Sunday, June 28, 2020

❖ቤተክርስቲያን፦

ቤተክርስቲያን ማለት ምን ማለት ነው?
በግሪክኛ ቋንቋ ቤተክርስቲያን"አቅሌስያ"ተብላ ተጠርታለች።ትርጉሙም"የተጠሩ "ማለት ነው።ይህንን ትርጉም በተለያዩ የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት በተለይም በቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት እናገኘዋለን፦
 " በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት፥ የእነርሱና የእኛ ጌታ የሆነውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም በየስፍራው ከሚጠሩት ሁሉ ጋር ቅዱሳን ለመሆን ለተጠሩት፤"
    (1ኛ ወደ ቆሮ1:2)።
ኢየሱስ ክርስቶስ መጀመሪያ አስራ ሁለት ቅዱሳን ሐዋርያትን ጠራ።ከእነዚህ ጋር የተጠሩ 36 ቅዱሳት አንስትን ጨምሮ 72 አርድእት ነበሩ።ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዚህ ቤተክርስቲያንን መሠረተ።

ቤተ ክርስቲያን በምድር ያለች የእግዚአብሔር ተቋም ናት። የተመሠረተችውም ለአንድ ዓላማ ነው።የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ለመሆን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የምድር አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደሰማይ ከማረጉ በፊት ደቀመዛሙርቱን እንዲህ ብሎአል፦
 "ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ አለ።" (የሐዋ ሥራ 1:8)። 

ይህ ዓላማ ቤተክርስቲያን ለምን እዚህ ምድር ላይ እንደምትኖር በሚገባ ያሳያል። የቤተክርስቲያን ሠሪዋም መሠረቷም እንዲሁም ማእዘንዋም ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"አንተ ዓለት ነህ ዓለት የተባለ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነው ብሎ የመሰከረው መስክርነት ነው።  በአንተ ዓለትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም።" (የማቴ 16:18)" 
ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልምና፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"
  (1ኛ  ቆሮ 3:11)
"በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ፤፤(ኤፌ2:20)።

ቤተክርስቲያን እስከ አሁን ድረስ በነቢያትና ሐዋርያት ትሠራለች፤ ሠራተኞችም ነቢያትና ሐዋርያት ናቸው። ነገር ግን እያንዳንዱ እንዴት እንደሚሠራ መጠንቀቅ ይኖርበታል።

" የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ ተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ።"(1ኛ  ቆሮ 3:10)።

ቤተክርስቲያንን ለማነጽ የሁሉም የቤተክርስቲያን አካል ደርሻ ነው። ነገር ግን በፊተ አውራሪነት የሚመግቡ መሪዎች አሉ።" እግዚአብሔርም በቤተ ክርስቲያን አንዳንዶቹን አስቀድሞ ሐዋርያትን፥ ሁለተኛም ነቢያትን፥ ሦስተኛም አስተማሪዎችን፥ ቀጥሎም ተአምራት ማድረግን፥ ቀጥሎም የመፈወስን ስጦታ፥ እርዳታንም፥ አገዛዝንም፥ የልዩ ልዩ ዓይነት ልሳኖችንም አድርጎአል።"(1ኛ ቆሮ 12:28)።
እነዚህ ሁሉ ቤተክርስቲያንን ለማነጽ ሥራ ሥራቸውን መሥራት አለበቸው።" አጵሎስ እንግዲህ ምንድር ነው? ጳውሎስስ ምንድር ነው? በእነርሱ እጅ ያመናችሁ አገልጋዮች ናቸው፤ ለእያንዳንዳቸውም ጌታ እንደ ሰጣቸው ያገለግላሉ።" (1ኛቆሮ3:5) 

ቤተክርስቲያንና ዓላማዋ፦

1.ሁሉንም እየስተማሩ የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀመዛሙርት ማዳረግ፦


እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ። (ማቴ 28፥19-20 ) ይህ ካልሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተክርስቲያንና ከአገለጋዮቹ ጋር አይኖርም

2. ለእግዚአብሔር ቃልና ለክርስቲያናዊ ስነምግባር ግዴለሽ አለመሆን፦

በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን አውቃለሁ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር። እንዲሁ ለብ ስላልህ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው። (ራዕ 3፥16 ) ይህ ደንታ ቢስነት ቤተክርስቲያንን አለማዊ ያደርጋታል .ከእግዚአብሔር መንግሥትም ያወጣታል ቤተክርስቲያን በምድር ያለሽ የእግዚአብሔር መንግሥት ናትና

3. በምድር የምታበራ መቅረዝ ናት፦

በመቅረዞቹም መካከል የሰው ልጅ የሚመስለውን አየሁ፥ እርሱም እስከ እግሩ ድረስ ልብስ የለበሰው ደረቱንም በወርቅ መታጠቂያ የታጠቀ ነበር። (ራዕ 1፥13) መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ። የቤተክርስቲያን መኖር በጨለማው ዓለም እንድታበራ ነው የተቃጠለ አንቦል ለምንም አይጠቅም ። ቤተክርስቲያን የክርስቶስን ብርሃን ያለማቋረጥ ማብራት ይኖርባታል

4. የዲብሎስን ሥራ ማፍርስ፦

 ይህም ዘርኘነት፤ ጥላቻ፤ ርኩሰት በአጠቃላይ ከእግዚአብሔር ቅዱስ ባህርይ የማይሠማሙትን ሁሉ ማስወገድ ዓላማዋና ተልኮዋ ነው።
ስለዚህ የዲያብሎስን ሥራ እንዲያፈርስ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ። ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ኃጢአትን አያደርግም፥ ዘሩ በእርሱ ይኖራልና፤ ከእግዚአብሔርም ተወልዶአልና ኃጢአትን ሊያደርግ አይችልም። (1ኛ ዮሐ 3፥9)

5. ፍቅርን መግለጽ፦

ወዳጆች ሆይ፥ ፍቅር ከእግዚአብሔር ስለ ሆነ፥ የሚወደውም ሁሉ ከእግዚአብሔር ስለ ተወለደ እግዚአብሔርንም ስለሚያውቅ፥ እርስ በርሳችን እንዋደድ። ፍቅር የሌለው እግዚአብሔርን አያውቅም፥ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና። በዚህ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፥ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና። ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም። ወዳጆች ሆይ፥ እግዚአብሔር እንዲህ አድርጎ ከወደደን እኛ ደግሞ እርስ በርሳችን ልንዋደድ ይገባናል። እግዚአብሔርን ማንም ከቶ አላየውም፤ እርስ በርሳችን ብንዋደድ እግዚአብሔር በእኛ ይኖራል ፍቅሩም በእኛ ፍጹም ሆኖአል። (1ኛ ዮሐ 4 ፡7-12)
 ፍቅር የሌላት ቤትክርስቲያንና ፍቅር የሌለው ክርስቲያን እግዚአብሔር በውስጡ የለም ያለፍቅር ክርስትና የለም።

Tuesday, June 23, 2020

❖ የማይገባ ደግነት:-

ይቅርታ በደልን ለመርሳት የሚደረግ ሙከራ፣ ወይም
ሰውዬውን መርሳት አይደለም፡፡ ይቅርታ ለበደለኛው
የማይገባውን መስጠት ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የታረቅንበት ምሥጢሩ ይህ የማይገባን ደግነት ነው፡፡
ለሰማያዊው አባት ያለንን ፍቅር ልንገልጥ የምንችለው እርሱ የፈጠራቸውን ሰዎች በመውደድ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያሳየንን
ፍቅር እኛም ለጎረቤታችን ማሳየት ይገባል፡፡ እግዚአብሔር
የጠፋውን ዓለም በእኛ ውስጥ ሆኖ ሊወደው ይፈልጋል፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ አስደናቂ ይቅርታ ስላሳዩ ሰዎች
እናነባለን፡፡ ከእነርሱም ሦስቱን በዚህ ክፍል ለማየት
መርጠናቸዋል፡፡ እነርሱም አዳም፣ ዮሴፍና የእስጢፋኖስ
ቤተሰቦች ናቸው፡፡
አዳም በሚወዳትና በሚያዳምጣት ሚስቱ አማካይነት
በኃጢአት ወደቀ፡፡ ጸጋው ተገፈፈ፣ ነጻነት የሌለው ሰው ሆነ፣
ፍርሃትና ሽሽት ከማያመልጠው ማንነት ጋር ገጠመው፡፡
ምክንያትም ሳያስጥለው የዘላለም ሞት ተፈረደበት፡፡ በሥጋ ሞት
ላይ የነፍስ ሞት፣ ወደ መቃብር በመውረድ ላይ ወደ ሲኦል
መውረድ ተፈረደበት፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ እግዚአብሔር ተለየው፡፡
አዳም የሚስቱን ዓይን ላለማየት ቢወስን፣ ቢሸሻትና እርሷን
ይቅር ለማለት ቢፈተን ማንም አይፈርድበትም፡፡ እርሱ ግን ፍጹም
ይቅር ባይ ነበርና ያን የማይገባ ደግነት አሳያት፡፡ ሞትን
ላመጣችበት ሴት «አዳምም ለሚስቱ ሔዋን ብሎ ስም አወጣ፣
የሕያዋን ሁሉ እናት ናትና» (ዘፍ3፡20)፡፡
ሔዋን አሁን ሕያው አይደለችም፡፡ ሙታንም ከእርሷ
ይወጣሉ፡፡ ነገር ግን አዳም የአሁኑን ሳይሆን የተስፋዋን ፍጻሜ
አየ፡፡ የሆነችውን ሳይሆን ልትሆን ያላትን አሰበ፡፡ ስለዚህ የሕያዋን
እናት አላት፡፡ ለወደቁት ሰዎች የመነሣት ጉልበታቸው ዛሬም
በእነርሱ ላይ ያለን እምነት ነው፡፡ ምን እንደሚሆኑ ያለን ተስፋ
አንድ ቀን ራእያቸው ይሆናል፡፡ «የወደቁ ሰዎች የተዘረጉ እጆችን
ይፈልጋሉ፡፡»
ጋብቻ እንደ አዳምና እንደ ሔዋን ነው፡፡ ውድቀት ያልፈታው
ትዳር የእነዚህ ወገኖች ትዳር ነው፡፡ ዛሬ ብዙዎች ትዳራቸውን
ይቅር ማለት አልቻሉም፡፡ ስለ ንብረታቸውና ስለ ልጆቻቸው እያዘኑ
ይኖራሉ፡፡ ዘይቱ እንዳለቀበት መቅረዝ ፍቅር አልቆባቸው
ጨልመዋል፡፡ ተዋደው የገቡ ሳይሆን በፍርድ ቤት ትእዛዝ
የተጣመሩ እስኪመስል መሸካከም አልቻሉም፡፡ ብዙ ጊዜም
አንዳቸው በመንፈስ ጭንቀት ሲያዙ የጠባይ ለውጥ እየመሰለ
ይበልጥ ይከፋፋሉ፡፡ የትዳር ጓደኛ መነጫነጭ፣አለመርካት፣
የትዳር ውሳኔውን መርገም፣ ልጆቹንና የትዳር ጓደኛውን ማየት
ሲጠላ . . . የጠባይ ለውጥ ብቻ ላይሆን ይችላልና መመርመሩ
መልካም ነው፡፡ በትዳር ውስጥ ትልቁ ጉዳትም ስህተትን
የሚፈልግ ዓይን በመሆኑ ከዚህ መትረፍ ያስፈልጋል፡፡ በየዕለቱ
ከምንሞላው ኃይል አንዱ ፍቅር ነውና ስንጎድልና ማፍቀር
ሲያቅተን በጸጋው ዙፋን ፊት ወድቀን ሙላኝ ልንል ይገባል፡፡

ሌላው የተደነቀ የይቅርታ ሕይወት የሚታየው በዮሴፍ
ላይ ነው፡፡ ዮሴፍ ከወንድሞቹ ይልቅ አባቱ ይወደው ነበር፡፡ ምንም
ባይበድላቸው መወደድም የመጠላት ምክንያት ይሆናልና
ወንድሞቹ ጠሉት (ዘፍ. 37፡4)፡፡ ዮሴፍ ሕልሙን በነገራቸው ጊዜ
ደግሞ ወደፊት ይሆናል የሚሉትን ነገር ሲያስቡ በቅንዓት አበዱ፡፡
በበረሃ እየተቅበዘበዘ ሲፈልጋቸው እነርሱ ግን ሊገድሉት
ተማክረው በጉድጓድ ጣሉት፡፡ የግብጽ ነጋዴዎች ሲያልፉ
አይተውም በሃያ ብር ሸጡት፡፡ በጉስቁልና ከሕልሙ ያራቁት
መስሏቸው ይበልጥ ወደ ሕልሙ ትርጓሜ ገፉት፡፡ «መገፋት ጥሩ
ነው እምብዛም ሳይወድቁ፣ የተገፉት ቆመው የገፉት ወደቁ፤»
ዮሴፍም ገና በልጅነቱ ብርቱ መከራ ደረሰበት፣ በባዕድ
አገር በአገልጋይነትና በእስር ተንገላታ፡፡ በኃጢአት አልተባበርም
ማለት በዓለም ያስቀጣልና አሥራ ሦስት ዓመት ተቀጣ፡፡ ነገር
ግን ይህ ጠባብ መንገድ ወደ ሰፊው ጎዳና የሚያወጣ ነበር፡፡
ዮሴፍ ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ራእይ የጠላትነት ብዛት
ሊያሸንፈው አልቻለም፡፡ እንደውም ጠላቶቹ ወደ ራእዩ እንዲደርስ
ያቻኩሉት ነበር ፡፡ አንድ ሰው «እግዚአብሔር ታላቅ በረከት
እንዳዘጋጀልኝ ቀድሞ የሚነግረኝ ሰይጣን ነው፡፡ ይተነኳኮለኛል»
ብሏል፡፡
ዮሴፍ የግብፅ አገር ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነ፡፡
እግዚአብሔር ያለው አይቀርምና ወንድሞቹ ሰገዱለት፡፡ በከነዓን
ምድር ረሃብ እያሯሯጠ ወደ ግብጽ አመጣቸው፡፡ ዮሴፍ
አወቃቸው እነርሱ ግን አላወቁትም፡፡ ራሱን በገለጠላቸው ጊዜ
በጭንቀት ተናጡ፡፡ በልባቸው ሌላውን ከመበደል ራስ መበደል
ይሻላል ሳይሉ አልቀሩም፡፡ የዮሴፍን ፊቱን ማየት አልቻሉም፡፡
እርሱ ግን አልበደላቸውምና ፊታቸውን አየ፡፡ መልካምነት
ሥልጣን ካልሆነን በቀር የማንንም ፊቱን ማየት አይቻለንም፡፡
ዮሴፍ አሁን ሊበቀላቸው ይችላል፡፡ እነርሱም ፈርተው
ነበር፡፡ ዮሴፍ ግን እግዚአብሔር ክፉውን ለውጦ ለመልካም
እንዳደረገው ስለተረዳ ይቅር አላቸው፡፡ ምንም ክፉ
ቢያደርጉበትም ወደ ተስፋው እንዳቀረቡት ተረዳ፡፡ እግዚአብሔር
አንዳንዴ እምነታችን እንዲያድግ በክፉ ሰዎች መካከል
ያስቀምጠናል፡፡ እንድንጠነክር ታዝዘው መከራ ያደርሱብናል፡፡
ታዲያ ከንጉሡ ታዝዞ ሎሌው አርባ ቢገርፈን እንቀየመዋለን?
ከሰዎች ጋር መታገል ከንቱ ነው፡፡
ዮሴፍ መበቀል እየቻለ አልተበቀላቸውም፡፡ በቀል
የእግዚአብሔር፣ ይቅርታ የእርሱ መሆኑን ተረዳ
(ዘፍ.50፣19-20)፡፡ ሕጋዊ መንግሥት ባለበት አገር የበደለንን
ሰው ራሳችን ብንቀጣ መንግሥትን እንደካድን ይቆጠራል፡፡
እንዲሁም በጽድቅ የሚፈርድ አምላክ እያለ እኛ ተበቃይ ብንሆን
እግዚአብሐርን ክደነዋል ማለት ነው (ሮሜ.12፣19-21)፡፡ አዎ
የእግዚአብሔር ሰዎች በእግዚአብሔር ቦታ ሆነው የነገሮችን
አካሄድ መለወጥ እንደማይችሉ ሲረዱ እግዚአብሔርም ለእነርሱ
ነገሮችን ወደ በጎ የሚለውጥ መሆኑን ያምናሉ፡፡ ዮሴፍ ቢበቀል
ኖሮ ከእግዚአብሔር ጋር በተጣላና ያን ክብር ባላገኘ ነበር፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ እግዚአብሔር የአገር መሪዎችና ባለሥልጣናት
የይቅርታ ሰዎች እንዲሆኑለት ይፈልጋል፡፡ የበለጠ ኃላፊነትን
ለመሸከም እግዚአብሔር ይቅር ባዮችን ያጫል፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የምናየው ሦስተኛው የይቅርታ
ሕይወት የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች ያደረጉት ነው፡፡ ወጣቱ ሰማዕት
እስጢፋኖስ የሞተው በአሁኑ ጳውሎስና በግብረ አበሮቹ
በድንጋይ ተወግሮ ነው፡፡ እስጢፋኖስ ግን «ጌታ ሆይ፡ ይህን
ኃጢአት አትቊጠርባቸው» እያለ ጸለየላቸው፡፡ ይህንን ጸሎት
የጸለየው «የእግዚአብሔርን ክብር ኢየሱስንም» ካየ በኋላ ነው
(የሐዋ.ሥራ.7፣55-60)፡፡ ክርስቶስን ስናይ ብቻ ልባችን
ለይቅርታ ይለዝባል፡፡ ከወጋሪዎቹ አንዱ ጳውሎስ የድሮው ሳውል
ክርስቲያን ሆነ፡፡ ጳውሎስ የእስጢፋኖስ የይቅርታ ጸሎት ልቡን
ነክቶታል፣ ወይም ልብን የሚነካ ጸጋ አምጥቶለታል፡፡
ይህ ጳውሎስ ያውም ለትምክሕት «የእስጢፋኖስንም
ቤተ ሰዎች ደግሞ አጥምቄአለሁ ጨምሬ ሌላ አጥምቄ
እንደሆነ አላውቅም» (1ቆሮ.1፣16) ማለቱ ያስገርመናል፡፡ እኛ
ይቅር ብንል እንኳ ቤተሰብ በቶሎ ይቅር አይልም፡፡ ቤተሰብ
ስለልጅ መቀየም ጽድቅ ነው የሚመስለው፡፡ የእስጢፋኖስ
ቤተሰቦች ግን በልጃቸው ገዳይ በጳውሎስ እጅ መጠመቃቸው
የይቅርታን ጽኑነት ያሳየናል፡፡
እኛ ገንዘብ የካዱንን ይቅር ማለት ሲያቅተን አዳም
ገነትንና እግዚአብሔርን ያሳጣችውን ሔዋንን ይቅር አላት፡፡ ዮሴፍ
ልጅነቱን ለመከራ እቶን የዳረጉት ወንድሞቹን በበቀል ሳይሆን
በይቅርታ አሸነፋቸው፡፡ የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች ደም መላሽ
ቢሆኑ ኖሮ ጳውሎስን በመልእክቱ ዛሬ አናገኘውም ነበር፡፡ ይቅርታ
ለትውልድ የምናቆየው ውለታ ነው፡፡ በእርግጥም ይቅርታ
የማይገባንን በሰጠን በእግዚአብሔር ፊት ሰውዬው
የማይገባውን መስጠት ነው፡፡
                  *ይቅርታ*
       የይቅርታ ልብ ይስጠን!!!

Friday, June 19, 2020

❖የጌታ መልአክና ወንጌል፦

የጌታ መልአክና ወንጌል፦
የእግዚአብሔር መልአክ ሕይወት የሆነው ጌታ ለዓለም እንዲበሰር ተናገረ። 

የጌታ መልአክ ግን በሌሊት የወኅኒውን ደጅ ከፍቶ አወጣቸውና፦
ሂዱና ቆማችሁ የዚህን ሕይወት ቃል ሁሉ ለሕዝብ በመቅደስ ንገሩ አላቸው። (የሐዋ 5፡19፡20)
ምክንያቱም ሰው ሕይወት እንዲኖረው ይፈልጋል። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም። (ዮሐ 5፡24)

በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።
እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።

ቆርኔሌዎስን ከቅዱስ ጴጥሮስ ወንጌልን እንዲሰማ አዘዘው፦

ጻድቅ ሰው እግዚአብሔርንም የሚፈራ በአይሁድም ሕዝብ ሁሉ የተመሰከረለት የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስ ወደ ቤቱ ያስመጣህ ዘንድ ከአንተም ቃልን ይሰማ ዘንድ ከቅዱስ መልአክ ተረዳ አሉት።ርሱም መልአክ በቤቱ ቆሞ እንዳየና፦ ወደ ኢዮጴ ሰዎች ልከህ ጴጥሮስ የተባለውን ስምዖንን አስመጣ፤እርሱ ቤቱ በባሕር አጠገብ ባለው በቍርበት ፋቂው በስምዖን ዘንድ እንግድነት ተቀምጦአል፤ ልታደርገው የሚገባህን እርሱ ይነግርሃል።

ይህ መልአክ ጴጥሮስ ስለዘዓለአለም ሕይወት እንደሚነገር ያውቃል።

በዘመን መጨረሻ የእግዚአብሔር መልአክ ወንጌልን ለዓለም ያውጃል፦

በምድርም ለሚኖሩ ለሕዝብም ለነገድም ለቋንቋም ለወገንም ሁሉ ይሰብክ ዘንድ የዘላለም ወንጌል ያለው ሌላ መልአክ ከሰማይ መካከል ሲበር አየሁ።  (ራእይ14፥6 )

በጨረሻም ቢሆን እንኳ ሰው ሁሉ ሕይወትን እንዲያገኝ የእግዚአብሔር መልአክ ያውጃል የሰው ልጅ ለሚያገኝው የዘለአለም ሕይወት ያለቸውን ከፍታኛ ፍለጎት ያረጋግጣል እኛ ግን ለኛ የሆነውን ሕይወት ቦታ አልሰጠነውም ።

   

                የእግዚአብሄር ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን!!

Sunday, June 7, 2020

❖መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውኃ ወንዝ ነው፦

☞መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውኃ ወንዝ ነው፦

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲስተምር፦
"በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ ይላል "ቅዱስ ወንጌል 

  (ዮሐ 7፥38)

❖  ይህን የተናገረው ለማን እንደሆነ ሲገልጽ፦

"ይህን ግን በእርሱ የሚያምኑ ሊቀበሉት ስላላቸው ስለ መንፈስ ተናገረ፤ ኢየሱስ ገና ስላልከበረ [ስላልተሰቀለ ማለት ነው] መንፈስ ገና አልወረደም ነበርና" ብሏል። 

ወንዝ ሳያቋርጥ የሚፈስ ነው የመንፈስ ቅዱስ ፀጋና በረከትም ለሚቀበሉት ሁሉ ያለማቋረጥ ሲሰጥ ይኖራል። 


❖  ቅዱስ ጴጥሮስ በሃምስኛው ቀን ለደቀመዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ መውረዱን ሲያስረዳ፦


እግዚአብሔር ይላል፦ 

"በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፥ ጎበዞቻችሁም ራእይ ያያሉ፥ ሽማግሌዎቻችሁም ሕልም ያልማሉ፤ደግሞም በዚያች ወራት በወንዶችና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ ትንቢትም ይናገራሉ"።

     (የሐዋ 2፥17-18)

   ወንዝ የፈሰሰበት ሁሉ ይለመልማል ያፈራል። መንፈስ ቅዱስም ያደረበት ሁሉ በእግዚአብሔር ፀጋ ይለመልማል የእግዚአብሔር የሆነውን ያፈራል ። 

  ሕዝቅኤል የመንፈስ ቅዱስን ፀጋና በረከት ከመቅደሱ የሚፈስ የሕይወት ውኀ መሆኑን ገልጿል።

ከመቅደሱ የሚወጣ ዉሃ ወደ ምስራቅ ሲፈስ ይመለከታል፡፡ 

ሰውየው (የሚያሳየው መልአክ ማለት ነው) ገመዱን በእጁ ይዞ 1000 ክንድ ለካ፡፡ 

  በዉሃው ውስጥ አሻገረኘ ዉሃው እስከ ቁርጭምጭሚት ደረሰ።

   ሁለተኛ ሲሻገረው እስከ ጉልበት።

   ሶስተኛ እስከ ወገብ ።

  አራተኛ እጀግ ጥልቅና ሰፊ ወንዝ በመሆኑ ማንም ሊሻገረው የማይችል ወንዝ ሆነ፡፡ 


❖  ወንዙ የእግዚአብሔርን በረከትና ፀጋ ዘልዓለማዊ ሕይወትን ይገልጻል፡፡ 


  እስከ ቁርጭምጭሚት በዘመነ አበው የነበረውን የእግዚአብሔር በረከትና ፀጋ፣ 

  እስከ ጉልበት በዘመነ መሳፍንት የነበረውን የእግዚአብሔር በረከትና ፀጋ፣ 

  እስከ ወገብ በዘመነ ነቢያት የነበረውን የእግዚአብሔር በረከትና ፀጋ ደህንነት፣ 

  ማንም ሊሻገረው የማይችለው ዉሃ በጌታችን በኢየሱስ ክረስቶስ የተሰጠውን በረከትና ፀጋ ዘልዓለማዊ ሕይወት የሚገልጽ ነው፡፡


ማንም ሊሻገረው የማይችል ታላቅ ወንዝ እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራልና፤ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና የሚለውን ያረጋግጣል። 

  መሲህ የሕይወት ዉሃ መሆኑን ተናግሯል፡፡ 

  መንፈስ ቅዱስም የሕይወት ውሃ መሆኑን ተናግሯል። 

  በርሱ የሚያምን የሕይወት ዉሃ ከርሱ እንደሚመነጭ አስተምሯል፡፡ 

   በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።


❖  ዉሃው ወደ ምስራቅ ባሕር በገባ ጊዜ የምስራቁ ባሕር ሙት ባሕር ነው፡፡ ዉሃው ይፈወሳል። 

  ዉሃው የሚወክለው የረከሰውን ሕዝብ ሰለሆነ በመሲህ ያመነ ሁሉ ፈውስንና የዘልዓለም ሕይወትን ማግኘቱን ያረጋግጣል፡፡ 

   ዉሃው ሕያው ነፍስ ያለው ተንቀሳቃሽ ሁሉ በሕይወት የሚኖርበት መሆኑን ይናገራል፡፡ 

  ወንዙ በሚመጣበት ያለው ሁሉ በሕይወት ይኖራል፡፡ 

ዉሃው የሚፈሰው እጅግ በበረሃማነት ወደሚታወቀው ወደ ይሁዳ ምድረበዳና ወደ ጨው ባሕር ነው፡፡ መራራው የጨው ባሕር የብዙ ዓሳዎችና ተንቃሳቃሽ ሕያዋን ፍጥረታት መኖርያ ይሆናል፡፡ ይህም የሆነው ጨዋማው ዉሃ በመቅደሱ ውሃ ስለተፈወሰ ነው፡፡ 

ረግረግና እቋሪው ግን ጨው እንደሆነ ይኖራል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ያላመኑትን ይመለከታል፡፡ በወንዙ በዚህና በዚያ ፍሬው የሚበላ ዛፍ ቅጠሉ የማይረግፍ ፍሬው ለሁልጊዜ የሚያፈራ አለ፡፡ ፍሬው ለመብል ቅጠሉ ለመድኀኒት የሕይወት ዛፍ ነው የሚወክለውም ዘልዓለማዊ ሕይወትን ነው፡፡

                                               (ሕዝቅኤል 47፥1-12)


                እግዚአብሄር ይክበር ይመስገን!!!

❖መንፈስ ቅዱስ፦

መንፈስ ቅዱስ ማን ነው?

፩. መንፈስ ቅዱስ ማን ነው?

  ☞ ከሦስቱ የሥላሴ አካላት አንዱ አካል ነው፡፡

  ☞ የማይጨበጥ፤የማይታይ አካል ያለው መንፈስ ነው፡፡

  ☞ የሰረፀው (የወጣው) ከአብ ነው።

  ☞ ከአብ እና ከወልድ ጋር እኩል ምስጋናና አምልኮ የሚገባው ነው። 

  ☞ እግዚአብሔር (አምላክ) ነው፡፡

  ☞ የአብ እና የወልድ እስትንፋስ (ሕይወት)ነው፡፡

  ☞ በነቢያትና በሐዋርያት አድሮ የተናገረ፥ሕይወትንም ያቀና : ምድርን ለክብሩ ያስጌጠ ነው፡፡

፪. የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌዎች ምን ምን ናቸው? 

   ርግብ፣ እሳት፣ ውኃ፣ ዘይትና ነፋስ ናቸው። 

☞  ርግብ የዋህ ናት፦ መንፈስ ቅዱስም የዋህና ቂም የማያውቅ ነው፡፡ ርግብ በኖህ ዘመን የጥፋት ውኃ መድረቁን  ያወጀች  የሰላም ምልክት ናት፤ መንፈስ ቅዱስም ክርስቶስ ሲጠመቅ የኃጢአት ባሕር መድረቁን በርግብ ምሳሌ ወርዶ የሰበከ የሰላም ጌታ ነው።

☞  እሳት ያበስላል፦  መንፈስ ቅዱስም ሕፃን የሆነውን አእምሮ በጥበብ ያጎለምሳል፡፡ እሳት የከበረ ማዕድንን ከአፈር ይለያል፥ መንፈስ ቅዱስም አምኖ የከበረውን ፡ ካላመነው ይለያል፡፡

☞  ውኃ ያነፃል፥ መንፈስ ቅዱስ ይቀድሳል፡፡

☞  ነፋስ፣ ነፍስና መንፈስ የሚወጡበት የግሪክ ቃል ኒዩማ የሚል ሲሆን ከነፋስ- ነፍስ፤ ከነፍስ- መንፈስ ይረቃል። ነፋስ በእንቅስቃሴው እንደሚታወቅ መንፈስ ቅዱስም በሥራው ይታወቃል፡፡

❖  በብሉይ ኪዳን የመብራት ዘይት ነበረ፥ በየዕለቱ በመቅረዙ ይጨመራል፡፡ ይህ የመብራቱ አለመጥፋት የመንፈስ ቅዱስን መኖር ያመለክታል፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ ለቅርፅ አልባዋ መሬት ውበት ያፈሰሰ፥ ውኆችን ለፍጥረት ጥቅም የቀደሰ ጌታ ነው፡፡ "ምድርም ባዶ ነበረች፥ አንዳችም አልነበረባትም፤ ጨለማም በጥልቁ ላይ ነበረ፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በውኃ ላይ ሰፍፎ ነበር።" ኦሪት ዘፍጥረት 1:2።

❖  መንፈስ ቅዱስ መሳፍንትን በምስፍና፥ ነገሥታትን በንግሥና፥ ካህናትን በክህነት ጸጋ፥ ነቢያትን በሀብተ ትንቢት፥ ዘማርያንን በዝማሬ ጸጋ፥ ፈዋሾችን በሀብተ ፈውስ ......የሾመ...ጸጋ የሰጠና ጸጋን ያደላደለ ቅዱስ መንፈስ ነው፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ ቅድስት ኤልሳቤጥ ለድንግል ማርያም የሆነላትን እንድትረዳ አደረባት፡፡ ድንግል ማርያም በድንግልና እንድትወልድ ሁሉን አስቻላት፡፡ በክርስቶስ አገልግሎት ነበረ፡፡ 

  ክርስቶስ ከማረጉ በፊት ስለ መንፈስ ቅዱስ መምጣት ተናግሯል፡፡

☞   "አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።" የዮሐንስ ወንጌል 14:26

☞  "እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ። እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤ ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ነው፤ ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው። የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ፥ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም። ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል።" ዮሐንስ 16:7-15::

☞   " ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤" የዮሐንስ 15:26።

☞  " ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል፤እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ።" ዮሐንስ 14:15-16::

❖  በመጽሐፍ ቅዱስ አንዱ መንፈስ ቅዱስ በአደራረጉ ምክንያት:- 

    ☞  የእውቀት መንፈስ፣ 

    ☞  የጥበብ መንፈስ፣ 

    ☞  የኃይል መንፈስ፣ 

    ☞  የእውነት መንፈስ፣ 

    ☞  የመገለጥ መንፈስ፣ ...ተብሎ ተጠርቷል፡፡ 

በክርስቶስ አገለግሎት የነበረው ሱታፌ እንዳለ ሆኖ በክርስቶስ ትምህርት እንዴት እንደተገለጠ ከላይ ባሉት ጥቅሶች አይተናል፡፡ በክርስቶስ ትምህርት አጽናኝ(ጰራቅሊጦስ)፣ የእውነት መንፈስ እና ሁሉን የሚነግር መምህር ተብሏል፡፡ የሚመጣው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው፡፡ የሚመጣበት አላማ ስለ ክርስቶስ ለመመስከር ነው፡፡ ስለዚህ በክርስቶስ የማያምኑትን ይወቅሳል፤ የዲያብሎስን መጣል ይናገራል፤ ጽድቅ ወደ አብ በሄደው በክርስቶስ እንደሆነ ይመሰክራል፤ የቤተክርስቲያንን እንቅስቃሴ ይመራል፤ ምእመናንን ያጽናናል፤ ለበጉ ሠርግ ያዘጋጃል፤ አገልጋዮችን ያሰማራል፡፡ 

❖  ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባረገ በአስረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስ ወደ ዓለም መጣ፤ በጽርሐ ጽዮን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የተወለደችውን የክብርት ቤተክርስቲያን ልደት በእሳት ላንቃ በዓለም ቋንቋ አከበረ፡፡ ሐዋርያትን ለእውነት አስጨከነ፤ ምስጢር እና ብዙ ቋንቋዎች ገለጠላቸው፡፡ በጉዞቸው ሁሉ አብሮ ነበረ፡፡ ዛሬም የቤተክርስቲያን አገለግሎት ሕይወት መንፈስ ቅዱስ ነውና ክብር ለመንፈስ ቅዱስ!!

❖  ላመነ ሰው ጥምቀት የሚፈጸመው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነው፡፡ ይህም የክርስቶስ ትእዛዝ ነው፡፡ ማቴ 28:19:: በጥቅሉ ያለ መንፈስ ቅዱስ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን አይፈጽሙም፡፡ የምስጢራቱ አፈጻጸም ሥርዓት የሚመራው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ 

በመግቢያዬ እንደጻፍኩት ቤተክርስቲያን ስለ መንፈስ ቅዱስ ጠንካራ አቋም አላት፦ "ማህየዊ በሚሆን በአንድ ጌታ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን፤ እርሱም ከአብ የሰረፀ ነው፡፡ በነቢያት እና በሐዋርያት ተናግሯል፡፡ ከአብ ከወልድ ጋር ምስጋና ይገባዋል።" ጸሎተ ሃይማኖት አንቀጽ ፰.

መንፈስ ቅዱስ፦

☞  ሕይወት ሰጭ፤ ጥበብ ገላጭ መንፈስ ነው፡፡

☞  የጸጋ ምንጭ እና አደላዳይ ነው፡፡

☞  ለበጎ ሥራ ቀስቃሽ፤ከኃጢአት እንድንወጣ ወቃሽ ነው

☞  ልብን አይቶ የሚሾም፤ ትሁታንን የሚያከብር ቅዱስ መንፈስ ነው፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ኃይል ነው፡፡ ብርታት የሆነን እርሱ ነው፡፡ ስንደክም ያግዘናል፡፡ እንዴት መጸለይ እንዳለብን ያስተምረናል(ሮሜ 8:26-27)፥ እንዴት ማምለክ እንዳለብን ይመራናል፥ ከዚያ ጸሎታችንን ይሰማል፤ አምልኮችንን ይቀበላል፡፡

❖  የመንፈስ ቅዱስ ነገር ለፍጥረታዊው ሰው ሞኝነት ነው፡፡ "ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፤ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ሆነ ሊያውቀው አይችልም።" 1ቆሮንቶስ 2:14። የመንፈስ ቅዱስ ጉዳይ በእምነት መንፈስ እንጂ በሥጋ አይመረመርም፡፡ የጰራቅሊጦስ የተቀበልነው ይህን የእውነት መንፈስ ነው፡፡ "እኛ ግን ከእግዚአብሔር እንዲያው የተሰጠንን እናውቅ ዘንድ ከእግዚአብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንም።" 1ቆሮንቶስ 2:12።

❖  መንፈስ ቅዱስ በፍጥረታዊ ሰው አይኖርም፡፡ እንዲያውም የክርስቶስ መንፈስ የሌለው የክርስቶስ ወገን አይደለም፡፡ "የክርስቶስ መንፈስ የሌለው ከሆነ ግን ይኸው የእርሱ ወገን አይደለም።" ሮሜ 8:9።

❖  ምክር፣ ጥበብ፣ ምስጢር፣ ትንቢት፣ ፈውስ፣ ዝማሬ፣ ሹመት፣ ኃይል .... ከመንፈስ ቅዱስ ይሰጣሉ፡፡ ደስታ፣ ፍቅር፣ እምነት፣ የዋሃት፣ ራስን መግዛት፣ ትዕግስት፤ በጎነት፣ ቸርነትና ሰላም የመንፈስ ፍሬ ናቸው፡፡ ገላ 5:23:: 

❖  መንፈስ ቅዱስ ከምንተነፍሰው አየር በላይ ያስፈልገናል፡፡ በሥራችን ዐመፃ የመንፈስ ቅዱስን አሠራር ልንቃወም እንችላለን፡፡ "መንፈስን አታጥፉ፤" 1ተሰሎንቄ 5:19። ንጉሥ ዳዊት በበደለ ጊዜ ይህ አጋዥ፣ አስተማሪ፣ መሪ እና አጽናኝ መንፈስ እንዳይወስድበት ለመነ፡፡ "ከፊትህ አትጣለኝ፥ ቅዱስ መንፈስህንም ከእኔ ላይ አትውሰድብኝ።" መዝሙረ ዳዊት 51:11።

❖  መንፈስ ቅዱስ ከተለየን ሕይወት፣ ሰላም፣ ዕረፍት፣ መንፈሳዊነት ... የንስሐ ጸጸት...ይለዩናል፡፡ ስለዚህ "ለቤዛም ቀን የታተማችሁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ። መራርነትና ንዴት ቁጣም ጩኸትም መሳደብም ሁሉ ከክፋት ሁሉ ጋር ከእናንተ ዘንድ ይወገድ። እርስ በርሳችሁም ቸሮችና ርኅሩኆች ሁኑ፥ እግዚአብሔርም ደግሞ በክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ ይቅር ተባባሉ።" ኤፌ 4:30-32:: የሥጋ ሥራ ከመንፈስ አላማ ያወጣል፡፡ የሥጋ አሠራር መንፈስ ቅዱስን ይቃወማል፡፡ ደስታ የሰጠን ሀዘን ሊቀበል አይችልም፡፡ ባናከብረው ደስታ የምናጣው እኛ ነን፡፡ " ለአሠራሩ እንመች፡፡ በኖህ ዘመን ርግቧ በመጀመሪያው ጉዞዋ ማረፊያ አጥታ እንደተንከራተተች መንፈስ ቅዱስም ለአሠራሩ የሚመች ሰው አጥቶ በዙሪያችን አለ።" ለአሠራሩ እንመች፡፡ እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ አደረሰን፡፡ ስለመንፈስ ቅዱስ አንብቡ ፥ ዘምሩ፡፡ 

 ለመንፈስ ቅዱስ ክብርና ምስጋና ይገባል!!! 

Friday, June 5, 2020

❖አቤቱ ሞትህን እንናገራለን ድንቅ ትንሳኤህን እናወራለን፦ (1ቆሮ 11:26)

አቤቱ ሞትህን እንናገራለን ድንቅ ትንሳኤህን እናወራለን፦

አብዛኛው  የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ስለ እርሱ እንደሚናገር ራሱ ባለቤቱ ኢየሱስ ክርስቶስ መስክሮአል። « ከሙሴና ከነቢያት ሁሉ ጀምሮ ስለ እርሱ በመጻሕፍት ሁሉ የተጻፈውን ተረጐመላቸው። ….. እርሱም፦ ከእናንተ ጋር ሳለሁ በሙሴ ሕግና በነቢያት በመዝሙራትም ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይገባል ብዬ የነገርኋችሁ ቃሌ ይህ ነው አላቸው።»  (ሉቃ 24:27:44)

መላው መጽሐፍ ቅዱስ በአቀራረቡ ከፍጥረተ-ዓለም እስከ ኅልፈተ-ዓለም ያሉ ነገሮችን በአብዛኛው ጠቅለል አድርጎ ሲናገር የክርስቶስን ሕይወት ግን ከልደቱ እስከ ሞቱና ትንሣኤው በዝርዝር ዘግቧል። ከሚናገርለት የብዙ ሺህ ዓመታት ጉዳይ እና ብዙ ሰዎች አንጻር ስናየው ስለ ክርስቶስ ከሁሉም የበለጠ ሰፊ ሽፋን ሰጥቷል። በተለይም መከራና ሞቱን(ከትንሣኤው ጋር) በተለየ ሁኔታ በየሰዓቱ ማለት ይቻላል የነበረውን ዝርዝር ሁኔታ በመናገር ከሌላው የሕይወት ክፍሉ የላቀ ትኩረት እንደሰጠው እናስተውላለን። 

ይህም የእግዚአብሔር ዘላለማዊ አጀንዳ በልጁ ከልጁ ለልጁ ራሱ እንደሆነ፤ በልጁ ያደረገው እያደረገው ያለውና በልጁ ዳግመኛ መምጣትም የሚያደርገው የዘላለሙ አጀንዳው እንደሆነ ልብ ይሏል።

የኢየሱስ ክርስቶስን መከራና ሞት እንዲሁም ትንሳኤ በአጠቃላይ የመስቀሉን ሥራ ሊተካ፣ ሊተካከል ወይም ሊወዳደር የሚችል አንዳች ነገር የለም አይኖርምም። ስለሆነም የአንድ ሰሞን አጀንዳ ብቻ ሳይሆን የዘወትር ርእሳችን ነው። በየዕለቱ ዘወትር የክርስቶስን መከራና ሞት ልናስብ ልንናገር ይገባል። 

ሞቱና ትንሳኤውን ማውራት ማለት ጲላጦስ ፊት ቆመ፣ ተገረፈ፣ ተቸነከረ፣ ...ወዘተ ማለት ብቻ አይደለም ይልቁንም በመስቀሉ ሥራ የተገኘውን ውጤትም ጭምር እንጅ። ጳውሎስ ስለጌታ ራት በጻፈበት መልዕክቱ የጌታ እራትን ዓላማ ሲገልጥ ሞቱን መናገር እንዲሁም ማሰብ እንደሆነ ነግሮናል። « ይህን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ፥ ይህንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁና። » (1ቆሮ 11:26)

ቢጻፍ ዓለም የማይበቃው ቢወራ የማይ'ሰለቸውን የክርስቶስ ነገር የመጽሐፍ ቅዱስ ትኩረት፤ የእግዚአብሔር መልእክት እንደሆነ ሁሉ የኛም የስብከታችን ትኩረት፣ የመዝሙራችንና የጸሎታችን ማዕከል ነው።  የቤተክርስቲያን የዘወትር ርእሷ፤ የሁልጊዜ መልእክቷ የክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ ብቻ ነው ሊሆንም ይገባል።  ጳውሎስ ወሬው ሁሉ እውቀቱ ሁሉ ኑሮውም ጭምር ለዚህ ነበር። (1ቆሮ 1:23 1ቆሮ 2:2 ፊልጽ 3:8-9) 

ሰው የእግዚአብሔርን መልክ እየገለጠ እንዲኖር ቢፈጠርም ፈቃድ ያለው ፍጥረት ስለሆነ ፈቃዱን ተጠቅሞ ለእግዚአብሔር እንዲገዛ፣ እርሱን እንዲያከብር አትብላ የሚል ትዕዛዝ አግዚአብሔር ሰጥቶታል።  (ዘፍ 2:16-17።)

 ነገር ግን በሰይጣን ተንኮል በሔዋን መተላለፍ አዳም በመተላለፍ አትብሉ ከተባሉት ከዛፉ በላ። ከዛፉ በበሉ ጊዜ በእግዚአብሔር ትዕዛዝ ላይ አመጹ። አዳም ትሞታለህ በተባለው መሠረት ወዲያው በስጋ አልሞተም ነገር ግን ከእግዚአብሔር በመንፈስ ተለየ (በመንፈስ ሞተ)። 

የሕይወት ምንጭ ከሆነው ከእግዚአብሔር ተለየ(ሞተ)። ከኤደን ገነት አባረራቸው። እንዲሁም ከእግዚአብሔር ጋር የነበረው ሕብረታቸው ተቋረጠ። በኋላም ዘጠኝ መት ሃምሳ ዓመት ኑሮ በስጋም ሞተ። ኃጢአት ሞትን አመጣበት። በዚህ ምንክያት ኃጢያት በአንድ ሰው ምክንያት ወደ ዓለም ገባ። ሞት የኃጢያት ውጤት ነውና በኃጢያትም ምክንያት ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ።  (ሮሜ 5:12)

መጽሐፍ ቅዱስ ግልጥ በሆነ መልኩ እንደሚነግረን፥ ከተካፈልነው የኃጢአት ተፈጥሮ የተነሳ፦ " ሁሉ ኃጢያትን ሠርተዋል የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሏቸዋል"  ይላል። (ሮሜ 3:23)

 በአንዱ አዳም አለመታዘዝ ሁሉ ኃጢያተኛ ሆነ ከእግዚአብሔር ክብር ጎደለ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ታላቅ ቁጣ ሥር ነው ያለው። የሰው ልጅ ሙት እና የእግዚአብሔር ጠላት ሆነ። (አፌ 2:1-3 ቆላ 1:20-21)

 የኃጢያት ደመወዝ ሞት ነውና ለዘላለም የሕይወት ምንጭ ከሆነው ከእግዚአብሔር ተለይቶ ቆዬ። (ሮሜ 6:23)

እግዚአብሔር ግን የምህረት አምላክ ሰለሆነ ለወደቀውና የዘላለም ፍርድ ለሚጠብቀው የሰው ዘር ሁሉ የምሕረት ዕድል ሰጠን። ስለዚህ በዘላለም ክብር የነበረው አምላክ እኛን ለማዳን በስጋ ተገለጠ። 

ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ መስቀል ላይ የእግዚአብሔር በግ ሆኖ የሁላችንን ኃጢያት ተሽክሞ ምትክ ሆኖ ሊሞት ተሰቀለ። በኛ ላይ ሊያርፍ የነበረ የእግዚአብሔር ቁጣ በክርስቶስ ላይ አረፈ። እኛ መሞት የነበረብንን ሞት እሱ ሞተልን። በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን። አሁን የኃጢያት ስርየት አገኘን። (ሮሜ 3:25)

 "እርሱንም እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው፤ ይህም በፊት የተደረገውን ኃጢአት በእግዚአብሔር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፥" ስለዚህ ክርስቶስ በሞቱ የኃጢያታችን ዕዳ ከፈለልን፤ እኛን ለማጽደቅ ደግሞም በአዲስ ማለትሜ በራሱ ሕይወት እንድንመላለስ ከሙታን ተነሳ። (ሮሜ 4:24-25 ኤፌ 2፣5)

 ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን በቀራንዮ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ለኃጢአታችን መስዋዕትን ሲከፍል የሚከተሉት ሦስት ነገሮች ተከናውነውልናል፡፡

የመጀመሪያው የኃጢአት ሥራ እና የእግዚአብሔርን ጽድቅ ነው። 

መስቀሉን ስንመለከት የኃጢአት ሥራ አስፈሪነትና አስቀያሚነት ይታየናል፡፡ የሰው ልጅ ኃጢአት ነው ክርስቶስን ከክብር ዙፋኑ ላይ ወደ እኛ እንዲመጣ ያደረገው፡፡ የሰው ኃጢአት ነው እርሱን የሀዘን ሰው ያደረገው፡፡ እኛን አሁን ባለንበት አሰቃቂ ክፋት እልቂት ጭከናና ጦርነት ሁኔታ ውስጥ የጣለን ኃጢአት ነው፡፡ ኃጢአት በእግዚአብሔር ፊት የተጠላ ነው፣ ስለዚህ ኃጢአትን ይቀጣ ዘንድ ልጁ በመስቀል ተንጠለጠለ። ኃጢአት ለእግዚአብሔር ባህሪ የማይስማማው መሆኑን ኃጢአትን በክርስቶስ ስጋ ላይ ሲቀጣ እንገነዛባለን እናም እግዚአብሔር ጻድቅ ነው። ሮሜ 3:25-26

ሁለተኛው የእግዚአብሔር ፍቅር ነው። 

1ዮሐ 4:10 የታረደውን በግ በመስቀሉ ላይ ሆኖ ስናይ ሌላ የምናስተውለው ነገር የእግዚአብሔርን ፍቅር ነው። እኛ የሰው ልጆች በኃጢአት የቆሸሸ ሕይወት ያለን ነን፡፡ እኛ እራሳችንን ለኃጢአት ሸጠናል፣ በኃጢአት ውስጥ ዘቅጠናል፣ ጥላቻ፣ ነፍስ ግድያ፣ ስርቆት፣ ውሸት፣ አመንዝራ፣ ወዘተ ታሪካችንን ሞልቶታል፡፡ ከእነዚህ ከወደቅንባቸው ኃጢአቶች የተነሳ ንፁህና ፍፁም የሆነው እግዚአብሔር የዘላለም ፍርድ ሊሰጠን ይገባዋል፡፡ 

ነገር ግን በመስቀል ላይ የታረደውን በግ ስንመለከት የእግዚአብሔርን ፍቅርና የምህረቱን ብዛት እንገነዘባለን፡፡ ጻድቅ እግዚአብሔር ፍርዳችንን በንፁህ ጌታ ኢየሱስ ላይ አድርጎ እኛን ለማዳን እርሱ በእኛ ምትክ እንዲታረድ አሳልፎ ሰጠው፡፡ ይህ ከኛ የተነሳ ሳይሆን ከእርሱ ፍቅር ብቻ የተነሳ እንደተደረገ ነው፡፡ ታዲያ ይህ ምን ዓይነት ፍቅር ነው፡፡ እኛን ጠላቶቹን እግዚአብሔር ወደደን። ይህንን ፍቅር በቃላት ለመግለፅ አይቻልም፡፡ ምን ማድረግ ይገባናል? መጽሐፍ ቅዱሳችን በውድ ልጁ እንዲያው የሠጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይኼን አደረገ ስለሚል በምስጋና እናወድሰው። (ኤፌ 1:6)


ሦስተኛ የእግዚአብሔር የዘላለም ዕቅድ ነው። 

አንዳንዶች የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ሞት እንደ ድንገተኛ አደጋ አድርገው ሊቆጥሩት ያስባሉ፡፡ በድንገት አዳምና ሔዋን ስለተሳሳቱ እግዚአብሔር እቅዱ እንዳይበላሽበት "በል እስኪ ሂድ ልጄ አድናቸው" ተብሎ የመጣ ድንገተኛ ሃሳብ አይደለም። ሲጀመርም ከዘላለም እግዚአብሔር ልጆቹ እንድንሆን ያሰበው በልጁ ስራ ነው። (ኤፌ 1:5)

 ይኼን ሃሳብ ጴጥሮስ በመልክቱ ያጠናክረዋል። "ከአባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከከንቱ ኑሮአችሁ በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ። ዓለም ሳይፈጠር እንኳ አስቀድሞ ታወቀ፥ ነገር ግን እምነታችሁና ተስፋችሁ በእግዚአብሔር ይሆን ዘንድ፥ ከሙታን ባስነሣው ክብርንም በሰጠው በእግዚአብሔር በእርሱ ስለምታምኑ ስለ እናንተ በዘመኑ መጨረሻ ተገለጠ። (1ጴጥ 1:18-21)

 ይህ የሚያሳየው የእርሱ የመስቀል ሞት በእግዚአብሔር ጥንት የታቀደ፤ የታሰበበት፣ ነገር ግን በድንገት ያልተፈፀመ መሆኑን ነው፡፡

በልጁ ሞት የኃጢአት ዕዳችን ተከፍሏል። ከእግዚአብሔር ቀጣ ተርፈናል። በልጁ ከሙታን መነሳት እኛም አብረን ከሞት መንደር ተነስተናል። የራሱን የእግዚአብሔርን ሕይወት ተካፍለናል፣ ጸድቀናል፣ ተቀድሰናል፣ ልጆች ሁነናል.....ወዘተ ይኼ ሁሉ በልጁ ሞት እና ትንሳኤ አግኝተን እንዴት ስለእርሱ አናወራ!

❖ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል ፦(ዮሐ 16:13-15)

የእግዚአብሔር መንፈስ ምንድነው የሚገልጠው?

በእኛ ውስጥ ያለው መንፈስ ቅዱስ ከአብ ና ከወልድ ጋር ብቻ ሳይሆን ቤተክርስቲያንን ከአካሏ ከክርስቶስ እንዲሁም በተለያዩ የምድር ስፍራ ካሉት ከምናውቃቸውም ከማናውቃቸውም አማኞች ጋር በሕይወት እንድንተሳሰር አድርጎናል። 

መጽሐፍ ቅዱስ አይሁድ ብንሆን የግሪክ ሰዎችም ብንሆን ባሪያዎችም ብንሆን ጨዋዎችም ብንሆን እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ አንድ አካል እንድንሆን ተጠምቀናልና። ሁላችንም አንዱን መንፈስ ጠጥተናል እንዲል፤ (1ቆሮ 12:13።)

ከዚህ መንፈስ ቅዱስ የተነሳ እኛ በአብና በወልድ ውስጥ  እንዲሁ አብና ወልድም በእኛ ውስጥ ለመሆን ችለዋል። "ከመንፈሱ ስለ ሰጠን፥ በእርሱ እንድንኖር እርሱም በእኛ እንዲኖር በዚህ እናውቃለን"።  (1ዮሐ 4:13።)

የእግዚአብሔር መንፈስ በእኛ ውስጥ ከመሆኑ የተነሳ የክርስቶስ ወገን ሁነናል። (ሮሜ 8:9።) ይሁን እንጅ ይህ የእግዚአብሔር መንፈስ በእኛ ውስጥ ሁኖ ዝም ብሎ መቀመጥ ሳይህን የሚሠራው ሥራ የሚገልጠው ነገር አለ። 

መንፈስ ቅዱስ  በእኛ ሕይወት የሚገልጠው በልጁ የተገለጠውን የአብን ፍቅር ወይም ልጁን ኢየሱስን ነው። "በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም። (ሮሜ 5:5 )

እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል። እርሱ ያከብረኛል፥ ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና። ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ ስለዚህ፡— ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋል አልሁ።"   (ዮሐ 16:13-15)

መንፈስ ቅዱስ በእኛ ሕይወት የሚገልጠው የዘላለም ሕይወትን ነው። የሰማዩን መንግሥት ነው። የማያልፈውን ነው። በአጠቃላይ መንፈስ ቅዱስ የሚገልጠው ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው እርሱ ሲገለጥ ደግሞ በርግጥም አብም ይገለጣል። መንፈስ ቅዱስ አብን ይገልጣል ስንል የአብን የዘላለም ሐሳብ ማለት ነው። ይኼም ሐሳቡ በልጁ የመስቀል ስራ የጀመረው፤ መንፈሱን በመላክ እየሠራ ያለው እንዲሁም በልጁ ዳግመኛ መገለጥ የሚጠቀልለውን የዘላለሙን ሐሰብ ማለት ነው።

❖ዘመኑን ማወቅ፦

   ዘመኑን ማወቅ፦
          (ሮሜ 13:11-14)

"ከእንቅልፍ የምትነሡበት ሰዓት አሁን እንደ ደረሰ ዘመኑን እወቁ፤ ካመንንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቦአልና። ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ። በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን፤" (ሮሜ 13:11-13)

ሰላም ለእናንተ ይሁን። ጳውሎስ በወንጌል ስለተገለጠው የእግዚአብሔር ጽድቅ በሚያወራበት በሮሜ መልዕክት ውስጥ ሰው እንዴት እንደሚጸድቅ፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ጽድቅ በተለያየ አቅጣጫ ሲገለጥ ምን እንደሚመስል ዘግቧል። በዚህ በመረጥነው ክፍልም ዘመንን ስለማወቅ ይነግረናል። እኛም በሚከተሉት ሁለት ንዑስ ርዕስ ከፍለን እንመለከታለን።

1. ዘመኑ ምንድነው?፣

ዘመንን ማወቅ ታላቅ ጥበብ ነው። ዘመንን ማወቅ ጥቅም እንደነበረው የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ይነግረናል። ለምሳሌ ዳዊት የእስራኤልና የይሁዳ ንጉሥ ከሆነ በኋላ እስራኤል የሚገባውን ያደርግ ዘንድ ዘመኑን የሚያውቁ ሁለት መቶ ከይሳኮር ልጆች አለቆች ነበሩ። (1ዜና 12:32።) 

ዛሬም በአዲስ ኪዳን ዘመንን ማወቅ የሚገባውን እናደርግ ዘንድ አስፈላጊ ነገር ነው። ዘመንን ያለማወቅ ችግር የክርስትናችንን ሩጫ እንደሚገባ እንዳንሮጥ መሰናክል ከሚሆኑብን ነገሮች አንዱ እና ዋናው  ነው።

 መቼም ዘመኑ የተገለባበጠበት፥ ዘመኑንም  ማስተዋል የተሳነው ክርስቲያን እንደዚህ ዘመን የበዛ አይመስልም። 

ጳውሎስ በዚህ መልዕክቱ ዘመኑን እወቁ የሚለን ከእኛ አንጻር ነው። ዘመኑ ለእኛ ለአማኞች ምንድነው? ዘመኑስ ምን ዓይነት ነው? ይኼን ያላስተዋለ አማኝ ብዙ ነገሩን ይስታል። እግዚአብሔር አብ ከታላቅ ምሕረቱ የተነሳ በልጁ ወንጌል ለጠራን በክርስቶስ የመስቀል ሥራ አምነን ለዳንን ለእኛ ለአማኞች ዘመኑ ምንድነው? ዘመኑን ማወቅ ካለብን በእርግጥም ለእኛ ለአማኞች ዘመኑ ከእንቅልፍ የምንነሳበት ሰዓት ነው ይለናል።

ከእንቅልፍ መነሳት ማለት ምንድነው?

ይኼን ለማብራራት ጳውሎስ እንዲህ ይለናል። "ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል"። 

 የሌሊትን ማለፍ እና የቀንን መቅረብ ሁኔታ በአትኩሮት ስናጤን በርግጥም ጳውሎስ ምን ሊለን እንደፈለገ ይገባናል። ጳውሎስ በዚህ ክፍል ሦስት የተለያዩ ጊዜዎችን ይነግረናል። ጊዜዎቹም ሌሊት፥ ቀን እና በሌሊትና በቀን መካከል ያለ ከእንቅልፍ የምንነሳበት ጊዜ ነው። ሌሊቱ የሚለው በክርስቶስ ከማመናችን በፊት የነበረውን በጨለማ ወይም በኃጢአት የነበርንበት ጊዜ ነው። ቀን የሚለው ደግሞ የክርስቶስ መምጣትና ከዚያ በኋላ ያለውን የዘላለም ዘመንን ነው። ሦስተኛው ደግም ከእንቅልፍ የምንሳበትን ወቅት ነው።

በእርግጥ ከእንቅልፍ የመነሻ ጊዜ በአሁኑ የሰለጠነው ዓለም የተለወጠ ቢሆንም ያኔ እዚያ መልክቱ የተጻፈበትን ዘመን ስንመረምር ሰዎች ከእንቅልፋቸው የሚነሱት ከሌሉቱ 10:30 ጀምሮ እስከ 11:30 ባለው ውስጥ እንደሆነ ታሪካዊ ዳራዎች ያመለክታሉ። በእርግጥ አሁንም ራቅ ወዳሉ የገጠር የሃገራችን ክፍሎች ስንሄድ ሰዎች ከእንቅልፋቸው የሚነሱት ከላይ በጠቀስኩት የሰዓት ክልል ውስጥ ነው።

ይኼ ከእንቅልፍ የመነሻ ጊዜ የእኛን ከጨለማ ማለትም ከኃጢአት ባርነት ወጥተን አሁን በእምነት በክርስቶስ ድነን ያለንበትን ጊዜ ይወክላል።  አዎ!  አሁን በክርስቶስ አምነን ከዚያ ከጨለማ ከሌሊቱ ጊዜ ወጥተናል። 

መጽሐፍም "ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን.." ይለናል። (1ጴጥ 2:9።)  በጌታም ብርሃን ሁነናል ነገር ግን እንደዚህ የሮሜ ክፍል አውድ ወደሙሉ ቀን ወይም ሙሉ ብርሃን ገና አልደረስንም። ወገግታው ላይ ነን።  ለዚያም ነው "ቀኑ" ተብሎ የጠራውን የክርስቶስን ዳግመኛ መገለጥ "ቀኑ ቀርቧል" የሚለን ጳውሎስ።

2. ለምንድነው ዘመኑን እንድናውቅ የተፈለገው?

ጳውሎስ ለምንድነው ዘመኑን እንዲያውቁ ወይም እንድናውቅ የፈለገው ለሚለው ጥያቄ  መልሱ ለዘመኑ እንደሚገባ እንድንኖር ነው። ዘመኑን አውቀናል እርሱም ከእንቅልፍ መነሻ ነው። 

ከእንቅልፉ የሚነሳ ሰው ደግሞ የሌሊት ልብሱን አውልቆ የቀኑን ልብስ ይለብሳል። ለዚያም ነው ጳውሎስ "ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ፤ " የሚለን። 

ሌሊቱ ስላለፈ ቀኑ ስለቀረበ የሌሊቱን ልብስ ማለትም የጨለማን ሥራ በማውለቅ የቀን ልብስ መልበስ አለብን። 

እኛም ሌሊቱ(በክርስቶስ ከማመናችን በፊት የነበረው ጊዜ) አልፎ ከእንቅልፍ የምንነሳበት ጊዜ ላይ ነን። "ቀኑ" ማለትም የክርስቶስን ምጻት ከፊት ለፊታችን ቀርቧል። ታዲያ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር ልንለብስ ይገባል። 

ጳውሎስም "በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን፤" ይለናል። ይልቁንም ካመንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን እየቀረበ ስለሆነ (የስጋ ትሥሳኤ) ኢየሱስን ልንለብስ ይገባል። 
ኢየሱስን መልበስ ሲባል  የኢየሱስን ባህሪ ፍቅርን፣ ጽድቅን፣ ቅድስናን..በሕይወታችን መግለጥ ነው።

Monday, June 1, 2020

❖የመዳን ወንጌል እና የተስፋው መንፈስ፦


«እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፣ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል ሰምታችሁ፣ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፣ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤»ብሏል /ኤፌ.1፡13/፡፡

1. ሰው ሁሉ ኃጢአተኛ ነው፦

ለሞት በሚያደርስ በሽታ እንደተያዙ የማያውቁ ሕሙማን ወደ ሐኪም ዘንድ ሄደው ለመታከምም ሆነ መድኃኒት ለማግኘት እንደማይንቀሳቀሱ ሁሉ ኃጢአተኛ መሆናቸውንና ኃጢአትም ዘላለማዊ ሞትን የሚያስከትል መሆኑን የማያውቁ ብዙ ሰዎች ስለመዳን መንገድ ለመረዳት ፍላጐት ላይኖራቸው ወይም ጊዜ ላይሰጡ ይችላሉ፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ግን ማንኛውም ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ እንደሚከተለው ይናገራል፡፡

«ሁሉ ዐመፁ በአንድነትም ረከሱ፤ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም እንኳ የለም»/መዝ.13፡3/፡፡

«ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፤ አስተዋይም የለም፤ እግዚአብሔርንም የሚፈልግ የለም፤ ሁሉ ተሳስተዋል፤ በአንድነትም የማይጠቅሙ ሆነዋል፤ ቸርነት የሚያደርግ የለም፤ አንድ ስንኳ የለም»/ሮሜ.3፡11-12/፡፡

«... ልዩነት የለምና፤ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና፤ የእግዚአብሔርም ክብር ጐድሏቸዋል»/ሮሜ.3፡22-23/፡፡

ከእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንደምንረዳው ማንኛውም ሰው ኃጢአተኛ እንደሆነ ነው፡፡ ሰው ሁሉ ኃጢአተኛ ሊሆን የቻለውም በኃጢአት ከወደቀው ከአንድ ሰው ማለትም ከአዳም የተወለደ በመሆኑ ነው፡፡ ኃጢአት ወደ ዓለም የገባውም በዚሁ በመጀመሪያው ሰው በኩል ነው፤ አዳም የተሰጠውን ትእዛዝ ቢተላለፍ ሞትን እንደሚሞት አስቀድሞ ተነግሮት ነበር /ዘፍ.2፡16-17/፡፡ ስለሆነም ትእዛዙን በተላለፈ ጊዜ ኃጢአት ወደ ዓለም ከመግባቱም ሌላ በኃጢአት ምክንያት የተፈረደው የሞት ፍርድ ለሰው ሁሉ ሊደርስ ችሏል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ይህን ሲናገር «ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ፤ በኃጢአትም ሞት፤ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ» ይላል /ሮሜ.5፡12/፡፡ ስለዚህ ማንኛውም ሰው በኃጢአት ከወደቀው ከመጀመሪያው ሰው ስለተወለደ ኃጢአተኛ ከመሆኑም ሌላ የሞት ፍርድ የተፈረደበትም ነው፡፡ ሆኖም እግዚአብሔር ለሰዎች ካለው ፍቅር የተነሣ ሰዎች ከዚህ ዘላለማዊ ፍርድ ይድኑ ዘንድ አንድ ልጁን አዳኝ አድርጎ ወደ ዓለም ልኳል፡፡

2. የእግዚአብሔር ፍቅር፦

እግዚአብሔር ጻድቅ ከመሆኑ አንጻር በኃጢአት ላይ የሚፈርድ እውነተኛ ፈራጅ የመሆኑን ያህል ኃጢአተኞችን ለማዳን የሚወድ የፍቅር አምላክም ነው፤ ይህ ፍቅሩ የተገለጠውም አንድ ልጁን ለእኛ በመስጠቱ ነው፤ መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ሲገልጽ «በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፤ ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና» ይላል /ዮሐ.3፡16-17/፡፡ ስለዚህ ኃጢአተኝነቱን ያወቀና በፍርድ ሥር እንዳለ የተረዳ አንድ ሰው ተስፋ ቈርጦ ከእግዚአብሔር ከመራቅ ይልቅ እግዚአብሔር ልጁን እስከመስጠት ድረስ እንደወደደው ሊገነዘብ ይገባል፡፡

ስለዚህይ አሁን ያለነው በምንም ሁኔታ ውስጥ ቢሆን እግዚአብሔር ልጁን ስለ እኛ ለሞት አሳልፎ እስኪሰጥ ድረስ የወደደን  መሆኑን ልናውቅ ይገባናል፡፡ 

ክርስቶስ በመስቀል ላይ የሞተው ሞት ይህን የእግዚአብሔርን ፍቅር ያስረዳል፤ መጽሐፍ ቅዱስ ይህን ሲናገር፦  «ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና፡፡ ስለ ጻድቅ የሚሞት በጭንቅ ይገኛልና፤ ስለቸር ሰው ግን ሊሞት እንኳ የሚደፍር ምናልባት ይገኝ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቷልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል» ይላል /ሮሜ.5፡6-8/፡፡ 

እግዚአብሔር ይህን ያህል እኛን  ኃጢአተኞቹን የሚወደን  ከሆነ እኛ ደግሞ እርሱ የሚያቀርብልንን የፍቅር ጥሪ ልንቀበል ይገባናል፡፡ 

እርሱ የሚጠራን እኛን ከዘላለም ጥፋት ለማዳን ነው፡፡ ስለዚህ የቀረበልንን የፍቅር ጥሪ ብንቀበል ለዘላለም የምንድነው እኛው ራሳችን ነን፡፡

3. የኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት፦

ሰው ከኃጢአትና ከዘላለም ሞት እንዲድን እግዚአብሔር ያዘጋጀው የመዳን መንገድ አንድ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው።  /ዮሐ.14፡6/፡፡ 

ኢየሱስ የሚለው የጌታችን ስም ትርጉምም አዳኝ ማለት ነው፡፡ በማቴ.1፡21 ላይ፦  «እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ» የሚለው ቃል ይህንን ያስረዳል። 

 እርሱ ወደ ዓለም የመጣበት ዋነኛ ዓላማም ሰውን ለማዳን እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ሲያስረዳ፦  «የሰው ልጅ የጠፋውን ለማዳን መጥቷልና /ማቴ.18፡11፤ ሉቃ.19፡10/፤ እንዲሁም፦  «ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው» /1ጢሞ.1፡15/ ይላል፡፡

 ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣበትን ይህንን ሰውን የማዳን ዓላማ ለመፈጸም እስከሞት ድረስ ታዝዟል፤ እርሱ በመስቀል ላይ የሞተው የሁላችንን ኃጢአት ተሸክሞና የሁላችን ምትክ ሆኖ ነው፤ «... እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ» /1ጴጥ.2፡24/ «አንዱ ስለሁሉ ሞተ፤ እንግዲያስ ሁሉ ሞቱ» /2ቆሮ.5፡14/ የሚሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ንባቦች ይህን ያረጋግጣሉ። 

 እርሱ ኃጢአት የሌለበት በመሆኑ ስለኃጢአተኞች መሞትና ኃጢአተኞችን ማዳን ተችሎታል፤ ኃጢአት ያለበት ማንም ቢሆን ይህን ማድረግ አልተቻለውም፡፡ ስለዚህ በሰማይም ሆነ በምድር ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አዳኝ የለም፤ መጽሐፍ ቅዱስ ከእርሱ በቀር ሌላ አዳኝ እንደሌለ አስረግጦ ሲናገር «መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና» ይላል /የሐ.ሥ.4፡12/፡፡ 

ከኃጢአተኝነታቸው የተነሣ በሞት ፍርሃት ውስጥ ለሚኖሩት ሁሉ ይህን የኢየሱስ ክርስቶስን ብቸኛ አዳኝነት መስማት ታላቅ የምስራች ነው፡፡ ይህም «የመዳን ወንጌል» ይባላል፡፡ 

ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች ሲጽፍ «እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፣ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል ሰምታችሁ፣ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፣ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤» ብሏል /ኤፌ.1፡13/፡፡ ይህም ቃል የመዳን ወንጌልን ተቀብለው በክርስቶስ ያመኑት ሁሉ የዘላለም መዳንን ከማግኘታቸውም በላይ በመንፈስ ቅዱስ መታተማቸውንም የሚያረጋግጥ ነው፡፡

መዳንንም  የምናገኘው በተሰተን ጸጋ ነው እንጂ መልካም ሥራን በመሥራታችን አይደለም። 
መጽሐፍ ቅዱስ ይህን በተመለከተ ሲናገር፦

 «ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለጠጋ ስለሆነ፣ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወትን ሰጠን፤ በጸጋ ድናችኋልና፣.. .. ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም» /ኤፌ.2፡4-9/ ይላል፡፡ 

እንዲሁም በሌላ ስፍራ «ነገር ግን የመድኃኒታችን የእግዚአብሔር ቸርነትና ሰውን መውደዱ በተገለጠ ጊዜ፣ እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፣ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለነበረው ሥራ አይደለም፤ ያን መንፈስም በጸጋው ጸድቀን በዘላለም ሕይወት ተስፋ ወራሾች እንድንሆን፣ በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ አትርፎ አፈሰሰው፡፡ ቃሉ የታመነ ነው» የሚል ቃል እናነባለን /ቲቶ3፡4-7/፡፡ 

ስለሆነም መዳን በጸጋ እንጂ በሥራ እንዳልሆነ ከእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባቦች ልንገነዘብ እንችላለን፡፡ መልካም ሥራ በኢየሱስ ክርስቶስ አምነን ከመዳናችን የተነሣ የምንሠራው ነው እንጂ መዳንን ለማግኘት የምንሠራው አይደለም፡፡ ሆኖም ከዳንን በኋላ መልካም ሥራን በመሥራት መዳናችን ይገልጣል፡፡ 

በኤፌ.2፡10 ላይ «እኛ ፍጥረቱ ነንና እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን» ተብሎ በተጻፈው ቃል መልካም ሥራ በክርስቶስ አዲስ ፍጥረት የመሆናችን ውጤት መሆኑን መረዳት ትችላለህ፡፡ ስለዚህ ሰው ሊድን የሚችለው በእግዚአብሔር ጸጋ ብቻ መሆኑን ልናውቅ ይገባናል፡፡ ከእኛ  የሚፈለገው ኃጢአተኝነታችንን በማመን ንስሐ መግባትና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ብቻ ነው፡፡ ይህንንም ለማድረግ ጊዜ ሳናጠፋ አሁኑኑ ልንወስ ይገባናል፡፡ 

መጽሐፍ ቅዱስ «እነሆ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ የመዳን ቀን አሁን ነው» ይላልና /2ቆሮ.6፡2/፡፡

በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መሰብሰብ፦

ስለጌታችን ስለኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት ሰምተው በእርሱ ያመኑና የዳኑ ሰዎች ከማያምኑት ተለይተው  በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መሰብሰብ አለባቸው፡፡ 

ጌታችን በስሙ ስለመሰብሰብ ሲናገር፦  «ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ እኔ በመካከላቸው እሆናለሁና» ብሏል /ማቴ.18፡20/፡፡ 

ከማያምኑት ተለይተው በኢየሱስ ስም የሚሰበሰቡትን እግዚአብሔር በዚያ ስፍራ ይቀበላቸዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ከማያምኑት ስለመለየት በሚናገርበት ክፍል ውስጥ «ስለዚህም ጌታ፡- ከመካከላቸው ውጡና የተለያችሁ ሁኑ ርኵሱንም አትንኩ» ይላል፤ ሁሉን የሚገዛ ጌታ እኔም እቀበላችኋለሁ ለእናንተም አባት እሆናለሁ፤ እናንተም ለእኔ ወንድ ልጆችና ሴት ልጆች ትሆናላችሁ ይላል፡፡» በማለት ይናገራል /2ቆሮ.6፡17-18/፡፡ እንዲሁም በዕብ.13፡13 ላይ «እንግዲህ ነቀፌታውን እየተሸከምን ወደ እርሱ ወደ ሰፈሩ ውጭ እንውጣ» በማለት የአማኞች ስፍራ የት እንደሆነ በግልጽ ይነግረናል፡፡ 

ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም «እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ» በማለት ሰዎችን ወደ ራሱ ይጠራል /ማቴ.11፡28/፡፡

  ውዳሴና አምልኮት የዘላለምን ሕይወት ለሰጠን ለነፍሳችን እረኛና ጠባቂው ክርስቶስ ይሁን!!!