Sunday, December 27, 2020

❖ ያለ ክርስቶስ የሆነ ባለ ጠግነት፦

በክርስቶስና ያለ ክርስቶስ የሆነ ባለ ጠግነት፦

1ኛ/ ራዕይ 2:9፦ "መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ ነገር ግን ባለ ጠጋ ነህ።
2ኛ/ ራዕይ 3:17፦ "ሀብታም ነኝና ባለ ጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም የምትል ስለ ሆንህ ጎስቋላና ምስኪንም ድሀም ዕውርም የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ•••"

እግዚአብሔር ባለ ጠጋ የሆነ አምላክ ነው። ከእርሱ ባለ ጠግነት የተነሳ በጎ ስጦታውንና በረከቱን ለሚወዱትና ለሚፈሩት ይሰጣል። በዓለም ብዙ ባለጠግነት አለ። የዚህ ዓለም ባለጠግነት ከንቱ ነው። በባለጠግነቱም ብዛት ነፍሱ ሊያድን የሚችልና የእግዚአብሔርን መንግስት ሊወርስ የሚችል የለም።
(ማቴ 16:26 በማር 10:25)
ሁለት ዓይነት ባለጠግነት በአማኞች ዘንድ እናገኛለን፦
የመጀመሪያው ባለጠግነት በሰምርኔስ አማኞች የተገለጠ ነው። እነዚህ አማኞች በታላቅ መከራና በጥልቅ ድህነት ውሰጥ ሆነው ፍፁም መከራን እየተቀበሉ እሰከ ሞት ድረስ ይታመኑ ዘንድ የበረቱ ናቸው።ምንም መከራ ቢያገኙ ድህነት ቢፈትናቸውም እግዚአብሔር ግን ባለ ጠጎች ናችሁ ይላቸዋል።

ይህ ባለጠግነት፦
1ኛ/ የእምነት ባለጠግነት ነው።መከራና ድህነትን ተቋቁመው በእምነት እግዚአብሔርን እየመሰሉ በፅድቅ የሚኖርበት ነው። "እግዚአብሔር በእምነት ባለ ጠጎች እንዲሆኑ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን መንግስት እንዲወርሱ የዚህ ዓለም ድሆች አልመረጠምን?(ያዕ 2:5)

2ኛ/ መንፈሳዊ በሆኑ ነገሮች ሁሉ ያለ ባለጠግነት ነው።አማኞች የመንፈሳዊ ፀጋ ተካፋዮች ናቸው። ክርስቶስ እሰኪ መጣ ድረስ አንድም የፀጋ ስጦታ አይገድልም። "በነገር ሁሉ በቃልም ሁሉ በእውትም ሁሉ በእርሱ ባለ ጠጎች እንድትሆኑ ተደርጎችኋልና።(1ኛ ቆሮ 1:6)
በክርስቶስ የሆነ ባለ ጠግነት ስጦታ ነው።በእርሱ•••••ተደርገችኋል በማለት የሰውን ሰራና ልፋት ፋይዳ ቢስ ያደርገዋል።

3ኛ/ በማያልፍ በበጎ ስራ ያለ ባለጠግነት ነው።አማኞች በኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል ቤዛነት የፀጋ ሰራ የዳኑ ናቸው። እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካም ስራ በጎ ስራ በእነርሱ ይገለጣል። "በሕያው እግዚአብሔር እንጂ በሚያልፍ ባለጠግነት ተስፋ እንዳያደርጉ,,,,,,,በበጎ ስራ ባለጠጎች እንዲሆኑ ሊረዱና ሊያካፍሉም የተዘጋጁ እንዲሆኑ ምከራቸው። (1ኛ ጢም 6:17-19)
እነዚህ ባለ ጠግነቶች በስምርኔስ አማኞች ታይተዋል።በዓለም ድሆች ሲሆኑ በመንፈሳዊ ነገር ብዙዎችን ባለ ጠጎች የሚያደርጉ ናቸው።2ኛ ቆሮ 6:8 ስለዚህ እግዚአብሔር በስጦታው በአማኞች በሚታየው ደስ ይለዋል።

ሁለተኛው ባለጠግነት ግን አማኞች ነን እያሉ በባለጠግነት አቆጥቁጠው ክርስቶስን ከቤቱ ወደ ደጅ የሚያወጡ ናቸው።

ይህ እግዚአብሔር ደስ አያሰኝም። በሎዶቅያ የታየው ይህ ነው።አንዳች አያስፈልገንም ባለጠጎች ነን በማለት ራስ የሆነውን ክርስቶስ አሰወጡ።ከደጅ ቆሞ ባለጠጋው ደጃቸውን ያንኳኳል። "እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ ። (ራዕ• 3:20)
ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ ከየትኛው ባለጠግነት ዘንድ ነን? እግዚአብሔር ደስ ከሚያሰኘው በእምነት በመንፈሳዊና በበጎ ስራ የሆነ ባለጠግነት? ወይስ ክርስቶስን ወደ ውጭ የሚያደርግ የዚህ ዓለም ባለጠግነት?
ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን!!

Thursday, September 17, 2020

❖ቤተክርስቲያንና አዲስ ዓመት፦


መለወጥ የሌለበት፣ ጸንቶ የሚኖረው እግዚአብሔር ዘመናትን ያፈራርቃል።

ዳንኤል፦ "ጊዜያትንና ዘመናትን ይለውጣል፤.."እንዳለው( ዳን 2፥2) ትናንትን በዛሬ ተክቶ፥ ዛሬን ደግሞ በነገ ያስረጃል፡፡ በጊዜ ዑደትም ውስጥ ብዙ ዓመታት አልፈው ብዙ አዲስ ዓመታት መጥተዋል፡፡ ይህ ሁሉ ቢሆንም እግዚአብሔር በባሕሪው ነበር፤ አለ ይኖራልም።

ዓመታት ሂደው ዓመታት ቢመጡም በእግዚአብሔር ዘንድ በየዓመቱ የሚቀያየር ሀሳብ የሚለዋወጥ አጀንዳ ፈጽም የለም፡፡ ዘላለማዊው እግዚአብሔር በዘላለም እቅዱ መሰረት ሁሉን ያከናውናል። በዕቅዱም መሰረት ይኼው በክርስቶስ ኢየሱስ በልጁ የመስቀል ስራ ሰዎችን ወደራሱ እያቀረበ ነው። በየዘመኑም ይኼን ለማድረግ ይተጋል። ይኼን ሃሳቡንም ለመደምደም በዘመን ፍጻሜ በክርስቶስ ኢየሱስ በሰማይም በምድርም ያለውን ሁሉ ሊጠቀልል አቅዷል። (ኤፌ 1፥10)።

ታዲያ ዘመናት ሲፈራረቁ ሁሉ ነገር ወደ እግዚአብሔር የዘመን ፍጻሜ ዕቅዱ ይፈጥናል። በዚህ መፈራረቅ ውስጥም ለዕቅዱ የወሰናቸው የመረጣቸው በተወሰነላቸው ዘመን እና ቦታ ሁነው ወደልጁ መንግስት ይፈልሳሉ። ለዚያም ነው የዘመናት መፈራረቅ ሰው የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ ዕቅዱን የሚከውንበት እንደሆነ እንዲያስተውል ዕድል የሚሰጥ እንዲሁም በልጁ የሠራውን እንዲያምን፣ እንዲያደንቅ እና መግቦቱንም እንዳይረሳ ያደርጋል የምንለው።

የሰው ልጆች አሮጌ የተባለው ዓመት አልፎ አዲስ ዓመት ሲመጣ እና ከዚህ ጋር በማያያዝ በማቀዳቸው ሕይወታቸው እንደሚለወጥ ያስባሉ ። በእርግጥ የዓመታት መለዋወጥ የሰውን ሕይወት ይለውጣልን? በመሠረቱ ሰዎች ብዙ ነገሮችን ማቀዳቸው ክፉ አይደለም። ለስጋዊ ኑሯቸው ሊጠቅም ይችላል። ነገር ግን ሕይወታቸውን ሊለውጥ አይችልም። የሰውን ሕይወት የጌታ ኢየሱስ የመስቀሉ ስራ እንጂ የሚለዋወጥ ዓመትም ይሁን ይኼን ተከትሎ ሰዎች የሚያቅዱት ዕቅድ አይለውጠውም፡፡

ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ የመስቀል ስራ አምነው ዳግመኛ የተወለዱትን ብልቶቿን ሁሉ የመንፈሳዊ ሕይወት መለወጥ መሻሻልና ማደግ መስራት አለባት፡፡ ይኼን ተግባራዊ ለማድረግም የአሮጌውን ሰው ባህሪ አውልቀው አዲሱን ሰው መልበስ እንዲችሉ በቃሉ አማኞችን ልታንጽ ያስፈልጋል፡፡

ለዚያም ነው ቅዱስ ጳውሎስ፦ «ፊተኛ ኑሯችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ። በአእምሯችሁ መንፈስ ታደሱ፤ ለእውነትም ለሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ።» የሚለው። (ኤፌ 4፥22-24)።

በእርግጥ የአዲሱ ሰው ማንነት በውስጣችን አለ። ጳውሎስ በመልክቱ፦ «አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር ገፍፋችሁታልና፤ የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል እውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታልና» ብሏል። (ቆላ 3፥10)። ነገር ግን ይህ የአዲሱ ሰው ባህርይ ሊገለጥ ሊታይ ይገባል። ይህም ባህርይ ፍቅር፣ ጽድቅ፣ ቅድስና በአጠቃላይ እግዚአብሔርን መምሰል ነው። ቤተክርስቲያን ይኼን ስታደርግ እንደቃሉ በዓለም እንደ ብርሃን ትታያለች።
ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን!!!

Saturday, September 12, 2020

❖የባሕረ ሐሳብ ቊጥር፦

በአብ ስም አምነን አብን ወላዲ ብለን በወልድ ስም አምነን ወልድን ተወላዲ ብለን በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን መንፈስ ቅዱስን ሠራጺ ብለን ምንም ለአጠይቆ አካላት ሦስት ስላልነ በባሕርይ በሕልውና አንድ አምላክ ብለን አምነን ጸሎቱ ልመናው በረከቱ ክብሩ ይደርብንና የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ድሜጥሮስ የተናገረውን የባሕረ ሐሳብ ቊጥር መጽሐፍን በእግዚአብሔር አጋዥነት እንጀምራለን፡፡


💥 እግዚአብሔር እንደዛሬው ኹሉ አንድነቱ ሦስትነቱን ሳይጠቀልለው ሦስትነቱ አንድነቱን ሳይከፍለው በአንድነት በሦስትነት ሳለ ክብሩ በብቻው እንደቀረ ዐውቆ ዓለምን ልፍጠር ብሎ አሰበ፤ አስቦም አልቀረ ሰውና መላእክትን ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ የቀረውን ፍጥረት ግን ለአንክሮ ለተዘክሮ ለምግበ ሥጋ ለምግበ ነፍስ ፈጠረ። 

    “ወኲሉ ዘተፈጥረ ለመፍቅደ ነባብያን ቦ እምኔሆሙ ለምህሮ ወቦ እምኔሆሙ ለተገብሮ፤ ወእንዘ ኢየኀድግ ርእሶ ዘእንበለ ሰማዕት፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘንተ እምአፍአ ብከ ሰማዕት ወመምህር ዘይመርሐከ ኀበ ዝንቱ፤ ወዘኢያስተርኢ እግዚአብሔር እምፍጥረተ ዓለም ይትዐወቅ በፍጥረቱ” እንዲል።


💥 እግዚአብሔርስ የፈጠረው ፍጥረት እያንዳንዱ ቢቈጠር ፍጡር ተናግሮ ባልፈጸመውም ነበር፤ እየወገን እየወገኑ ግን ብዙውን አንድ ብዙውን አንድ እያሉ ቢቈጥሩ ከእሑድ እስከ ዐርብ የፈጠረው ሥነ ፍጥረት 22 ነው፡፡ እስከዚኽ አርዕስት ነው፤ ይኽንንም በሥነ ፍጥረት ይመለከቷል። 

የፀሓይ ጥንታት ሦስት የጨረቃን ዐምስት የሚል ነውና፤ ይኽ ዓለም የተፈጠረበት ዕለተ እሑድ ጥንተ ዕለት፤ አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፀዋት የተፈጠሩበት ዕለተ ሠሉስ ጥንተ ቀመር፤ ብርሃናት የተፈጠሩበት ዕለተ ረቡዕ ጥንተ ዮን ይባላል፤ “እሑድ ወሠሉስ ወረቡዕ ዘውእቶሙ ሠለስቱ ጥንታት” እንዲል


💥 ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ዘመን ቢቈጠር በፀሓይ 7513 ዘመን፤  በጨረቃ 7743 ዘመን ከ7 ወር ከ16 ዕለት ነው፡፡ 


💥 ከልደተ ክርስቶስ አስቀድሞ የነበረው በፀሓይ 5500 ዘመን፤ በጨረቃ 5668 ዘመን ከ10 ወር ከ9 ዕለት ነው፤ ይኽም  ዓመተ ኩነኔ፣ ዓመተ ፍዳ ይባላል፡፡


💥 ከልደተ ክርስቶስ ወዲኽ ያለው ግን በፀሓይ 2013 ዘመን፤ በጨረቃ 2074 ከ9 ወር ከ7 ዕለት ነው።  ይኽ ዓመተ ሥጋዌ፣ ዓመተ ምሕረት ይባላል፤ መላው ዓመተ ዓለም ነው፤ ዓመተ ዓለም ባለው ዓመተ ምሕረት የሚል ይገኛል፤ ጊዮርጊስ ወልደ አሚድም ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት ብሎ ተርጒሞታል፤ ስለምን ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት አለው ቢሉ? ሰው በዚኽ ዓለም ሳለ ኀጢአት ሠርቶ ንስሓ ቢገባ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረት የሚያገኝበት ስለኾነ ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት ብሎ ተርጒሞታል “በዕለት ኅሪት እሰምዐከ ወበዕለተ መድኀኒት እረድአከ ወናሁ ይእዜ ዕለት ኅሪት ወናሁ ዮም ዕለተ አድኅኖት” እንዲል፡፡


💥 ለዚኹም መሥፈሪያ ሰባት አዕዋዳት አሉት፤ ምንና ምን ቢሉ? ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ፀሓይ፣ ዐውደ ማኅተም፣ ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡ ከሊኹም ሦስቱ በዕለት አራቱ በዓመት ይቈጠራሉ፤ በዕለት የሚቈጠሩት ሦስቱ ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት ናቸው፤ በዓመት የሚቈጠሩ አራቱ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ፀሓይ፣ ዐውደ ማኅተም፣ ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡ ዐውደ ዕለት ከእሑድ እስከ ቀዳሚት ያሉ ሰባት ዕለታት ናቸው፤ እሊኽም አውራኅን ለማስገኘት በሰባት በሰባት ሲመላለሱ ይኖራሉ “እስመ ኊልቊ ሳብዕ ፍጹም ውእቱ በኀበ ዕብራውያን ” እንዲል። 


💥 ዐውደ ወርኅ በፀሐይ ዘወትር ፴ በጨረቃ አንድ ጊዜ 29፤ አንድ ጊዜ ፴ ይኾናል፤ እሊኽም ዓመታትን ለማግኘት በ፴ በ፴ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡


💥 ዐውደ ዓመት በፀሓይ 365 ዕለት በጨረቃ 354 ዕለት ነው፤ በፀሓይማ ምነው 365 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልኢት፤ በጨረቃ 354 ዕለት ከ22 ኬክሮስ ከ1 ካልዒት ከ37 ሣልሲት ከ52 ራብዒት ከ48 ኀምሲት አይደለውም ቢሉ “ወበውስተ ውሁድኒ ንብል አልቦ ወኢአሐዱ” እንዲል መጽሐፍ ትርፍን  ትቶ ጐደሎን  መልቶ መቊጠር ልማድ ነውና ፷ ካልመላ ብሎ እንዲኽ አለ እንጂ ቊጥሩስ አለ።  “እስመ ልማደ መጽሐፍ ይነግር ኊልቈ ምሉዓ ወፍጹመ ወየኀድግ ዘተርፈ ወይዌስክ ዲበ ሕፀፅ ካልዐ” እንዲል፤  ዕለታትን አዕዋድ አላቸው አውራኅን የሚያስገኙ ስለኾነ፤ አውራኅን አዕዋድ አላቸው ዓመታትን የሚያስገኙ ስለኾነ።  “ወበከመ ይትወለዳ አውራኅ እምዕለታት ወዓመታት እምአውራኅ ከማሁ ይትወለዳ አዕምሮታት እመከራት ወእምግባራት እንዲል፡፡


💥 ዐውደ አበቅቴ 19 ዓመት ነው።  በዚኽም  ፀሓይና ጨረቃ መንገዳቸውን ፈጽመው በተፈጠሩበት ኆኅት ይገናኙበታል፤ ሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ መምህራነ ወንጌል ሐዋርያት፣ ሊቀ ጳጳሳት ዲሜጥሮስ ከ፳ው አንድ ቀመር አንድ ተረፈ ቀመር፤ ከ፵ው ኹለት ቀመር ኹለት ተረፈ ቀመር፤ ከ፷ው 3 ቀመር 3ት ተረፈ ቀመር፤ ከ፹ው 4 ቀመር 4ት ተረፈ ቀመር፤ ከ፻ው 5ቀመር 5ት ተረፈ ቀመር እያላችኊ ቊጠሩ ማለታቸው ከዚኽ የተነሣ ነው።  “ወእምዘተርፈከ እምዐሠርቱ ወተሰዓቱ ተአትት እምኔሁ አሐደ ዓመተ እስመ ለዛቲኒ ዐሠርቱ ወተሰዓቱ ሙሴ ገብራ በጥበበ እግዚአብሔር ዘይገብሩ ባቲ ፍሥሐ አይሁድኒ ወክርስቲያንኒ” እንዲል። 


💥 ዐውደ ፀሓይ 28 ዓመት ነው፤ በዚኽ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፤ ዕለቱ ረቡዕ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ነው፤ ረቡዕ ማቴዎስ እንዲል፤ ዕለትን ፀሓይ አለው “ወበትእዛዝከ ይቀውም ዕለት” እንዲል፤ ወንጌላዊዉን ፀሓይ አለው “አንትሙ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም” ካለው አንዱ ርሱ ነውና፤ በሰንጠረዥ ፀ፣ ደ ይላል፤ ዐውደ ፀሓይ ማለት ነው፡፡


💥 ዐውደ ማኅተም 76 ዘመን ነው፤ በዚኽ አበቅቴ ወንጌላዊ ይገናኙበታል፤ አበቅቴው 18 ወንጌላዊዉ ዮሐንስ ነው፤ ማኅተም አለው አበቅቴው ለአበቅቴ ወንጌላዊዉ ለወንጌላዊው ፍጻሜ ነውና፡፡ ዐውደ ቀመር 532 ዘመን ነው፤ በዚኽ ዕለት፣ ወንጌላዊ፣ አበቅቴ እሊኽ 3ቱ ይገናኙበታል፤ ዕለቱ ሠሉስ፣ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ነው፤ ሠሉስ ማቴዎስ እንዲል አበቅቴው አልቦ ነው “ጥንቱ ለቀመር ዕለተ ሠሉስ ወንጌላዊ ማቴዎስ ወፍጻሜሁ ዕለተ ሰኑይ ወንጌላዊ ዮሐንስ” እንዲል።


💥 በዐውደ ፀሓይ ቦታ ዐውደ ማኅተም፤ በዐውደ ማኅተም ቦታ ዐውደ ፀሓይ የሚል ይገኛል፤ ከኹለቱ አንዱ ቢታጣ አንዱ ከቀመር ገብቶ ይቈጠራል፤ ቀመርን ለሦስቱ ስም በሰጡ ጊዜ ዐውደ ቀመር ዐቢይ ቀመር፤ ዐውደ ማኅተም ማዕከላዊ ቀመር፤ ዐውደ አበቅቴ ንዑስ ቀመር ይባላል፤ ዐቢይ ቀመር መደቡ 14 ቊጥሩ 532፣532፤ ማዕከላዊ ቀመር መደቡ 6 ቊጥሩ 76፣76፤ ንዑስ ቀመር መደቡ 3 ቊጥሩ 19፣19 ነው፡፡


💥 ከዚኽም ዓመተ አበቅቴን ለማግኘት 7513 ዘመን በዐቢይ ቀመር ቢቀምሩ 532፤ 532 የተፈጸመለት 14 ዐቢይ ቀመር፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኾኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡ 


💥 መላውንም በማእከላዊ ቀመርም ቢቀምሩ 76፤ 76 የተፈጸመለት 98 ማእከላዊ ቀመር 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኹኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡ 


💥 በዐውደ ፀሓይም ቢቀምሩ 28፤ 28 የተፈጸመለት 266 ዐውደ ፀሓይ፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኾኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡ 


💥 መላውንም በንዑስ ቀመር ቢቀምሩ 19፤ 19 የተፈጸመለት 395 ንዑስ ቀመር ኹኖ 8 ዓመት ይተርፋል፡፡


💥 7513ኙን ዘመን በቀመረ ዐረብም ቢቀምሩ 228፤ 228 የተፈጸመለት 32 ቀመረ ዐረብ፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 11 ንዑስ ቀመር ኹኖ 8 ዓመት ይተርፋል፤ ስመ አቅማር ብዙ ነው አይቶ መተው ነው፤ አሐደ አዕትት ለዘመን እንዲል ስለተጀመረ ተቈጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ ብሎ ከ8ቱ አንዱን ቢያትቱ 7 ይተርፋል፤ 7 ወንበር (ዓመተ አበቅቴ)ወጣ ይሏል በዘመነ ማቴዎስ።

💥 አበቅቴን ለማግኘት ከ7ቱ ዓመተ አበቅቴ 11 ቢሄዱ፤ 77 ይኾናል፤ 60ውን በ2 ፴ ቢገድፉት 17 ይተርፋል፤ 17 አበቅቴ ወጣ በዘመነ ማቴዎስ፡፡ 


💥 መጥቅዕንም ለማግኘት ከ7ቱ ዓመተ አበቅቴ 19 ዕለት ቢሄዱ 133 ይኾናል፤ 120ውን በ4 ፴ ቢገድፉት 13 ይቀራል፤ 13 መጥቅዕ ወጣ በዘመነ ማቴዎስ፡፡ 


💥 13 መጥቅዕና 17ት አበቅቴ ፴ ይኾናሉ እንጂ ከ፴ አይወጡም ከ፴ አይወርዱም፤ “ዓዲ መጥቅዕ ወአበቅቴ ክልኤሆሙ እመ ይበዝኁ ወእመ ይውኅዱ ኢየዐርጉ እም፴ ወኢይወርዱ እም፴ ወባሕቱ ወትረ ይከውኑ ፴” እንዲል። 

            

💥 ከዚኽም በዘመኑ የኾኑ አጽዋማትና በዓላትን ይናገሯል፤ መጥቅዕ 13 ነው።  መጥቅዕ ቢያንስ በጥቅምት ይውላልና፤ ጥቅምት እሑድ ይብታል፤ ከእሑድ እስከ እሑድ 8፤ ሰኞ 9፤ ማግሰኞ 10፤ ረቡዕ 11፤ ኀሙስ 12፤ ዐርብ 13፤ በዐለ መጥቅዕ ጥቅምት 13 ዐርብ ቀን ይውላል፤ የዐርብ ተውሳክ 2፤ 2 እና 13= 15 መባጃ ሐመር ይገኛል፤ በጥቅምት ሳኒታ የካቲት ሰኞ ይብታል፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 8፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 15፡፡ የካቲት 15 ሰኞ ነነዌ ይውላል፡፡


♦ የዐቢይ ጾም ተውሳክ 14፤ 14 ና 15 =29፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 8፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 15፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 22፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 29 የካቲት 29 ቀን ዐቢይ ጾም፡፡


♦ የደብረ ዘይት ተውሳክ 11፤ 11 ና 15= 26፤ መጋቢት ረቡዕ ይብታል፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 8፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 15፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 22፤ ኀሙስ 23፤ ዐርብ 24፤ ቅዳሜ 25፤ እሑድ 26፤ መጋቢት 26 ቀን ደብረ ዘይት፡፡


♦ የሆሳእና ተውሳክ 2፤ 2 እና 15=17፤ ሚያዝያ ዐርብ ይብታል፡፡ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 15፤ ቅዳሜ 16፤ እሑድ 17 ይብታል፡፡ ሚያዝያ 17 ሆሳዕና 


♦ የስቅለት ተውሳክ 7፤ 7 እና 15=22፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 15፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 22፡፡ ሚያዝያ 22 ስቅለት፡፡ 


♦ የትንሣኤ ተውሳክ 9፤ 9 እና 15= 24፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 15፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 22፤ ቅዳሜ 23፤ እሑድ 24፡፡ ሚያዝያ 24 ትንሣኤ 


♦ የርክብ ተውሳክ 3፤ 3 እና 15=18፤ ግንቦት እሑድ ይብታል፤ እሑድ እስከ እሑድ 8፤ እሑድ እስከ እሑድ 15፤ ሰኞ 16፤ ማግሰኞ 17፤ ረቡዕ 18፤ ግንቦት 18 ርክበ ካህናት፡፡


♦ የዕርገት ተውሳክ 18፤ 18 እና 15= 33፤ ፴ውን ገድፎ 3 ይቀራል፤ ሠኔ ማክሰኞ ይብታል፤ ማክሰኞ 1፤ ረቡዕ 2፤ ኀሙስ 3፤ ሠኔ 3 ዕርገት፡፡


♦ የጰራቅሊጦስ ተውሳክ 28፤ 28 እና 15= 43፤ ፴ውን ገድፎ 13 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ረቡዕ 9፤ ኀሙስ 10፤ ዐርብ 11፤ ቅዳሜ 12፤ እሑድ 13፤ ሠኔ 13 በዓለ ጰራቅሊጦስ፡፡


♦ የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ 29፤ 29 እና 15=44፤ ፴ውን ገድፎ 14 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ማግሰኞ እስከ ሰኞ 14፤ ሠኔ 14 ጾመ ሐዋርያት፡፡ 


♦ የጾመ  ድኅነት ተውሳክ 1፤ 1 ና 15= 16፤ ማክሰኞ እስከ ማክሰኞ 8፤ ማክሰኞ እስከ ማክሰኞ 15፤ ረቡዕ 16፤ ሠኔ 16 ጾመ ድኅነት ይውላል፡፡


💥 ዓመተ ወንጌላዊን ከዚኽ ይናገሯል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዓመተ ወንጌላዊ ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ ለእመ ተርፈ አሐዱ ማቴዎስ ወክልኤቱ ማርቆስ ወሠለስቱ ሉቃስ ወለእመ ዐረየ ክፍል ዮሐንስ እንዲል፤ ዓመተ ወንጌላዊን ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ አንድ ቢተርፍ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ መኾኑ፤ ኹለት ቢተርፍ ማርቆስ፤ ሦስት ቢተርፍ ሉቃስ ቢተካከል  መኾኑን በዚኽ ይታወቃል፤ 7513 ዘመን ለአራቱ ወንጌላውያን ቢያካፍሉ 1878 ደርሷቸው 1 ይተርፋል፤ 1 ቢተርፍ ማቴዎስ ያለው ይኽ ነው፤ ዛሬ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ መኾኑ በዚኽ ታውቋል፡፡


💥 ጥንተ ዮንንም ከዚኽ ይናገሯል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ጥንተ ዮን ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ ወትዌስክ ቦቱ መጠነ ራብዒት ወትገድፎ በበሱባኤ ወዘተርፈከ እምሱባኤ ተአትት እምኔሁ አሐደ ዓመተ ወእምዝ ይከውን ጥንተ ዮን እንዲል፤ ጥንተ ዮንንም ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ 5ኛ መጠነ ራብዒት 6ኛ ጳጉሜንን አክሎ በሱባዔ ገድፎ ከሱባዔ የተረፈውን አንዱን አትቶ 1 ቢተርፍ ጥንተ ዮን ረቡዕ መኾኑን መስከረም ረቡዕ መባቱን፤ 2ት ቢተርፍ ኀሙስ፤ 3 ቢተርፍ ዐርብ፤ 4 ቢተርፍ ቀዳሚት፤ 5 ቢተርፍ እሑድ፤ 6 ቢተርፍ ሰኞ፤ 7 ቢተርፍ ማግሰኞ መኾኑ በዚኽ ይታወቃል፡፡ አከፋፈል እንዳለፈው።


💥 7513 ዘመን ለአራቱ ወንጌላውያን ቢያካፍሉ 1878 ደርሷቸው 1 ይተርፋል፤ ይኽን በሱባዔ ይገድፏል፤ ከሺው 300 ነሥቶ 700 ግዱፍ፤ ከ800ው አንዱን መቶ ነሥቶ 700 ግዱፍ፤ 400 ይተርል፤ ከ100ው 2፤ ከ400ው 8፤ ከ8ቱ አንድ፤ ከዚያም 1 እና 78= 79 ይኾናል፤ ከ79ኙ 70ውን በ11 ሱባዔ ቢገድፉ 2 ይተርፋል፡፡


💥 ከአንዱ ወንጌላዊ 2 ከ4ቱ ወንጌላውያን 8፤ መጠነ ራብዒት፤ 6ኛ ጳጉሜን 1878 ዕለት ትኾናለች፤ ርሷ በዕለት፤ ወንጌላዊ በዓመት ይተካከላሉና ግድፈት እንዳለፈው፤ መጠነ ራብዒት  2= 10፤ ከዓመተ ወንጌላዊ የተረፈ 1 ና 10= 11 ይኾናል፤ ከ11ዱ 7ቱን በአንድ ሱባዔ ቢገድፉ 4 ይተርፋል፤ አሐደ አዕትት ለዘመን እንዲል ስለተዠመረ ተቈጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ ብሎ ከ4ቱ አንዱን ቢያትቱ 3 ይተርፋል፤ 3 ቢተርፍ ዐርብ ያለው ይኽ ነው፤ የዐርብ ጥንተ ዮን 3 ነውና፡፡ ጥንተ ዮንም ማለት ጥንተ ፀሓይ፤ ጥንተ ጨረቃ፤ ጥንተ ከዋክብት ማለት ነው፤ ጥንተ ዮን ብሂል ጥንተ ተፈጥሮቶሙ ለፀሓይ፤ ወወርኅ ወከዋክብት እንዲል፡፡


💥 ዕለተ ቀመርንም ለማወቅ ለጥንተ ዮን ከወጣው አንዱን ሳያትቱ በሱባዔ ገድፎ 1 ቢተርፍ ማግሰኞ መኾኑ፤ 2 ቢተርፍ ረቡዕ፤ 3 ቢተርፍ ኀሙስ፤ 4 ቢተርፍ ዐርብ፤ 5 ቢተርፍ ቀዳሚት፤ 6 ቢተርፍ እሑድ፤ 7 ቢተርፍ ሰኞ መኾኑ በዚኽ ይታወቃል፤ ለጥንተ ዮን የወጣው 4 ነው፤ 4 ቢተርፍ ዐርብ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ቀመርም ማለት ቀመር የተዠመረበት ዕለት ማለት ነው፤ ቀመር የተዠመረው ማግሰኞ ነውና፡፡


💥 ዕለተ ዮሐንስንም ከዚኽ ይናገሩታል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዕለተ ዮሐንስ ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ፤ ወትዌስክ ቦቱ መጠነ ራብዒት፤ ወክልዔተ ዕለተ ጠቢባን ወትገድፎ በበሱባዔ ወዘተርፈከ እምሱባዔ ኢተአትት አሐደ ዓመተ፤ ወእምዝ ይከውን ዕለተ ዮሐንስ እንዲል ዕለተ ዮሐንስን ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ፤ 5ኛ መጠነ ራብዒት፤ 6ኛ ጳጉሜንን አክሎ 7ኛ 2ት ዕለተ ጠቢባንን ጨምሮ በሱባዔ ገድፎ ከሱባዔ የተረፈውን አንዱን ሳያትቱ አንድ ቢተርፍ ዕለተ ዮሐንስ እሑድ መኾኑ፤ 2 ቢተርፍ ሰኞ፤ 3 ቢተርፍ ማግሰኞ፤ 4 ቢተርፍ ረቡዕ፤ 5 ቢተርፍ ኀሙስ፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ፤ 7 ቢተርፍ ቀዳሚት መኾኑ በዚኽ ይታወቃል።


💥 ለጥንተ ዮን የወጣ 4 እና 2 ዕለተ ጠቢባን= 6 ይተርፋል፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ዮሐንስም ማለት አሻቅቦ ወደ ላይ እስከ ፍጥረተ ዓለም፤ አቈልቊሎ ወደ ታች እስከ ምጽአተ ክርስቶስ ቢቈጥሩ ለወንጌላዊዉ ዮሐንስ የሚደርሰው ቀን ማለት ነው፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘኀለፈ ይመርሐከ ዝንቱ እስከ ፍጥረተ ዓለም ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘይመጽእ ያበጽሐከ ዝንቱ እስከ ምጽአተ ክርስቶስ እንዲል፤ አንድም ሠርቀ ቲቶን ዕለተ ዮሐንስ ይለዋል፤ ቲቶ የተባለው መስከረም ነው፤ የመጥምቁ ዮሐንስ በዓል የሚውልበት ቀን ማለት ነው፤ ርዕሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ እንዲል፡፡


💥 ዕለተ በዓል ዘኀለፈ ዕለተ በዓል ዘይመጽእ የእሑድ አሚሩ ሰንበተ ክርስቲያንን ለማወቅ በዘመኑ የወጣውን ጥንተ ዮን፤ ሠርቀ መዓልት፤ 2 ዕለተ ጠቢባን በየወሩ የሚገኘውን አጽፈ ወርኅ እሊኽን 4ቱን አንድ አድርጎ ቈጥሮ በሱባዔ ገድፎ 1 ቢተርፍ እሑድ አሚሩ፤ 2 ቢተርፍ ሰኞ ሰኑዩ፤ 3 ቢተርፍ ማግሰኞ ሠሉሱ፤ 4 ቢተርፍ ረቡዕ ረቡዑ፤ 5 ቢተርፍ ኀሙስ ኀሙሱ፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ሰዱሱ፤ 7 ቢተርፍ ቀዳሚት ሰቡዑ፤ 8 ቢተርፍ በሱባዔ ገድፎ እሑድ አሚሩ የሚያሰኘው ይኽ ነው፡፡ 


💥 አጽፈ ወርኅም ማለት የወርኁ ከወርኅ የሚደረብ ማለት ነው፤ ይኽስ ከምን ይገኛል ቢሉ? ወሩን በሱባዔ ቢገድፉ 4 ሱባዔ ኾኖ 2 ይተርፋል፤ የወርኁ 2 የዓመቱ 24፤ እንዲኽ ግን ስለኾነ ለመስከረም አጽፈ ወርኅ የለውም በጥንተ ዮን፤ በሠርቀ መዐልት በኹለት ዕለተ ጠቢባን ይቈጠራል፤ በእሊኽ በ3ቱ ይቈጠራል፤ ጥንተ ዮን 3፤ ሠርቀ መዐልት 1=4፤ ኹለት ዕለተ ጠቢባን 2፤ 6 ይኾናል፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ሰዱሱ ያለው ይኽ ነው። 


💥 ዕለተ ጠቢባንም ማለት ጠቢባን ሥላሴ ይኽነን ዓለም የፈጠሩበት፤ ጠቢባን መላእክት ሥላሴን የሚያመሰግኑበት ቀን ማለት ነው፤ (ዬ) ጠቢባን ሥላሴ ይኽነን ዓለም ከእሑድ እስከ ዐርብ ፈጥረዋል፤ ጠቢባን መላእክት ሥላሴን ዘወትር ያመሰግናሉ ብሎ የቊጥር መጽሐፍን የተማሩ መምህራን ዕለተ ሰንበትን፤ 6ቱ ዕለታትን፤ ያለፉትን የሚመጡትን በዓላት የሚያውቁባቸው የሚያሳውቁባቸው ማለት ነው፤ ዕለተ ጠቢባንም የተባሉ እሑድና ሰኞ ናቸው፤ ከቀመር ገብተው አልተቈጠሩም፡፡


💥 ዕለተ ምርያ አዕዋዲትንም ለማወቅ የፀሓይ ዐውደ ዓመት 365 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ነው፤ ይኽነን በሱባዔ ቢገድፉት 52 ሱባዔ ኾኖ 1 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ይተርፋል፤ ይኽቺውም አንድ ዕለት የተባለችው ዐምስተኛዪቱ ጳጒሜን ናት፤ ዕለተ ምርያ አዕዋዲት ይላታል፤ ዕለተ ምርያ ማለት ዕለተ መድኀኒት ማለት ነው፤ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበትን ቀን የምታሳውቅ ማለት ነው፤ ርሷ በዋለች ልደት ይውላልና፤ አዕዋዲትም አላት ዘመኑን የምታዘዋውር የምታለዋውጥ ማለት ነው፤ እሑድ የዋለውን ሰኞ፤ ሰኞ የዋለውን ማግሰኞ እንዲውል የምታደርግ ርሷ ናትና፡፡


💥 መጠነ ራብዒት 6ኛ ጳጉሜንም ለማወቅ የአንዱ ዓመት ኬክሮስ 15፤ የ2 ዓመቱ 30፤ የ4 ዓመቱ 60 ኬክሮስ ነው፤ 60ው ኬክሮስ 1 ዕለት ይኾናል፤ ይኽቺውም በሉቃስ መጨረሻ ዮሐንስን ተጠግታ የምትውል ስድስተኛዪቱ ጳጉሜን ናት፤ መጠነ ራብዒት፣ ሠግረ ዮሐንስ ይላታል፤ መጠነ ራብዒት አላት ርሷ በዕለት ወንጌላዊ በዓመት ይተካከላሉና፤ ሠግረ ዮሐንስም አላት ዮሐንስ ተራምዶ የሚውልባት ስለኾነ፡፡


💥 ዕሪና መዓልትና ዕሪና ሌሊትን ሰባተኛዪቱን ጳጉሜን ለማወቅ የአንዱ ዓመት ካልዒት 6፤ የ5ቱ ዓመት 30፤ የ10ሩ ዓመት 60 ይኾናል፤ 60ው ካልዒት 1 ኬክሮስ ይኾናል፤ የ100ው ዓመት 10 ኬክሮስ፤ የ600 ዓመት 60 ኬክሮስ፤ 60ው ኬክሮስ አንድ ዕለት ይኾናል፤ ይኽቺውም ሰባተኛዪቱ ጳጉሜን ናት፤ ዓለም በተፈጠረ በ600 ዘመን ዕሪና መዓልት ዕሪና ሌሊት ኾኗል፤ ዓለም ከተፈጠረ ዠምሮ እስከ ዛሬ ድረስ 12 ዕሪና መዓልት 12 ዕሪና ሌሊት ኾኖ 13ኛው ከተዠመረ 313 ኾኖ በዘመነ ማቴዎስ ይኸውም ሊመላ 287 ይቀራል፡፡

ከዚኽ በኋላ እንዲኽ ብሎ ባሕረ ሐሳብ አውጪው እንዲኽ ብሎ አሥርቆት ያውጣ፡፡


💥 በዘንዜከር ሐሳባተ ሕጉ ወትእዛዙ ለእግዚእነ ወአምላክነ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዘ ሀሎነ በዘመነ ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ዘመነ ማርቆስ ዜናዊ፤ ወንጌላዊ አለው ማቴዎስን ባለዘመን ነውና፤ ዜናዊ አለው ማርቆስን የሚመጣ ነውና ወረኛ ንጉሥ እንዲሉ፡፡ በሰብዐ ወኀምስቱ ምእት ዐሡሩ ወሠሉሱ ዓመተ ዓለም፡፡ በኀምሳ ወኀምስቱ ምዕት ዓመተ ዓለም፤ በዕሥራ ምዕት ዐሡሩ ወሠሉሱ ዓመተ ምሕረት፤ ሠረቀ ለነ ወርኀ መስከረም ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ወርኀ ጥቅምት በሰላመ እግዚአብሔር አሜን፤ አበቅቴ 17 ሠርቀ መዓልት 1፤ ሕጸጽ 1= 19፤ ዐሡሩ ወተሱዑ ሠርቀ ሌሊት፤ ዕሥራ ወሡሉሱ ሠርቀ ወርኅ፤ አሚሩ ሠርቀ መዓልት፤ ሰዱሱ ሠርቀ ዕለት፤ ዮም በዛቲ ዕለት ዘአቅረብነ ለከ አምኀ ስብሐት ያዐርጉ ለነ መላእክት ተወከፍ ለነ እግዚአ ስብሐት። 

             ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!


Saturday, September 5, 2020

❖የ2013 ዓ.ም አጽዋማትና በዓላት ቀመር፦


የ2013 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የዘመን አቆጣጠር (ባሕረ- ሐሳብ )


“በቸርነትህ ዓመታትን ታቀዳጃለህ” [መዝ.64(65)፥11]

▰▰▰▰▰▰▰▰▰
ዓመተ ዓለም = ዓመተ ምህረት + ዓመተ ኩነኔ (ፍዳ) = 2013 + 5500 =7513
ወንጌላዊ፦ በዓመቱ የሚሾም ወንጌላዊ ማለት ነው፡፡
ዓመተ ዓለም፥4
7513 ÷ 4 = 1878
1878 ፦ መጠነ ራብዒት ይባላል፡፡
7513 - 4×1878 = 1
ቀሪው ' 1 ' ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ማቴዎስ
ቀሪው ' 2 ' ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ማርቆስ
ቀሪው ' 3 ' ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ሉቃስ
ቀሪው ' 0 ' ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ዮሐንስ ይሆናል።
ስለዚህ ቀሪው '1' ስለሆነ የዘንድሮው ወንጌላዊ ማቴዎስ ሲሆን ዘመኑ ዘመነ ማቴዎስ ይባላል።
•••
ዕለተ ቀመር፦ መስከረም አንድ የሚውልበት ቀን ነው፡፡
ዕለተ ቀመር= ዓመተ ዓለም+መጠነ ራብዒት÷7
= 7513 + 1878 =9391
= 9391 ÷ 7 = 1341 ቀሪ 4
ቀሪው '0 'ከሆነ ሰኞ
ቀሪው '1' ከሆነ ማክሰኞ
ቀሪው '2 'ከሆነ ረቡዕ
ቀሪው '3 'ከሆነ ሐሙስ
ቀሪው '4 'ከሆነ ዓርብ
ቀሪው '5 'ከሆነ ቅዳሜ
ቀሪው '6 'ከሆነ እሁድ መባቻ ይሆናል። በመሆኑም ዘንድሮ ቀሪው '4'ስለሆነ ዕለተ ቀመር ዓርብ ይሆናል።
•••
መደብ = ዓመተ ዓለምን በ19 በመግደፍ እናገኛለን። = 7513፥19=395 ደርሶ 8 ይቀራል። ስለዚህ መደብ 8 ይሆናል፡፡
•••
• ወንበር = ከመደብ አንድን ለዘመን በመተው ወንበርን እናገኛለን።
ወንበር =8 - 1= 7 ይሆናል።

• አበቅቴ ፦ጥንተ አበቅቴን በወንበር አባዝተን በ30 ገድፈን እናገኛለን።
አበቅቴ =11*7=77
77፥30= '2' ደርሶ ቀሪው '17' ሲሆን ዘንድሮ አበቅቴ '17'ይሆናል።

• መጥቅዕ፦ ጥንተ መጥቅዕን በወንበር አባዝተን ለ30 በመግደፍ(በማካፈል) እናገኛለን።
መጥቅዕ = 19×7 = 133
133 ÷ 30= 4 ቀሪው '13 'ስለሆነ መጥቅዕ ዘንድሮ '13 'ይሆናል።

“አበቅቴ ወመጥቅ ክሌሆሙ ኢይበዝሁ እም30 ወኢይኅዱ እም 30 ወትረ ይከዉኑ 30 ፤ አበቅቴ ቢበዛ መጥቅ ቢያንስ መጥቅ ቢበዛ አበቅቴ ቢያንስ ከ30 አይበዙም አያንሱም” ይህም ማለት በሌላ አገላለጽ መጥቅዕና አብቅቴ ተደምረዉ ዉጤቱ ከ30 መብለጥና ማነስ የለበትም፤ ሁሌ 30 ይሆናል፡፡ የዘንድሮዉ የ2013 ዓ.ም = 17+ 13 = 30

መጥቅዕ ከ14 በላይ ከሆነ በመስከረም ይዉላል፤
መጥቅዕ ከ14 በታች ከሆነ በጥቅምት ይዉላል፤

መጥቅዕ በመስከረም ቢዉል ጾመ ነነዌ በጥር፣ መጥቅዕ በጥቅምት ቢዉል ጾመ ነነዌ በየካቲት ይብታል።
ስለዚህ በዚህ ዓመት መጥቅዕ 13 ሲሆን ከ14 ያንሳል፤ ስለዚህም መጥቅዕ በጥቅምት ይዉላል፤
•••
ስለዚህ የ2013 መጥቅዕ ጥቅምት 13 ነው ሲሆን ዕለተ መጥቅዕ አርብ ይሆናል፡፡
•••
መባጃ ሐመር፦ መጥቅዕንና የባለመጥቅዕን ተውሳክ በመደመር በ30 በመግደፍ እናገኛለን፡፡ ከዕለተ መጥቅዕ ጀምረን እስከ ነነዌ ጾም መግቢያ ስንቆጥር 128 ቀን ይሆናል፡፡ በ30 ብንገድፈዉ 4 ቀሪ 8 ይሆናል፡፡ ይህም የቅዳሜ ተውሳክ ነው። ልብ ይበሉ የዕለት ተውሳክ ከቅዳሜ ይጀምራል፡፡
• ቅዳሜ፡ 128፥30=4 ቀሪ 8
• እሁድ፡127፥30=4 ቀሪ 7
• ሰኞ፡126፥30=4 ቀሪ 6
• ማክሰኞ፡125፥30=4 ቀሪ 5
• ረቡዕ፡124 ፥30=4 ቀሪ 4
• ሐሙስ፡123፥ 30= 4 ቀሪ 3
• ዐርብ፡122፥ 30= 4 ቀሪ 2

መባጃ ሐመር=13+2=15
መባጃ ሐመር ከ30 ስለሚያንስ ራሱ 15 ይያዝና መጥቅዕ በጥቅምት ስለዋለ ጾመ ነነዌ በየካቲት 15 በዕለተ ሰኞ ይውላል ማለት ነው።

• ጾመ ነነዌ፦ መጥቅዕና የዕለቱን ተውሳክ
በመደመር በ30 ገድፈን እናገኛለን፡፡ይህ ጾም ሕጸፅ የለውም፡፡ ሌሎችን አጽዋማት ተውሳኩን ከነነዌ ደምረን ከ30 ከበለጠ ለ30 እያካፈልን እናገኛለን።
•••
፩፥ ከነነዌ ጾም እስከ ዐቢይ ጾም 14 ቀናት አሉ። ስለዚህ የዐቢይ ጾም ተውሳክ 14 ይሆናል፡፡
፪፥ ከነነዌ እስከ ደብረዘይት 41 ቀኖች አሉ፡፡
41 ÷ 30 = 1 ደርሶ ቀሪው 11 የደብረዘይት ተውሳክ ይሆናል፡፡
፫፥ ከነነዌ እስከ ሆሣዕና 62 ቀኖች አሉ፡፡
62 ÷ 30 = 2 ደርሶ ቀሪው 2 የሆሣዕና ተውሳክ ይሆናል፡፡
፬፥ ከነነዌ እስከ እስከ ስቅለት 67 ቀኖች አሉ፡፡
67 ÷ 30 = 2 ደርሶ ቀሪው 7 የስቅለት ተውሳክ ይሆናል፡፡
፭፥ ከነነዌ እስከ ትንሣኤ 69 ቀኖች አሉ፡፡
69 ÷ 30 = 2 ደርሶ ቀሪው 9 የትንሣኤ ተውሳክ ይሆናል፡፡
፮፥ ከነነዌ እስከ ርክበ ካህናት 93 ቀኖች አሉ፡፡
93 ÷ 30=3ደርሶ ቀሪው 3 የርክበ ካህናት ተውሳክ ይሆናል፡፡
፯፥ ከነነዌ እስከ ዕርገት 108 ቀኖች አሉ፡፡
108 ÷ 30 = 3 ደርሶ ቀሪው 18 የዕርገት ተውሳክ ይሆናል፡፡
፰፥ ከነነዌ እስከ ጰራቅሊጦስ 118 ቀኖች አሉ፡፡ 118 ÷ 30 = 3 ደርሶ ቀርው 28 የጰራቅሊጦስ ተውሳክ ይሆናል፡፡
፱፥ ከነነዌ እስከ ጾመ ሐዋርያት 119 ቀኖች አሉ፡፡ 119 ÷ 30 =3 ደርሶ ቀሪው 29 የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ነው፡፡
፲፥ ከነነዌ እስከ ጾመ ድኅነት 121 ቀኖች አሉ፡፡ 121 ÷ 30 = 4 ደርሶ ቀሪው 1 ሲሆን የጾመ ድኅነት ተውሳክ 1 ይሆናል፡፡
•••

ከዚህ ተነስተን አጽዋማትንና በዓላትን ተውሳኮቻቸውን ከነነዌ ጋር እየደመርን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ የ2013 የነነዌ ጾም መገቢያ የካቲት 15 ይሆናል፡፡
13+2=15 ስለሆነ ነው፡፡
★ ዓብይ ጾም ተውሳኩ 14 ነው
= 14 +15= 29 ሲሆን ስለዚህ ዘንድሮ በዘመነ ማቴዎስ ዓብይ ጾም በየካቲት 29 ይገባል ማለት ነው፡፡
* ደብረ ዘይት፡ ተውሳኩ 11 ነው፡፡
11+15 =26 ይሆናል፡፡ 26 ከ 30 ስለሚያንስና በየካቲት ስላለፍን ቀጣዩን በመጋቢት እናገኛለን። ስለዚህ በመጋቢት 26 እሁድ ደብረዘይት ይሆናል።
★ ሆሣዕና ተውሳኩ 2 ነው፡፡
= 2+15 =17 ሲሆን ከ30 ስለሚያንስና በመጋቢት ስላለፍን ቀጣዩን ሚያዚያን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ ሚያዚያ 17 እሁድ ይሆናል፡፡
★ ስቅለት ተውሳኩ 7 ነው፡፡
7+15= 22 ሲሆን ዘንድሮ በሚያዝያ 22 ዓርብ ስቅለት ይሆናል፡፡
★ ትንሣኤ ተውሳኩ 9 ነው፡፡
9 +15 = 24 ሲሆን ሚያዝያ 24 በዓለ ትንሣኤ ይውላል።
★ ርክበ ካህናት ተውሳኩ 3 ነው፡፡
3 +15 = 18 ሲሆን 18ን በሚያዝያ ስላለፍን በግንቦት 18 ረቡዕ ርክበ ካህናት ይሆናል።
★ ዕርገት ተውሳኩ 18 ነው፡፡
18 +15 = 33 ሲሆን ዘንድሮ ሰኔ 3 ሐሙስ በዓለ ዕርገት ይሆናል።
★ ጰራቅሊጦስ ተውሳኩ 28 ነው፡፡
28 +15= 43 ዚህ ሰኔ 13 እሁድ በዓለ
ጰራቅሊጦስ ይውላል።
★ ጾመ ሐዋርያት ተውሳኩ 29 ነው፡፡
29 +15=44
44 ን በ30 ገድፍን ቀሪው 14 ሲሆን ሰኔ 14 ሰኞ የሐዋርያት ጾም ይገባል።
ፆመ ድህነት ተውሳኩ 1 ነው፡፡
= 1 + 15 =16 በመሆኑም ጾመ ድህነት(የረቡዕና ዓርብ ጾም) ሰኔ 16 ይገባል።

▰▰▰▰▰▰▰▰▰
የአጽዋማትና የበዓላት ኢይወርድ ኢይዓርግ(ገደብ)
➛ጾመ ነነዌ ከጥር 17 በታች አይወርድም ፤ ከየካቲት 21 በላይ አይወጣም።
➛ ዐቢይ ጾም ከየካቲት 1 በታች አይወርድም ፤ ከመጋቢት 5 በላይ አይወጣም።
➛ ደብረዘይት ከየካቲት 28 በታች አይወርድም ፤ ከሚያዝያ 2 በላይ አይወጣም።
➛ ሆሣዕና ከመጋቢት 19 በታች አይወርድም ፤ ከሚያዝያ 23 በላይ አይወጣም።
➛ ስቅለት ከመጋቢት 24 በታች አይወርድም ፤ ከሚያዝያ 28 በላይ አይወጣም።
➛ ትንሣኤ ከመጋቢት 26 በታች አይወርድም ፤ ከሚያዝያ 30 በላይ አይወጣም።
➛ ርክበ ካህናት ከሚያዝያ 20 በታች አይወርድም ፤ ከግንቦት 24 በላይ አይወጣም።
➛ ዕርገት ከግንቦት 5 በታች አይወርድም ፤ ከሰኔ 9 በላይ አይወጣም።

▰▰▰▰▰▰▰▰▰
# ልብ_በሉ
• ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ሐዋርያት ከሰኞ አይወጡም።
• በዓለ ደብረዘይት፣ ሆሣዕና፣ ትንሣኤና ጰራቅሊጦስ ከእሁድ አይወጡም፡፡
• ዕርገት ከሐሙስ
• ስቅለት ከዓርብ አይወጣም።
• ርክበ ካህናትም ከረቡዕ አይወጣም።

Friday, August 21, 2020

❖የክርስቶስ ራስነት:-

የክርስቶስ ራስነት:-

ራስ የሚለው ቃል በመፅሐፍ ቅዱስ ውሰጥ ያለው ትርጉም የነገሮች ዋና:የበላይ የሆነ:ከሁሉም ከፍ ያለ:ሁሉን ገዢ የሁሉ መሪ ማለት ነው።ታድያ ክርስቶስ ኢየሱስ የብዙ ነገር ዋናና የበላይ ነው።ይህን ስፍራ እንዲይዝ አሰቀድሞ መከራን መቀበል ቀጥሎም ወደ ክብሩ መግባት ነበረበት።

የብሉይ ኪዳን ነቢያት ይህን እውነት በአፅንዖት ተናግረዋል።ሉቃ 24:26 1ኛ ጴጥ 1:11 ይህን እውነት ሐዋርያት መሰክረዋል።ዕብ 2:18 12:2 13:12-13። እግዚአብሔር አንድያ ልጁ ኢየሱስን ያለ ልክ ከፍ ከፍ አድርጎታል።ፊሊ 2:9 በግርማዊ ዙፋን ቀኝም ጌታም ክርስቶስም አድርጎ የነገሮች ሁሉ ራስ አድርጎታል።የሐዋ 2:36 ይህ እንደ መደርደሪያ ካልን ኢየሱስ ራስ የሆነባቸው ጉዳዬች በጥቂቱ እንመልከት፦

1ኛ,ክርስቶስ ኢየሱስ የቤተክርትያን ራስ ነው።

ኤፌ 1:21-22"ሁሉንም ከእግሩ በታች አስገዛለት ከሁሉ በላይም ራስ እንዲሆን ለቤተክርስትያን ሰጠው።ክርስቶስ ሲሰቀል ሰይጣንና ዓለም ያላቸውን ኃይልና ብርታት አሳይተዋል።ያለ የሌለ ኃይል በመጠቀም ክርስቶስ ወደ መስቀለ ሞት ገፍተውታል።ይህን እንዲሆን የአይሁድ ሃይማኖትና የሮም የመንግስት ሰርዓት ተጠቅማል።ክርስቶስ የሚቃጠል መሥዋዕት ሆኖ ስለ ፅድቅና የኃጢአት መሥዋዕት ሆኖ ስለ ኃጢአት ሞተ።እግዚአብሔር ክርስቶስን ከሞት በማስነሳት የኃይሉ ብርታት አሳዬ።ከጌትነት ከአለቅነት ከኃይላትና በዓለም ከሚጠራ ስም ሁሉ በላይ እግዚአብሔር አደረገው።ለአካሉ ማለትም ለቤተክርትያንም ራስ እንደሆን ሰጠው።ቤተክርስትያን አንድ ራስ ነው ያላት እርሱም ክርስቶስ ብቻ ነው።የቤተክርስትያን head office ክርስቶስ ነው።

2ኛ,ከዚህ የቤተክርስትያን ጉዳይ ጋር ክርስቶስ የማዕዘን ድንጋይ ራስ ነው።

ኤፌ 2:20"በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኅል።የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው።አማኞች ሕያዋን ድንጋይ ናቸው።1ኛ ጴጥ 2:5 እነዚህ አማኞች በክርስቶስ የማዕዘን ድንጋይ ራስነት ይገጣጠማሉ።ክርስቶስ በአማኞች ላይ የበላይ ዋና የሆነ ብቻ ሳይሆን አማኞች ሚገጣጠሙበት ነው።በእርሱ ተገጣጥመው ቅዱስ መቅደስ ይሆናሉ።

3ኛ,ክርስቶስ የህይወት ራስ።

የሐዋ 3:14-15"እናንተ ግን,,,የሕይወት ራስ ገደላችሁት እርሱን ግን እግዚአብሔር ከሙታን አስነሣው።ሰው በበደል በኃጢአት ሙት ነው።ኤፌ 2:1ነገር ግን ሰው ህይወትን ለማግኘት ወደ ክርስቶስ መምጣት አለበት።ዮሐ 17:2 ስለዚህ በስሙ ለሚያምኑ ኢየሱስ ህይወትን ይሰጣቸዋል።ምክንያቱም የህይወት ራስ ነው።ዮሐ 3:36 1ኛ ዮሐ 5:12

4ኛ,ክርስቶስ የመዳን ራስ ነው።

ዕብ 2:10"ብዙ ልጆች ወደ ክብር ያመጣ ዘንድ የመዳናቸውንም ራስ በመከራው ይፈፅም ዘንድ ለእርሱ ተገብቶታልና።ሰው መዳን የሚችል ከፍጡር ዘንድ አንድም የለም።መዳን በማንም በሌላ የለም።የሐዋ 4:12 በእርሱ(በክርስቶስ) የሚመጡትን ፈፅሞ ያድናቸዋል።ዕብ 7:23 ክርስቶስ ኃጢአተኞችን ሊያድን መጣ።1ኛ ጢም 1:15 ስለዚህ መዳንን በተመለከተ ክርስቶስ ብቻ ይመለከተዋል።ክርስቶስ የመዳናችን ዋና ነው።

5ኛ,ክርስቶስ የእምነታችን ራስ ነው።

ዕብ 12:3"የእምነታችን ራስና ፈፃሚውን ኢየሱስን ተመልከቱ።አንድ እምነት አለ።እርሱም ለቅዱሳን የተሰጠ ነው።ይሁዳ 1:3 የዚህ እምነት የበላይ ኢየሱስ ነው።ብዙ ሃይማኖቶች ራስ አላቸው። መፅሐፍ ግን ኢየሱስ የእምነታችን ራስ ነው ይለናል።አዎን ኢየሱስ ብቻ የሃይማኖት ራስ ነው።

❖በክርስቶስ ኢየሱስ ሥር መስደድ:-

በክርስቶስ ኢየሱስ ሥር መስደድ!
(ወደ ቆላስይስ ሰዎች ምዕ. 2)
----------
6፤ እንግዲህ ጌታን ክርስቶስ ኢየሱስን እንደ ተቀበላችሁት በእርሱ ተመላለሱ።
7፤ ሥር ሰዳችሁ በእርሱ ታነጹ፥ እንደ ተማራችሁም በሃይማኖት ጽኑ፥ ምስጋናም ይብዛላችሁ።
በእነዚህ ሁለት ቁጥሮች ውስጥ ብቻ በፍልስፍና እና የሰው ስርዓት በሆነ ሃይማኖት እየተናወጡ ለነበሩት ለቆላስይስ ክርስቲያኖች ድንቅ ምክር ተለግሷቸዋል። በክርስቶስ መመላለስ፣ በክርስቶስ ሥር መስደድ እና በክርስቶስ መታነፅ ወይም መገንባት ሶስቱ ቁልፍ ነገሮች ናቸው።
ለሁለቱ ነገሮች መሰረት ወደሆነው ቃል እንምጣ። ተክል፣ ሁሉ ነገሩ ያለው ሥሩ ላይ ነው። ሥሩ ለተክሉ ዋና ነገር ከሆነ ደግሞ በተመቻቸ ቦታ ሊተከል ይገባዋል። ጥሩ አፈር እና ውሃ ያለበት ቦታ ላይ ትንሽ የነበረው ሥር በሚገርም ሁኔታ አድጐ ይሰፋል። ተክሉም ያድጋል። ገና ሲተከል አካባቢ ህፃናት እንኳ በቀላሉ ሊጎዱት ይችላሉ። ከጊዜያት በኃላ ግን ጐልማሳም እንኳ አይደፍረውም።
እንዲህ ነው። እኛን በተመለከተ የተተከልንበት ቦታ ፍፁም፣ አስፈላጊው ሁሉ የሚገኝበት ውብ ስፍራ ነው። በዚያ የሕይወት ውሃ ምንጭ ሳያቋርጥ ይፈልቃል። ከእኛ የሚጠበቀው ዝም ብሎ የሚልቀውን ምንጭ እየጠጡ ሥርን ማስፋት ብቻ ነው።
ክርስቶስ የሕይወት ውሃ ምንጭ ነው። በእርሱ ዘንድ ሁሉም አለ። እርሱ ሁሉም ነው።
" ክርስቶስ ሁሉ ነው"
(ወደ ቆላስይስ ሰዎች 3:11)
ነፍስ ከትላንት ዛሬ፣ ከዛሬ ነገ ከክርስቶስ እየተመገበች፣ ከክርስቶስ ጋር በቃሉ በኩል ጊዜ እየሰጠች ስታሳልፍ፣ በክርስቶስ ውስጥ ስር ትሰድዳለች። ዕለት ዕለት ከቃሉ ጋር በፅሎት ስትጣበቅ ሥሯ ይሰፋል።
> የዚህም ውጤት ያች ነፍስ በሕይወቷ የምትመራው በክርስቶስ ሆኖ በእርሱ ትመላለሳለች፣ ደግሞ በዛው በክርስቶስ እየተገነባች በፍሬ ትታጀባለች።
" በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል።"
(የዮሐንስ ወንጌል 15:5)
ያኔ ሙቀት ቢመጣ ድርቅ ማለትም የሰው ፍልስፍና ሆነ የሰው ሐይማኖት ሊያናውጧት እና ሊያሰጓት አይችሉም።
(ትንቢተ ኤርምያስ ምዕ. 17)
----------
7፤ በእግዚአብሔር የታመነ እምነቱም እግዚአብሔር የሆነ ሰው ቡሩክ ነው።
8፤ በውኃ አጠገብ እንደ ተተከለ፥ በወንዝም ዳር ሥሩን እንደሚዘረጋ ሙቀትም ሲመጣ እንደማይፈራ ቅጠሉም እንደሚለመልም፥ በድርቅ ዓመትም እንደማይሠጋ ፍሬውንም እንደማያቋርጥ ዛፍ ይሆናል።

Sunday, June 28, 2020

❖ቤተክርስቲያን፦

ቤተክርስቲያን ማለት ምን ማለት ነው?
በግሪክኛ ቋንቋ ቤተክርስቲያን"አቅሌስያ"ተብላ ተጠርታለች።ትርጉሙም"የተጠሩ "ማለት ነው።ይህንን ትርጉም በተለያዩ የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት በተለይም በቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት እናገኘዋለን፦
 " በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት፥ የእነርሱና የእኛ ጌታ የሆነውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም በየስፍራው ከሚጠሩት ሁሉ ጋር ቅዱሳን ለመሆን ለተጠሩት፤"
    (1ኛ ወደ ቆሮ1:2)።
ኢየሱስ ክርስቶስ መጀመሪያ አስራ ሁለት ቅዱሳን ሐዋርያትን ጠራ።ከእነዚህ ጋር የተጠሩ 36 ቅዱሳት አንስትን ጨምሮ 72 አርድእት ነበሩ።ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዚህ ቤተክርስቲያንን መሠረተ።

ቤተ ክርስቲያን በምድር ያለች የእግዚአብሔር ተቋም ናት። የተመሠረተችውም ለአንድ ዓላማ ነው።የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ለመሆን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የምድር አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደሰማይ ከማረጉ በፊት ደቀመዛሙርቱን እንዲህ ብሎአል፦
 "ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ አለ።" (የሐዋ ሥራ 1:8)። 

ይህ ዓላማ ቤተክርስቲያን ለምን እዚህ ምድር ላይ እንደምትኖር በሚገባ ያሳያል። የቤተክርስቲያን ሠሪዋም መሠረቷም እንዲሁም ማእዘንዋም ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"አንተ ዓለት ነህ ዓለት የተባለ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነው ብሎ የመሰከረው መስክርነት ነው።  በአንተ ዓለትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም።" (የማቴ 16:18)" 
ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልምና፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"
  (1ኛ  ቆሮ 3:11)
"በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ፤፤(ኤፌ2:20)።

ቤተክርስቲያን እስከ አሁን ድረስ በነቢያትና ሐዋርያት ትሠራለች፤ ሠራተኞችም ነቢያትና ሐዋርያት ናቸው። ነገር ግን እያንዳንዱ እንዴት እንደሚሠራ መጠንቀቅ ይኖርበታል።

" የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ ተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ።"(1ኛ  ቆሮ 3:10)።

ቤተክርስቲያንን ለማነጽ የሁሉም የቤተክርስቲያን አካል ደርሻ ነው። ነገር ግን በፊተ አውራሪነት የሚመግቡ መሪዎች አሉ።" እግዚአብሔርም በቤተ ክርስቲያን አንዳንዶቹን አስቀድሞ ሐዋርያትን፥ ሁለተኛም ነቢያትን፥ ሦስተኛም አስተማሪዎችን፥ ቀጥሎም ተአምራት ማድረግን፥ ቀጥሎም የመፈወስን ስጦታ፥ እርዳታንም፥ አገዛዝንም፥ የልዩ ልዩ ዓይነት ልሳኖችንም አድርጎአል።"(1ኛ ቆሮ 12:28)።
እነዚህ ሁሉ ቤተክርስቲያንን ለማነጽ ሥራ ሥራቸውን መሥራት አለበቸው።" አጵሎስ እንግዲህ ምንድር ነው? ጳውሎስስ ምንድር ነው? በእነርሱ እጅ ያመናችሁ አገልጋዮች ናቸው፤ ለእያንዳንዳቸውም ጌታ እንደ ሰጣቸው ያገለግላሉ።" (1ኛቆሮ3:5) 

ቤተክርስቲያንና ዓላማዋ፦

1.ሁሉንም እየስተማሩ የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀመዛሙርት ማዳረግ፦


እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ። (ማቴ 28፥19-20 ) ይህ ካልሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተክርስቲያንና ከአገለጋዮቹ ጋር አይኖርም

2. ለእግዚአብሔር ቃልና ለክርስቲያናዊ ስነምግባር ግዴለሽ አለመሆን፦

በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን አውቃለሁ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር። እንዲሁ ለብ ስላልህ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው። (ራዕ 3፥16 ) ይህ ደንታ ቢስነት ቤተክርስቲያንን አለማዊ ያደርጋታል .ከእግዚአብሔር መንግሥትም ያወጣታል ቤተክርስቲያን በምድር ያለሽ የእግዚአብሔር መንግሥት ናትና

3. በምድር የምታበራ መቅረዝ ናት፦

በመቅረዞቹም መካከል የሰው ልጅ የሚመስለውን አየሁ፥ እርሱም እስከ እግሩ ድረስ ልብስ የለበሰው ደረቱንም በወርቅ መታጠቂያ የታጠቀ ነበር። (ራዕ 1፥13) መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ። የቤተክርስቲያን መኖር በጨለማው ዓለም እንድታበራ ነው የተቃጠለ አንቦል ለምንም አይጠቅም ። ቤተክርስቲያን የክርስቶስን ብርሃን ያለማቋረጥ ማብራት ይኖርባታል

4. የዲብሎስን ሥራ ማፍርስ፦

 ይህም ዘርኘነት፤ ጥላቻ፤ ርኩሰት በአጠቃላይ ከእግዚአብሔር ቅዱስ ባህርይ የማይሠማሙትን ሁሉ ማስወገድ ዓላማዋና ተልኮዋ ነው።
ስለዚህ የዲያብሎስን ሥራ እንዲያፈርስ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ። ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ኃጢአትን አያደርግም፥ ዘሩ በእርሱ ይኖራልና፤ ከእግዚአብሔርም ተወልዶአልና ኃጢአትን ሊያደርግ አይችልም። (1ኛ ዮሐ 3፥9)

5. ፍቅርን መግለጽ፦

ወዳጆች ሆይ፥ ፍቅር ከእግዚአብሔር ስለ ሆነ፥ የሚወደውም ሁሉ ከእግዚአብሔር ስለ ተወለደ እግዚአብሔርንም ስለሚያውቅ፥ እርስ በርሳችን እንዋደድ። ፍቅር የሌለው እግዚአብሔርን አያውቅም፥ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና። በዚህ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፥ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና። ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም። ወዳጆች ሆይ፥ እግዚአብሔር እንዲህ አድርጎ ከወደደን እኛ ደግሞ እርስ በርሳችን ልንዋደድ ይገባናል። እግዚአብሔርን ማንም ከቶ አላየውም፤ እርስ በርሳችን ብንዋደድ እግዚአብሔር በእኛ ይኖራል ፍቅሩም በእኛ ፍጹም ሆኖአል። (1ኛ ዮሐ 4 ፡7-12)
 ፍቅር የሌላት ቤትክርስቲያንና ፍቅር የሌለው ክርስቲያን እግዚአብሔር በውስጡ የለም ያለፍቅር ክርስትና የለም።

Tuesday, June 23, 2020

❖ የማይገባ ደግነት:-

ይቅርታ በደልን ለመርሳት የሚደረግ ሙከራ፣ ወይም
ሰውዬውን መርሳት አይደለም፡፡ ይቅርታ ለበደለኛው
የማይገባውን መስጠት ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የታረቅንበት ምሥጢሩ ይህ የማይገባን ደግነት ነው፡፡
ለሰማያዊው አባት ያለንን ፍቅር ልንገልጥ የምንችለው እርሱ የፈጠራቸውን ሰዎች በመውደድ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያሳየንን
ፍቅር እኛም ለጎረቤታችን ማሳየት ይገባል፡፡ እግዚአብሔር
የጠፋውን ዓለም በእኛ ውስጥ ሆኖ ሊወደው ይፈልጋል፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ አስደናቂ ይቅርታ ስላሳዩ ሰዎች
እናነባለን፡፡ ከእነርሱም ሦስቱን በዚህ ክፍል ለማየት
መርጠናቸዋል፡፡ እነርሱም አዳም፣ ዮሴፍና የእስጢፋኖስ
ቤተሰቦች ናቸው፡፡
አዳም በሚወዳትና በሚያዳምጣት ሚስቱ አማካይነት
በኃጢአት ወደቀ፡፡ ጸጋው ተገፈፈ፣ ነጻነት የሌለው ሰው ሆነ፣
ፍርሃትና ሽሽት ከማያመልጠው ማንነት ጋር ገጠመው፡፡
ምክንያትም ሳያስጥለው የዘላለም ሞት ተፈረደበት፡፡ በሥጋ ሞት
ላይ የነፍስ ሞት፣ ወደ መቃብር በመውረድ ላይ ወደ ሲኦል
መውረድ ተፈረደበት፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ እግዚአብሔር ተለየው፡፡
አዳም የሚስቱን ዓይን ላለማየት ቢወስን፣ ቢሸሻትና እርሷን
ይቅር ለማለት ቢፈተን ማንም አይፈርድበትም፡፡ እርሱ ግን ፍጹም
ይቅር ባይ ነበርና ያን የማይገባ ደግነት አሳያት፡፡ ሞትን
ላመጣችበት ሴት «አዳምም ለሚስቱ ሔዋን ብሎ ስም አወጣ፣
የሕያዋን ሁሉ እናት ናትና» (ዘፍ3፡20)፡፡
ሔዋን አሁን ሕያው አይደለችም፡፡ ሙታንም ከእርሷ
ይወጣሉ፡፡ ነገር ግን አዳም የአሁኑን ሳይሆን የተስፋዋን ፍጻሜ
አየ፡፡ የሆነችውን ሳይሆን ልትሆን ያላትን አሰበ፡፡ ስለዚህ የሕያዋን
እናት አላት፡፡ ለወደቁት ሰዎች የመነሣት ጉልበታቸው ዛሬም
በእነርሱ ላይ ያለን እምነት ነው፡፡ ምን እንደሚሆኑ ያለን ተስፋ
አንድ ቀን ራእያቸው ይሆናል፡፡ «የወደቁ ሰዎች የተዘረጉ እጆችን
ይፈልጋሉ፡፡»
ጋብቻ እንደ አዳምና እንደ ሔዋን ነው፡፡ ውድቀት ያልፈታው
ትዳር የእነዚህ ወገኖች ትዳር ነው፡፡ ዛሬ ብዙዎች ትዳራቸውን
ይቅር ማለት አልቻሉም፡፡ ስለ ንብረታቸውና ስለ ልጆቻቸው እያዘኑ
ይኖራሉ፡፡ ዘይቱ እንዳለቀበት መቅረዝ ፍቅር አልቆባቸው
ጨልመዋል፡፡ ተዋደው የገቡ ሳይሆን በፍርድ ቤት ትእዛዝ
የተጣመሩ እስኪመስል መሸካከም አልቻሉም፡፡ ብዙ ጊዜም
አንዳቸው በመንፈስ ጭንቀት ሲያዙ የጠባይ ለውጥ እየመሰለ
ይበልጥ ይከፋፋሉ፡፡ የትዳር ጓደኛ መነጫነጭ፣አለመርካት፣
የትዳር ውሳኔውን መርገም፣ ልጆቹንና የትዳር ጓደኛውን ማየት
ሲጠላ . . . የጠባይ ለውጥ ብቻ ላይሆን ይችላልና መመርመሩ
መልካም ነው፡፡ በትዳር ውስጥ ትልቁ ጉዳትም ስህተትን
የሚፈልግ ዓይን በመሆኑ ከዚህ መትረፍ ያስፈልጋል፡፡ በየዕለቱ
ከምንሞላው ኃይል አንዱ ፍቅር ነውና ስንጎድልና ማፍቀር
ሲያቅተን በጸጋው ዙፋን ፊት ወድቀን ሙላኝ ልንል ይገባል፡፡

ሌላው የተደነቀ የይቅርታ ሕይወት የሚታየው በዮሴፍ
ላይ ነው፡፡ ዮሴፍ ከወንድሞቹ ይልቅ አባቱ ይወደው ነበር፡፡ ምንም
ባይበድላቸው መወደድም የመጠላት ምክንያት ይሆናልና
ወንድሞቹ ጠሉት (ዘፍ. 37፡4)፡፡ ዮሴፍ ሕልሙን በነገራቸው ጊዜ
ደግሞ ወደፊት ይሆናል የሚሉትን ነገር ሲያስቡ በቅንዓት አበዱ፡፡
በበረሃ እየተቅበዘበዘ ሲፈልጋቸው እነርሱ ግን ሊገድሉት
ተማክረው በጉድጓድ ጣሉት፡፡ የግብጽ ነጋዴዎች ሲያልፉ
አይተውም በሃያ ብር ሸጡት፡፡ በጉስቁልና ከሕልሙ ያራቁት
መስሏቸው ይበልጥ ወደ ሕልሙ ትርጓሜ ገፉት፡፡ «መገፋት ጥሩ
ነው እምብዛም ሳይወድቁ፣ የተገፉት ቆመው የገፉት ወደቁ፤»
ዮሴፍም ገና በልጅነቱ ብርቱ መከራ ደረሰበት፣ በባዕድ
አገር በአገልጋይነትና በእስር ተንገላታ፡፡ በኃጢአት አልተባበርም
ማለት በዓለም ያስቀጣልና አሥራ ሦስት ዓመት ተቀጣ፡፡ ነገር
ግን ይህ ጠባብ መንገድ ወደ ሰፊው ጎዳና የሚያወጣ ነበር፡፡
ዮሴፍ ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ራእይ የጠላትነት ብዛት
ሊያሸንፈው አልቻለም፡፡ እንደውም ጠላቶቹ ወደ ራእዩ እንዲደርስ
ያቻኩሉት ነበር ፡፡ አንድ ሰው «እግዚአብሔር ታላቅ በረከት
እንዳዘጋጀልኝ ቀድሞ የሚነግረኝ ሰይጣን ነው፡፡ ይተነኳኮለኛል»
ብሏል፡፡
ዮሴፍ የግብፅ አገር ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነ፡፡
እግዚአብሔር ያለው አይቀርምና ወንድሞቹ ሰገዱለት፡፡ በከነዓን
ምድር ረሃብ እያሯሯጠ ወደ ግብጽ አመጣቸው፡፡ ዮሴፍ
አወቃቸው እነርሱ ግን አላወቁትም፡፡ ራሱን በገለጠላቸው ጊዜ
በጭንቀት ተናጡ፡፡ በልባቸው ሌላውን ከመበደል ራስ መበደል
ይሻላል ሳይሉ አልቀሩም፡፡ የዮሴፍን ፊቱን ማየት አልቻሉም፡፡
እርሱ ግን አልበደላቸውምና ፊታቸውን አየ፡፡ መልካምነት
ሥልጣን ካልሆነን በቀር የማንንም ፊቱን ማየት አይቻለንም፡፡
ዮሴፍ አሁን ሊበቀላቸው ይችላል፡፡ እነርሱም ፈርተው
ነበር፡፡ ዮሴፍ ግን እግዚአብሔር ክፉውን ለውጦ ለመልካም
እንዳደረገው ስለተረዳ ይቅር አላቸው፡፡ ምንም ክፉ
ቢያደርጉበትም ወደ ተስፋው እንዳቀረቡት ተረዳ፡፡ እግዚአብሔር
አንዳንዴ እምነታችን እንዲያድግ በክፉ ሰዎች መካከል
ያስቀምጠናል፡፡ እንድንጠነክር ታዝዘው መከራ ያደርሱብናል፡፡
ታዲያ ከንጉሡ ታዝዞ ሎሌው አርባ ቢገርፈን እንቀየመዋለን?
ከሰዎች ጋር መታገል ከንቱ ነው፡፡
ዮሴፍ መበቀል እየቻለ አልተበቀላቸውም፡፡ በቀል
የእግዚአብሔር፣ ይቅርታ የእርሱ መሆኑን ተረዳ
(ዘፍ.50፣19-20)፡፡ ሕጋዊ መንግሥት ባለበት አገር የበደለንን
ሰው ራሳችን ብንቀጣ መንግሥትን እንደካድን ይቆጠራል፡፡
እንዲሁም በጽድቅ የሚፈርድ አምላክ እያለ እኛ ተበቃይ ብንሆን
እግዚአብሐርን ክደነዋል ማለት ነው (ሮሜ.12፣19-21)፡፡ አዎ
የእግዚአብሔር ሰዎች በእግዚአብሔር ቦታ ሆነው የነገሮችን
አካሄድ መለወጥ እንደማይችሉ ሲረዱ እግዚአብሔርም ለእነርሱ
ነገሮችን ወደ በጎ የሚለውጥ መሆኑን ያምናሉ፡፡ ዮሴፍ ቢበቀል
ኖሮ ከእግዚአብሔር ጋር በተጣላና ያን ክብር ባላገኘ ነበር፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ እግዚአብሔር የአገር መሪዎችና ባለሥልጣናት
የይቅርታ ሰዎች እንዲሆኑለት ይፈልጋል፡፡ የበለጠ ኃላፊነትን
ለመሸከም እግዚአብሔር ይቅር ባዮችን ያጫል፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የምናየው ሦስተኛው የይቅርታ
ሕይወት የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች ያደረጉት ነው፡፡ ወጣቱ ሰማዕት
እስጢፋኖስ የሞተው በአሁኑ ጳውሎስና በግብረ አበሮቹ
በድንጋይ ተወግሮ ነው፡፡ እስጢፋኖስ ግን «ጌታ ሆይ፡ ይህን
ኃጢአት አትቊጠርባቸው» እያለ ጸለየላቸው፡፡ ይህንን ጸሎት
የጸለየው «የእግዚአብሔርን ክብር ኢየሱስንም» ካየ በኋላ ነው
(የሐዋ.ሥራ.7፣55-60)፡፡ ክርስቶስን ስናይ ብቻ ልባችን
ለይቅርታ ይለዝባል፡፡ ከወጋሪዎቹ አንዱ ጳውሎስ የድሮው ሳውል
ክርስቲያን ሆነ፡፡ ጳውሎስ የእስጢፋኖስ የይቅርታ ጸሎት ልቡን
ነክቶታል፣ ወይም ልብን የሚነካ ጸጋ አምጥቶለታል፡፡
ይህ ጳውሎስ ያውም ለትምክሕት «የእስጢፋኖስንም
ቤተ ሰዎች ደግሞ አጥምቄአለሁ ጨምሬ ሌላ አጥምቄ
እንደሆነ አላውቅም» (1ቆሮ.1፣16) ማለቱ ያስገርመናል፡፡ እኛ
ይቅር ብንል እንኳ ቤተሰብ በቶሎ ይቅር አይልም፡፡ ቤተሰብ
ስለልጅ መቀየም ጽድቅ ነው የሚመስለው፡፡ የእስጢፋኖስ
ቤተሰቦች ግን በልጃቸው ገዳይ በጳውሎስ እጅ መጠመቃቸው
የይቅርታን ጽኑነት ያሳየናል፡፡
እኛ ገንዘብ የካዱንን ይቅር ማለት ሲያቅተን አዳም
ገነትንና እግዚአብሔርን ያሳጣችውን ሔዋንን ይቅር አላት፡፡ ዮሴፍ
ልጅነቱን ለመከራ እቶን የዳረጉት ወንድሞቹን በበቀል ሳይሆን
በይቅርታ አሸነፋቸው፡፡ የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች ደም መላሽ
ቢሆኑ ኖሮ ጳውሎስን በመልእክቱ ዛሬ አናገኘውም ነበር፡፡ ይቅርታ
ለትውልድ የምናቆየው ውለታ ነው፡፡ በእርግጥም ይቅርታ
የማይገባንን በሰጠን በእግዚአብሔር ፊት ሰውዬው
የማይገባውን መስጠት ነው፡፡
                  *ይቅርታ*
       የይቅርታ ልብ ይስጠን!!!

Friday, June 19, 2020

❖የጌታ መልአክና ወንጌል፦

የጌታ መልአክና ወንጌል፦
የእግዚአብሔር መልአክ ሕይወት የሆነው ጌታ ለዓለም እንዲበሰር ተናገረ። 

የጌታ መልአክ ግን በሌሊት የወኅኒውን ደጅ ከፍቶ አወጣቸውና፦
ሂዱና ቆማችሁ የዚህን ሕይወት ቃል ሁሉ ለሕዝብ በመቅደስ ንገሩ አላቸው። (የሐዋ 5፡19፡20)
ምክንያቱም ሰው ሕይወት እንዲኖረው ይፈልጋል። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም። (ዮሐ 5፡24)

በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።
እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።

ቆርኔሌዎስን ከቅዱስ ጴጥሮስ ወንጌልን እንዲሰማ አዘዘው፦

ጻድቅ ሰው እግዚአብሔርንም የሚፈራ በአይሁድም ሕዝብ ሁሉ የተመሰከረለት የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስ ወደ ቤቱ ያስመጣህ ዘንድ ከአንተም ቃልን ይሰማ ዘንድ ከቅዱስ መልአክ ተረዳ አሉት።ርሱም መልአክ በቤቱ ቆሞ እንዳየና፦ ወደ ኢዮጴ ሰዎች ልከህ ጴጥሮስ የተባለውን ስምዖንን አስመጣ፤እርሱ ቤቱ በባሕር አጠገብ ባለው በቍርበት ፋቂው በስምዖን ዘንድ እንግድነት ተቀምጦአል፤ ልታደርገው የሚገባህን እርሱ ይነግርሃል።

ይህ መልአክ ጴጥሮስ ስለዘዓለአለም ሕይወት እንደሚነገር ያውቃል።

በዘመን መጨረሻ የእግዚአብሔር መልአክ ወንጌልን ለዓለም ያውጃል፦

በምድርም ለሚኖሩ ለሕዝብም ለነገድም ለቋንቋም ለወገንም ሁሉ ይሰብክ ዘንድ የዘላለም ወንጌል ያለው ሌላ መልአክ ከሰማይ መካከል ሲበር አየሁ።  (ራእይ14፥6 )

በጨረሻም ቢሆን እንኳ ሰው ሁሉ ሕይወትን እንዲያገኝ የእግዚአብሔር መልአክ ያውጃል የሰው ልጅ ለሚያገኝው የዘለአለም ሕይወት ያለቸውን ከፍታኛ ፍለጎት ያረጋግጣል እኛ ግን ለኛ የሆነውን ሕይወት ቦታ አልሰጠነውም ።

   

                የእግዚአብሄር ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን!!

Sunday, June 7, 2020

❖መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውኃ ወንዝ ነው፦

☞መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ውኃ ወንዝ ነው፦

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲስተምር፦
"በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ ይላል "ቅዱስ ወንጌል 

  (ዮሐ 7፥38)

❖  ይህን የተናገረው ለማን እንደሆነ ሲገልጽ፦

"ይህን ግን በእርሱ የሚያምኑ ሊቀበሉት ስላላቸው ስለ መንፈስ ተናገረ፤ ኢየሱስ ገና ስላልከበረ [ስላልተሰቀለ ማለት ነው] መንፈስ ገና አልወረደም ነበርና" ብሏል። 

ወንዝ ሳያቋርጥ የሚፈስ ነው የመንፈስ ቅዱስ ፀጋና በረከትም ለሚቀበሉት ሁሉ ያለማቋረጥ ሲሰጥ ይኖራል። 


❖  ቅዱስ ጴጥሮስ በሃምስኛው ቀን ለደቀመዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ መውረዱን ሲያስረዳ፦


እግዚአብሔር ይላል፦ 

"በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፥ ጎበዞቻችሁም ራእይ ያያሉ፥ ሽማግሌዎቻችሁም ሕልም ያልማሉ፤ደግሞም በዚያች ወራት በወንዶችና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ ትንቢትም ይናገራሉ"።

     (የሐዋ 2፥17-18)

   ወንዝ የፈሰሰበት ሁሉ ይለመልማል ያፈራል። መንፈስ ቅዱስም ያደረበት ሁሉ በእግዚአብሔር ፀጋ ይለመልማል የእግዚአብሔር የሆነውን ያፈራል ። 

  ሕዝቅኤል የመንፈስ ቅዱስን ፀጋና በረከት ከመቅደሱ የሚፈስ የሕይወት ውኀ መሆኑን ገልጿል።

ከመቅደሱ የሚወጣ ዉሃ ወደ ምስራቅ ሲፈስ ይመለከታል፡፡ 

ሰውየው (የሚያሳየው መልአክ ማለት ነው) ገመዱን በእጁ ይዞ 1000 ክንድ ለካ፡፡ 

  በዉሃው ውስጥ አሻገረኘ ዉሃው እስከ ቁርጭምጭሚት ደረሰ።

   ሁለተኛ ሲሻገረው እስከ ጉልበት።

   ሶስተኛ እስከ ወገብ ።

  አራተኛ እጀግ ጥልቅና ሰፊ ወንዝ በመሆኑ ማንም ሊሻገረው የማይችል ወንዝ ሆነ፡፡ 


❖  ወንዙ የእግዚአብሔርን በረከትና ፀጋ ዘልዓለማዊ ሕይወትን ይገልጻል፡፡ 


  እስከ ቁርጭምጭሚት በዘመነ አበው የነበረውን የእግዚአብሔር በረከትና ፀጋ፣ 

  እስከ ጉልበት በዘመነ መሳፍንት የነበረውን የእግዚአብሔር በረከትና ፀጋ፣ 

  እስከ ወገብ በዘመነ ነቢያት የነበረውን የእግዚአብሔር በረከትና ፀጋ ደህንነት፣ 

  ማንም ሊሻገረው የማይችለው ዉሃ በጌታችን በኢየሱስ ክረስቶስ የተሰጠውን በረከትና ፀጋ ዘልዓለማዊ ሕይወት የሚገልጽ ነው፡፡


ማንም ሊሻገረው የማይችል ታላቅ ወንዝ እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራልና፤ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና የሚለውን ያረጋግጣል። 

  መሲህ የሕይወት ዉሃ መሆኑን ተናግሯል፡፡ 

  መንፈስ ቅዱስም የሕይወት ውሃ መሆኑን ተናግሯል። 

  በርሱ የሚያምን የሕይወት ዉሃ ከርሱ እንደሚመነጭ አስተምሯል፡፡ 

   በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።


❖  ዉሃው ወደ ምስራቅ ባሕር በገባ ጊዜ የምስራቁ ባሕር ሙት ባሕር ነው፡፡ ዉሃው ይፈወሳል። 

  ዉሃው የሚወክለው የረከሰውን ሕዝብ ሰለሆነ በመሲህ ያመነ ሁሉ ፈውስንና የዘልዓለም ሕይወትን ማግኘቱን ያረጋግጣል፡፡ 

   ዉሃው ሕያው ነፍስ ያለው ተንቀሳቃሽ ሁሉ በሕይወት የሚኖርበት መሆኑን ይናገራል፡፡ 

  ወንዙ በሚመጣበት ያለው ሁሉ በሕይወት ይኖራል፡፡ 

ዉሃው የሚፈሰው እጅግ በበረሃማነት ወደሚታወቀው ወደ ይሁዳ ምድረበዳና ወደ ጨው ባሕር ነው፡፡ መራራው የጨው ባሕር የብዙ ዓሳዎችና ተንቃሳቃሽ ሕያዋን ፍጥረታት መኖርያ ይሆናል፡፡ ይህም የሆነው ጨዋማው ዉሃ በመቅደሱ ውሃ ስለተፈወሰ ነው፡፡ 

ረግረግና እቋሪው ግን ጨው እንደሆነ ይኖራል፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ያላመኑትን ይመለከታል፡፡ በወንዙ በዚህና በዚያ ፍሬው የሚበላ ዛፍ ቅጠሉ የማይረግፍ ፍሬው ለሁልጊዜ የሚያፈራ አለ፡፡ ፍሬው ለመብል ቅጠሉ ለመድኀኒት የሕይወት ዛፍ ነው የሚወክለውም ዘልዓለማዊ ሕይወትን ነው፡፡

                                               (ሕዝቅኤል 47፥1-12)


                እግዚአብሄር ይክበር ይመስገን!!!

❖መንፈስ ቅዱስ፦

መንፈስ ቅዱስ ማን ነው?

፩. መንፈስ ቅዱስ ማን ነው?

  ☞ ከሦስቱ የሥላሴ አካላት አንዱ አካል ነው፡፡

  ☞ የማይጨበጥ፤የማይታይ አካል ያለው መንፈስ ነው፡፡

  ☞ የሰረፀው (የወጣው) ከአብ ነው።

  ☞ ከአብ እና ከወልድ ጋር እኩል ምስጋናና አምልኮ የሚገባው ነው። 

  ☞ እግዚአብሔር (አምላክ) ነው፡፡

  ☞ የአብ እና የወልድ እስትንፋስ (ሕይወት)ነው፡፡

  ☞ በነቢያትና በሐዋርያት አድሮ የተናገረ፥ሕይወትንም ያቀና : ምድርን ለክብሩ ያስጌጠ ነው፡፡

፪. የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌዎች ምን ምን ናቸው? 

   ርግብ፣ እሳት፣ ውኃ፣ ዘይትና ነፋስ ናቸው። 

☞  ርግብ የዋህ ናት፦ መንፈስ ቅዱስም የዋህና ቂም የማያውቅ ነው፡፡ ርግብ በኖህ ዘመን የጥፋት ውኃ መድረቁን  ያወጀች  የሰላም ምልክት ናት፤ መንፈስ ቅዱስም ክርስቶስ ሲጠመቅ የኃጢአት ባሕር መድረቁን በርግብ ምሳሌ ወርዶ የሰበከ የሰላም ጌታ ነው።

☞  እሳት ያበስላል፦  መንፈስ ቅዱስም ሕፃን የሆነውን አእምሮ በጥበብ ያጎለምሳል፡፡ እሳት የከበረ ማዕድንን ከአፈር ይለያል፥ መንፈስ ቅዱስም አምኖ የከበረውን ፡ ካላመነው ይለያል፡፡

☞  ውኃ ያነፃል፥ መንፈስ ቅዱስ ይቀድሳል፡፡

☞  ነፋስ፣ ነፍስና መንፈስ የሚወጡበት የግሪክ ቃል ኒዩማ የሚል ሲሆን ከነፋስ- ነፍስ፤ ከነፍስ- መንፈስ ይረቃል። ነፋስ በእንቅስቃሴው እንደሚታወቅ መንፈስ ቅዱስም በሥራው ይታወቃል፡፡

❖  በብሉይ ኪዳን የመብራት ዘይት ነበረ፥ በየዕለቱ በመቅረዙ ይጨመራል፡፡ ይህ የመብራቱ አለመጥፋት የመንፈስ ቅዱስን መኖር ያመለክታል፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ ለቅርፅ አልባዋ መሬት ውበት ያፈሰሰ፥ ውኆችን ለፍጥረት ጥቅም የቀደሰ ጌታ ነው፡፡ "ምድርም ባዶ ነበረች፥ አንዳችም አልነበረባትም፤ ጨለማም በጥልቁ ላይ ነበረ፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በውኃ ላይ ሰፍፎ ነበር።" ኦሪት ዘፍጥረት 1:2።

❖  መንፈስ ቅዱስ መሳፍንትን በምስፍና፥ ነገሥታትን በንግሥና፥ ካህናትን በክህነት ጸጋ፥ ነቢያትን በሀብተ ትንቢት፥ ዘማርያንን በዝማሬ ጸጋ፥ ፈዋሾችን በሀብተ ፈውስ ......የሾመ...ጸጋ የሰጠና ጸጋን ያደላደለ ቅዱስ መንፈስ ነው፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ ቅድስት ኤልሳቤጥ ለድንግል ማርያም የሆነላትን እንድትረዳ አደረባት፡፡ ድንግል ማርያም በድንግልና እንድትወልድ ሁሉን አስቻላት፡፡ በክርስቶስ አገልግሎት ነበረ፡፡ 

  ክርስቶስ ከማረጉ በፊት ስለ መንፈስ ቅዱስ መምጣት ተናግሯል፡፡

☞   "አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።" የዮሐንስ ወንጌል 14:26

☞  "እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ። እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤ ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ነው፤ ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው። የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ፥ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም። ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል።" ዮሐንስ 16:7-15::

☞   " ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤" የዮሐንስ 15:26።

☞  " ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል፤እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ።" ዮሐንስ 14:15-16::

❖  በመጽሐፍ ቅዱስ አንዱ መንፈስ ቅዱስ በአደራረጉ ምክንያት:- 

    ☞  የእውቀት መንፈስ፣ 

    ☞  የጥበብ መንፈስ፣ 

    ☞  የኃይል መንፈስ፣ 

    ☞  የእውነት መንፈስ፣ 

    ☞  የመገለጥ መንፈስ፣ ...ተብሎ ተጠርቷል፡፡ 

በክርስቶስ አገለግሎት የነበረው ሱታፌ እንዳለ ሆኖ በክርስቶስ ትምህርት እንዴት እንደተገለጠ ከላይ ባሉት ጥቅሶች አይተናል፡፡ በክርስቶስ ትምህርት አጽናኝ(ጰራቅሊጦስ)፣ የእውነት መንፈስ እና ሁሉን የሚነግር መምህር ተብሏል፡፡ የሚመጣው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው፡፡ የሚመጣበት አላማ ስለ ክርስቶስ ለመመስከር ነው፡፡ ስለዚህ በክርስቶስ የማያምኑትን ይወቅሳል፤ የዲያብሎስን መጣል ይናገራል፤ ጽድቅ ወደ አብ በሄደው በክርስቶስ እንደሆነ ይመሰክራል፤ የቤተክርስቲያንን እንቅስቃሴ ይመራል፤ ምእመናንን ያጽናናል፤ ለበጉ ሠርግ ያዘጋጃል፤ አገልጋዮችን ያሰማራል፡፡ 

❖  ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባረገ በአስረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስ ወደ ዓለም መጣ፤ በጽርሐ ጽዮን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የተወለደችውን የክብርት ቤተክርስቲያን ልደት በእሳት ላንቃ በዓለም ቋንቋ አከበረ፡፡ ሐዋርያትን ለእውነት አስጨከነ፤ ምስጢር እና ብዙ ቋንቋዎች ገለጠላቸው፡፡ በጉዞቸው ሁሉ አብሮ ነበረ፡፡ ዛሬም የቤተክርስቲያን አገለግሎት ሕይወት መንፈስ ቅዱስ ነውና ክብር ለመንፈስ ቅዱስ!!

❖  ላመነ ሰው ጥምቀት የሚፈጸመው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነው፡፡ ይህም የክርስቶስ ትእዛዝ ነው፡፡ ማቴ 28:19:: በጥቅሉ ያለ መንፈስ ቅዱስ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን አይፈጽሙም፡፡ የምስጢራቱ አፈጻጸም ሥርዓት የሚመራው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ 

በመግቢያዬ እንደጻፍኩት ቤተክርስቲያን ስለ መንፈስ ቅዱስ ጠንካራ አቋም አላት፦ "ማህየዊ በሚሆን በአንድ ጌታ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን፤ እርሱም ከአብ የሰረፀ ነው፡፡ በነቢያት እና በሐዋርያት ተናግሯል፡፡ ከአብ ከወልድ ጋር ምስጋና ይገባዋል።" ጸሎተ ሃይማኖት አንቀጽ ፰.

መንፈስ ቅዱስ፦

☞  ሕይወት ሰጭ፤ ጥበብ ገላጭ መንፈስ ነው፡፡

☞  የጸጋ ምንጭ እና አደላዳይ ነው፡፡

☞  ለበጎ ሥራ ቀስቃሽ፤ከኃጢአት እንድንወጣ ወቃሽ ነው

☞  ልብን አይቶ የሚሾም፤ ትሁታንን የሚያከብር ቅዱስ መንፈስ ነው፡፡

❖  መንፈስ ቅዱስ የሕይወት ኃይል ነው፡፡ ብርታት የሆነን እርሱ ነው፡፡ ስንደክም ያግዘናል፡፡ እንዴት መጸለይ እንዳለብን ያስተምረናል(ሮሜ 8:26-27)፥ እንዴት ማምለክ እንዳለብን ይመራናል፥ ከዚያ ጸሎታችንን ይሰማል፤ አምልኮችንን ይቀበላል፡፡

❖  የመንፈስ ቅዱስ ነገር ለፍጥረታዊው ሰው ሞኝነት ነው፡፡ "ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፤ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ሆነ ሊያውቀው አይችልም።" 1ቆሮንቶስ 2:14። የመንፈስ ቅዱስ ጉዳይ በእምነት መንፈስ እንጂ በሥጋ አይመረመርም፡፡ የጰራቅሊጦስ የተቀበልነው ይህን የእውነት መንፈስ ነው፡፡ "እኛ ግን ከእግዚአብሔር እንዲያው የተሰጠንን እናውቅ ዘንድ ከእግዚአብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንም።" 1ቆሮንቶስ 2:12።

❖  መንፈስ ቅዱስ በፍጥረታዊ ሰው አይኖርም፡፡ እንዲያውም የክርስቶስ መንፈስ የሌለው የክርስቶስ ወገን አይደለም፡፡ "የክርስቶስ መንፈስ የሌለው ከሆነ ግን ይኸው የእርሱ ወገን አይደለም።" ሮሜ 8:9።

❖  ምክር፣ ጥበብ፣ ምስጢር፣ ትንቢት፣ ፈውስ፣ ዝማሬ፣ ሹመት፣ ኃይል .... ከመንፈስ ቅዱስ ይሰጣሉ፡፡ ደስታ፣ ፍቅር፣ እምነት፣ የዋሃት፣ ራስን መግዛት፣ ትዕግስት፤ በጎነት፣ ቸርነትና ሰላም የመንፈስ ፍሬ ናቸው፡፡ ገላ 5:23:: 

❖  መንፈስ ቅዱስ ከምንተነፍሰው አየር በላይ ያስፈልገናል፡፡ በሥራችን ዐመፃ የመንፈስ ቅዱስን አሠራር ልንቃወም እንችላለን፡፡ "መንፈስን አታጥፉ፤" 1ተሰሎንቄ 5:19። ንጉሥ ዳዊት በበደለ ጊዜ ይህ አጋዥ፣ አስተማሪ፣ መሪ እና አጽናኝ መንፈስ እንዳይወስድበት ለመነ፡፡ "ከፊትህ አትጣለኝ፥ ቅዱስ መንፈስህንም ከእኔ ላይ አትውሰድብኝ።" መዝሙረ ዳዊት 51:11።

❖  መንፈስ ቅዱስ ከተለየን ሕይወት፣ ሰላም፣ ዕረፍት፣ መንፈሳዊነት ... የንስሐ ጸጸት...ይለዩናል፡፡ ስለዚህ "ለቤዛም ቀን የታተማችሁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ። መራርነትና ንዴት ቁጣም ጩኸትም መሳደብም ሁሉ ከክፋት ሁሉ ጋር ከእናንተ ዘንድ ይወገድ። እርስ በርሳችሁም ቸሮችና ርኅሩኆች ሁኑ፥ እግዚአብሔርም ደግሞ በክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ ይቅር ተባባሉ።" ኤፌ 4:30-32:: የሥጋ ሥራ ከመንፈስ አላማ ያወጣል፡፡ የሥጋ አሠራር መንፈስ ቅዱስን ይቃወማል፡፡ ደስታ የሰጠን ሀዘን ሊቀበል አይችልም፡፡ ባናከብረው ደስታ የምናጣው እኛ ነን፡፡ " ለአሠራሩ እንመች፡፡ በኖህ ዘመን ርግቧ በመጀመሪያው ጉዞዋ ማረፊያ አጥታ እንደተንከራተተች መንፈስ ቅዱስም ለአሠራሩ የሚመች ሰው አጥቶ በዙሪያችን አለ።" ለአሠራሩ እንመች፡፡ እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ አደረሰን፡፡ ስለመንፈስ ቅዱስ አንብቡ ፥ ዘምሩ፡፡ 

 ለመንፈስ ቅዱስ ክብርና ምስጋና ይገባል!!!