Tuesday, April 16, 2013

❖የሐዋርያው የጳውሎስ መልእክት ወደ ሮሜ ሰዎች ትርጓሜ


የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክት ወደ ሮሜ ሰዎች፦

ምዕራፍ ዐሥራ ሦስት

v  የክርስቲያን ኑሮ በእግዚአብሔር ዘንድ ምን መምሰል እንዳለበት በምዕራፍ 12 ተመልክተናል:: አሁን ደግሞ ያ በመልካምነት በእግዚአብሔር ፊት እንዲገለጥ የተገባው የክርስቲያን ሕይወት በምድራዊ መንግሥት ዘንድ እንዴት መገለጥ እንዳለበት በዚህ ምዕራፍ እንመለከታለን::

Ø  ክርስቲያን :

·         ከዚህ ዓለም ያልሆነ፤

·         ሀገሩም በሰማይ የሆነ /ሰማያዊ/ ዜግነት ያለው፤

·         የሚያገለግለውም ንጉሥ ክርስቶስ ኢየሱስ የሆነለት ነው:: (ዮሐ 15፥19፤ 17፥14-16፤ ፊል 3፥20፤ ቈላ 3፥24)

Ø  ይሁን እንጂ :-

·         በዚህ ምድራዊ ኑሮ እያለ የዚህ ምድር መንግሥት አገልጋይ (ሠራተኛ)፤

·         የምድሪቱም መንግሥት ታማኝ ዜጋ እንደሆነ ሊገነዘብ ይገባል::

Ø  ስለዚህም:- ክርስቲያን በዚህ ዓለም ኑሮው ታማኝነት እና መልካም አኗኗር ምን እንደሆነ ለሌላው የሚያስተምርበት ኑሮ ሊኖረው ይገባል ማለት ነው::

v  ቁጥር 1-7 :-

Ø  በዚህ ክፍል የሚያስረዳው :-

·         ሥልጣን ሁሉ የእግዚአብሔር እንደሆነ (13፥1)

·         ክርስቲያንም በታማኝ ኑሮው ለባለሥልጣናቱ ይታዘዝና ይገዛ ዘንድ ተገቢ እንደሆነ  (1ጴጥ 2፥13-17)

·         የመግዛቱ ሥርዓት የእግዚአብሔር ሥርዓት እንደሆነ የሚያሳይ ነው::

Ø  ይህ ማለት ክርስቲያን የሚቃወመው ምድራዊ መንግሥት የለም ማለት ግን አይደለም

·         የተሠራለትን ዓላማ የሚያደናቅፍ ማለት የሚኖርለትን እውቀት የሚቃወም ትዕዛዝ ከባለሥልጣናቱ ቢመጣ ይሁን ብሎ የሚጓዝ ማለት ግን አይደለም:: ከእውነት የወጣን ትዕዛዝ ሊቃወም ግድ አለበት:: (ሐዋ 4፥18-20 ፤ 5፥28-29 ፤ 5፥40-42)

Ø  ይሁን እንጂ ተቃውሞውን የሚገልጥበት መንገድም ሆነ ክፋቱን የሚዋጋበት መሣሪያ ሥጋዊ አይደለም

·         2ቆሮ 10፥3-5 ፤  ማቴ 10፥28)

v  ቁጥር 8-10 :-

Ø  እርስ በርሳችሁ ከመዋደድ በቀር ለማንም ዕዳ አይኑርባችሁ

·         ይህ ቃል የዚህ ክፍል መሪ ቃል ነው፤

·         ከላይ በቁጥር 7 ለሁሉ የሚገባውን አስረክቡ ብሎ ነበርና አሁን ባለዕዳ አትሁኑ በማለት ያንን ምክር ያፀናል::

Ø  ልናስተውል የሚገባን ሐዋርያው ስለ ገንዘብ ዕዳ ብቻ እያወራ እንዳልሆነ ነው፤

·         ጳውሎስ ራሱ “ዕዳ አለብኝ” ብሎ ነበር (ምዕ 1፥14)

·         ይህም ዕዳ የእውነት ቃልን ያለማድረስ ዕዳ ነውና ሊከፍል ወይም ሊወጣው ይተጋል (ምዕ 1፥10፤ 15)

·         ዕዳ ማለት ከእኛ የሚፈለግ ነገር ከሆነ ኃጢአተኛው ከኃጢአቱ ይመለስ ዘንድ አለማስተማር ከእኛ የሚፈለግ ዕዳ ተሸካሚዎች ያደርገናል ማለት ነው:: (ሕዝ 33፥6፤ 34፥1-10)::

v  ቁጥር 11-14 :-

Ø  ሐዋርያው ከላይ የተመለከትናቸውን ትዕዛዛት ሁሉ የሰጠበትን ምክንያት በእነዚህ ከ 11-14 ካሉት ቁጥሮች ይገልጥልናል::

Ø  እርሱም :-

·         የመዳናችን መቅረብ ፣ ይህም ታማኝ ሠራተኛ የሚሸለምበት ጊዜ (ማቴ 25፥5-6)፤

·         ማታለል፣ ዐመፅ እና ውሸት የጨለማ ሥራ ስለሆነና ከእኛ መወገድ ስላለበት (ቁጥር 12)፤

·         የብርሃንን ጋሻ ጦር ልንለብስ ስለሚገባ፣ ያውም የጠላትን ኃይል የምንዋጋበት (ኤፌ 6፥10-18)

·         ከሥጋ ሥራዎች ተለይተን በአግባብ መመላለስ (13፥13)

ማስገንዘቢያ :-

Ø  በዚህ ምዕራፍ 13፥13 ላይ ተዘርዝረው የቀረቡት ስድስት ኃጢአቶች ሲሆኑ እነርሱም የዘመኑ ኃጢአቶች ናቸው::

Ø  ምክንያቱም : በቁጥር 11 ላይ “ዘመኑን እወቁ” ካለ በኋላ በ ቁጥር 12 ላይ ደግሞ “ቀኑ ቀርቧል” በማለት አሳስቧልና ነው::

Ø  እነዚህ በቁጥር 13 ላይ የቀረቡት የመጨረሻው ዘመን ጉልህ ኃጢአቶች :

·         ዘፈንና ስካር

·         ዝሙትና መዳራት

·         ክርክርና ቅናት ናቸው

No comments:

Post a Comment