻ ናፈቀ። ትንሹም ትልቅ ነውና።

   📖ሉቃስም ቀጠለ፦

"ተነሥቶም ወደ አባቱ መጣ። እርሱም ገና ሩቅ ሳለ አባቱ አየውና አዘነለት፥ ሮጦም አንገቱን አቀፈውና ሳመው። ልጁም፦ አባቴ ሆይ፥ በሰማይና በፊትህ በደልሁ፥ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም አለው። አባቱ ግን ባሪያዎቹን አለ፦ ፈጥናችሁ ከሁሉ የተሻለ ልብስ አምጡና አልብሱት፥ ለእጁ ቀለበት ለእግሩም ጫማ ስጡ፤ የሰባውን ፊሪዳ አምጥታችሁ እረዱት፥ እንብላም ደስም ይበለን፤ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም። ደስም ይላቸው ጀመር።" (ሉቃ.15፥20-24)

      📝አባቱ ልጁን የተለየው በግድ ነው። ልቡ አላረፈም። ማዶ ማዶ እያየ ይጠብቀው ነበር። እስኪደርስ አላስቻለውም፣ መንገድ አጋምሶ ተቀበለው። አልተጸየፈውም፣ ከነ ቆሻሻው አቅፎ ሳመው። አልተበሳጨበትም አዘነለት። ልብሱን ቀየረለት፣ ታሪኩን ለወጠለት። ቀለበት አደረገለት፣ ቃልኪዳኑን አደሰለት። ፍሪዳ ሠዋለት አምልኮ ተጀመረ። ታላቅም ደስታ ሆነ።

     📖ሞት በሕይወት ፣ መጥፋት በመገኘት የሚተካው በመመለስ ነው። የሚፈርድብን ሳይሆን የሚምረን አባት ነው። ዛሬም ማዶ ማዶ እያየ ይጠብቀናል። ሉቃስ የጌታችንን ንግግር መጻፍ ይቀጥላል። በጠፋው ልጅ መገኘት ትክለኛ ወይም ኗሪ ነኝ የሚለው ልጅ ተበሳጨ። አባቱ ግን መልስ ሰጠ(ሉቃ.15፥25-32)።

     💌ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት የአባትና የልጅ ግንኙነት ነው። እርሱም አፍቃሪ አባታችን ነው። ስለ እኛ የሚቆጭ፣ በርህራሄ የሚቀበለን፣ ልብሳችንን የሚለውጥልን፣ ቃልኪዳንን ሊያድስልንና እንዴት መኖር እንዳለብን የሚመክረን አባት እርሱ ነው! እግዚአብሔር ዛሬም የፍቅር እጆቹን ዘርግቶ "ልጄ ሆይ" ና ይላል!
     መመለስ ይሁንልን!!!

No comments:

Post a Comment