Friday, April 26, 2019

❖እንደ ተሰቀለ...!

መስቀል ላይ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ይታዬን!

" የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?"
ገላትያ ሰዎች 3:1

እንኳን አደረሰን!! ዛሬ ነፃነታችን በደም የተገዛበት ዕለት ነው።
ዛሬ የፍቅር ጥግ የታየበት ጌታችን ነፍሱን ለወዳጆቹ አሳልፎ የሰጠበት ነው።
ዛሬ ለእኛ የሚገባውን መከራ ሁሉ ተቀብሎ ልጆች የተደረግንበት ነው።የሰማይና የምድር ንጉስ ልጅ ሆነን አንነስ እባካችሁ በልባችን ይታተም እንኑርበት ፣
ዛሬ ተርቦ እኛን ያጠገበበት ፣ተጠምቶ እኛን ያረካበት ፣ቆስሎ እኛን የፈወሰበት፣የማይገባውን ሞት ተቀብሎ የማይገባንን ሕይወት ለእኛ የሰጠበት ቀን ነው፡፡ይህ ሁሉ ለእኛ ነው።

ከዘመናት በፊት ጌታችን ኢየሱስ በዛሬው ዕለት ትውልድ ፊቱን አዞረበት( ዛሬም ከተፈጠርንለት አላማ ውጪ መኖር እርሱ ላይ ፊትን ማዞር እንደሆነ ይሰመርበት)።በአይሁድ ተገርፎ፥ በወዳጅ ተከድቶ ታመመ፡፡በገዥዎች ፊት በሐሰት ተከሶ ቀረበ፥ ያለ በደሉ ተፈረደበት፥ እርጥብ መስቀል ተሸክሞ ደከመ፥ በደላችንን ተሸክሞ ተራራ ወጣ፥ በክፉዎች መሀል ተሰቀለ፥ ውኃ ፈልጎ በቸርነት የሚሰጠው አጣ፥ የጭፍሮች መሳለቂያ ሆነ፡፡ይህን መከራ ኢሳይያስ እንዲህ ይተነትናል
" በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፤ እኛ ግን እንደ ተመታ በእግዚአብሔርም እንደ ተቀሠፈ እንደ ተቸገረም ቈጠርነው።እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ።ተጨነቀ ተሣቀየም አፉንም አልከፈተም፤ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፥ በሸላቶቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። " ኢሳ 53 ሙሉውን ያንብቡ! ይህን የታመነ ጌታ እንደ ተሰቀለ ሆኖ በፊታችን ተስሏልና ይታዬን፦ ብናየው አንለያይም፥ ብናየው አንከፋም፥ ብናየው አንሸነፍም፥ ብናየው ለእውነት እንታዘዛለን፡፡ ኢትዮጵያ የተሰቀለውን ስታይ ታርፋለቺ፣የችግሮች ሁሉ መንስኤ እርሱን አለማየት ነው፡፡አዚምን ቆርጦ እንድናየው ያግዘን።
 
  ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

Wednesday, April 24, 2019

❖ጸሎተ ሐሙስ፦

የመጨረሻው እራት፦

ዛሬ ጌታችን ከደቀመዛሙርቱ ጋር የመጨረሻውን እራት የበላበት እና እግራቸውን በትሕትና ያጠበበት ዕለት ነው፡፡ማቴ. 26፡20-29።ይህን እራት ጌታ ከደቀመዛሙርቱ ጋር ሊበላ በናፍቆት ይጠብቀው ነበረ፡፡ " እርሱም። ከመከራዬ በፊት ከእናንተ ጋር ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር፤"ሉቃስ  22:15።

በሞት ዋዜማ ራት፡ በመከራ ዋዜማ ራት፡ ወዳጅ እንደሚሸሽ እየተረዳ ከወዳጅ ጋር ራት ይገርማል፡፡የመጨረሻ ነገር ትዝታ የሞላው ነው፡፡ልቡ ውስጥ ዘመናት የማያስረጁት ጥልቅ ፍቅር እና ክብር አለ፡፡ቃሉ እንዲህ ሲል አረጋገጠው፦ "ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው።"ዮሐንስ 13:1 ይህ ሁላችንም እርግጠኛ ሆነን የምንናገረው ፍቅር ነው፡፡አምላክ አለን ወገን የሆነን፥ወዳጅ አለን ወገን ያደረገን፡፡ልባችን በዚህ ይታመን አጥብቆ ወዶናል፡፡አንስጋ የወደደን ለዘላለም ነው፡፡

ዛሬ ልዩ ነው፦ ደቀመዛሙርቱም እራት ከበሉ በኋላ የዘመሩበት የምስጋና ምሽት ነበር፡፡ ማቴ. 26፡30።

በዚህ ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ- የሐዲስ ኪዳን ሥርዓት ሰርቷል፤አዲስ ኪዳን ስላደረገ ስለዚህ  ዕለቱ የአዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል፡፡ማቴ. 26፡26።

የደቀመዛሙርቱን እግር አጥቧል፤ስለዚህ ዕለቱ ሕጽበተ እግር ሐሙስ ተብሏል፡፡ዮሐ. 13፡2-14።

በአረንጓዴው የአትክልት ስፍራ ጸልዮአል፤ስለዚህ ዕለቱን ጸሎተ ሐሙስ ተብሏል፡፡ማቴ. 26፡36-41

እስከ መጨረሻ ከወደዳቸው መካከል  በችኮላ የሚታወቀው  ጴጥሮስ፥ ተጠራጣሪው ቶማስ፥ አፍቃሪው ዮሐንስ፥ አሳልፎ የሚሰጠው ይሁዳ ይገኙበታል፡፡ይህን ሁሉ ችሎ እስከ መጨረሻው መውደድ እጅግ ይገርማል  እኛ ሰውን ሳናውቀው ወደነው ስናውቀው እንጠላዋለን፡፡
ይህ ምን አይነት ፍቅር ነው? ስንደክምም ስንበረታም ስናጠፋም ስናለማም የማይለወጥ ፍቅር፡፡ይህ ፍቅር
በትህትና  ሲገለጽ መምህሩ ተማሪዎችን፥ ጌታ ባሪያዎችን እግራቸውን ሲያጥብ አየን፡፡እሱ ያላጠበው አይነፃም፡፡እሱ ያላጠበው ከእርሱ ጋር እድል የለውም፡፡ከዘላለማዊ በደል በደሙ ያጠበን ይህ ትሑት ሊቀካህናት ነው፡፡ይህን የተደረገልንን እናስተውላለን?እርሱም በቃሉ ያደረኩላችሁን ታስተውላላችሁን  ? ብሎናል።ልዑሉ በፍቅር ጎንበስ ማለቱ ይግባን፡፡ውለታ አናጥፋ፡፡ ዝቅ ብሎ ከፍ ማድረጉን አንርሳ፡፡በእውነት ፍቅሩን አስተዋይ ትውልድ መሆን አለብን፡፡መተጣጠቡን  እርስ በእርሳችን እንዲሁ እናድርገው፡፡ለበዓሉ ብቻ ሳይሆን የዘወትርም ተግባራችን ይሁን፡፡ቃሉ ይህን ብታዉቁ ማወቅ ብቻ አይጠቅምምና ብታደርጉ ብፁዓን ናችሁ ይለናል፡፡ክርስትና የፍቅር ድርጊት እንጂ የአፍ ማስመሰል አይደለም፡፡ጌታ በሕይወት በድርጊት ነው ያስተማረን፡፡  
  
   ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

Thursday, April 18, 2019

❖ሆሳዕና፦

          እንኳን ለሆሳዕና በዓል አደረሰን!!!
❖ሆሳዕና ፦
        ሆሳዕና ማለት አሁን አድን ወይም መድኃኒት ማለት ነው!
የሚቀድሙ እና የሚከተሉ ሕፃናት እና አዋቂዎች የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው ፥ልብሳቸውን አንጥፈው የሰማዩ ልዑል በተናቀች አህያ ጀርባ ተጭኖ ሲገባ፦  "ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስምየሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር።" (ማቴ. 21፥9)
   መረጋጋት ላቃታት ለኢየሩሳሌም ቅኝ አገዛዝ ለጸናባቸው ለአይሁድ "አሁን አድነን" ትልቅ ልመና ነበረ፡፡እያመሰገኑ መለመን መታደል ነው፡፡ በልቡ እንቆቅልሽ ታቅፎ ከከንፈሩ የእግዚአብሔር ምስጋና የማይጎድልበት ምስጉን ነው፡፡ ዛሬም ሆሳዕና እንበል፥ የምስጋና ነዶ በፊቱ እያከማቸን አቤቱ አሁን አድን እንበል፡፡ የዳዊት ልጅ ሆይ ማረን ፥ሆሳዕና ለዳዊት ልጅ እያልን እንጩህ!

❖ወንጌል ስለ ሆሳዕና ምን አለ?
      1/☞ለጌታ ያስፈልጉታል!
"በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፥ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርስዋ ጋር ታገኛላችሁ፤ፈትታችሁ አምጡልኝ።ማንም አንዳች ቢላችሁ። ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ፤ ወዲያውም ይሰዳቸዋል።" (ማቴ. 21፥2)
  ደቀመዛሙርቱ የታሰሩትን እንዲያስፈቱ ተልዕኮ ሲሰጣቸው "ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ" ከሚል ትእዛዝ ጋርነበረ፡፡ ጌታ ወደዚህ ዓለም የመጣው በኃጢአት የታሰረውን የሰውን ልጅ ለመፍታት ነው፡፡

  አዎ!  ታስሮ አስፈትቶናል፥ ወድቆ አንስቶናል፥ ደሙን ክሶ ከማዕሰረ ኃጢአት ፈትቶናል፡፡.  
    ዛሬም በሱስ በኃጢአት በተንኮል በክፋት በአመፃ ወደታሰሩት ሰው ይልካል! ከሞት ጋር ወደተስማሙት የሟቹን ሞት የማይፈቅድ ጌታአገልጋዮችን ይልካል፡፡ እኛ ተስፋ የቆረጥንባቸው ሁሉ ለጌታ ያስፈልጉታል፡፡ ዛሬም የታመሙ እንዲፈወሱ፥ የወደቁ እንዲነሱ፥ የታሰሩ እንዲፈቱ፥ ያዘኑ እንዲጽናኑ፥ የተሰበሩ እንዲጠገኑ፥ የጠፉ እንዲገኙ ክርስቶስ ይፈልጋል፡፡

የኃጢአት እሳት ላይ የሚጫወተው፥ በሞት መንደር ያንቀላፋው ትውልድ ባለቤት አለው፡፡ ፈላጊ አለን፥ አክባሪ አለን፥ የማይጸየፈን አባት አለን፡፡ በራሳችን ተስፋ የቆረጥን፥ ለማንም አላስፈልግም የምንል ለጌታ እናስፈልጋለን፡፡
   
        2/☞ንጉሣችን ይመጣል!

    " ለጽዮን ልጅ። እነሆ፥ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደአንቺ ይመጣል በሉአት ተብሎ በነቢይ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሆነ።" (ማቴ. 21፥4-5)
   በመገፋት የእርሱን ቀን ለምትጠብቁ፥ ቀን ያስጎነበሳችሁ፥ ከተማችሁ በቅኝ ገዥዎች የተያዘባችሁ፥ ስጦታው ነክቷችሁ በጸጋ ተሹማችሁ ዙፋን ተከልክላችሁ ወደ ምድረ በዳ የተሰደዳችሁ፥ ወንድማችሁ የቃየልን ድንጋይ እያሳየ የሚያስፈራራችሁ ንጉሣችን ይመጣል የሚያነግሰው ይመጣል ቀን አውጭው ይመጣል የሆሳዕና የዋህ ሆኖ እንደ ትንቢቱ የመጣው በስልጣን ይመጣል!
     
     3/☞የሚቀድሙት እና የሚከተሉት የእርሱ የምስጋና ሠራዊት ናቸዉ!

 " የሚቀድሙትም ሕዝብ የሚከተሉትም  ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕናበአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር።" (ማቴ. 21፥9)
  በአህያ ጀርባ ያየነው በእሳታውያን ኪሩቤል እና በሱራፌል ጀርባ የነበረ ነው፤ ይህ ምስጋና ይገባል። የሚቀድሙት ነቢያት፡ የሚከተሉት ሐዋርያት አመስግነውታል።

ወደፊትም የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው በጉን ይከቡታል፤ ወድቀው ይሰግዱለታል፡፡ ትውልድ ለምስጋና ይነሳ ፥ ለእርሱ ያንጥፍ ፥ ለእርሱ መንገዶች ሁሉ ክፍት ይሁኑ ፥ ለእርሱ አንደበት ሁሉ ይቀኝ ፥ ለእርሱ ትልቅ ትንሹ አዋቂ ሕፃኑ ምስጋና ያቅርብ!
   
        4/☞ይህ ማን ነው ?

     "ወደ ኢየሩሳሌምም በገባ ጊዜ መላው ከተማ። ይህ ማን ነው? ብሎ ተናወጠ።" (ማቴ 21:10)
  ይህ ማነው ከተማ የሚናወጥለት ? ይህ ማን ነው ዓለሙ ሁሉ የሚከተለው ? ይህ ማነው ? ይህ የኛ ልዑል ነው፡ ይህ የኛ ቤዛ ነው፡፡ ይህ የኛ የዘመናት ወዳጅ ነው፡፡ ይህ የኛ አምላክ ነው። ሞገድ ባሕር የሚታዘዝለት ይህማን ነው ? ልዑል ሳለ በትሕትና የተገለጸ ይህ ማነው ? ንጉሥ ሆኖ ሳለ የዋህ የሆነ ይህ ማነው? ይህ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡
     
        5/☞አንኩራበት፦

   " ከሕዝብም መካከል ከፈሪሳውያን አንዳንዱ። መምህር ሆይ፥ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው አሉት። መልሶም።እላችኋለሁ፥ እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ አላቸው።" (ሉቃስ 19:39-40)
  እርሱ የምስጋና ጌታ ነው፤ ባናመሰግነው ምስጉን ነው፡፡ በምስጋና የምንጨምርለት፤ ባለማመስገን የምንቀንስበትነገር የለም፡፡ ስለዚህ አመስጋኞችን አንገስጽ፡፡ እጃችንን አጣጥፈን ዳር ይዘን ተመልካች አንሁን፡፡  ሜልኮል ኮርታምን አተረፈች? አንኩራ አንታበይ እኛ ዝምታን ብንመርጥ ድንጋዮች እንኳ ለቅኔ ሊነሱ ዝግጁ ናቸውና፡፡
     
          6/☞የልባችን ደጅ ይከፈት!

     " ይህች ትውልድ እርሱን የምትፈልግ ናት፥ የያዕቆብን አምላክ ፊት የምትፈልግ። እናንት መኳንንት፥ በሮችን ክፈቱ፥የዘላለም ደጆችም ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ። ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው? እግዚአብሔር ነው፥ ብርቱናኃያል፥ እግዚአብሔር ነው፥ በሰልፍ ኃያል።" (መዝ 24:6-9)
  ዛሬ የቤተክርስቲያናችን ሥርዓተ አምልኮ በዚህ ቃል የተመሠረተ ነበረ፡፡ ይህ ልዑል የዘላለም ደጆችን የከፈተ ነው፥ የሕይወት ቁልፍ በእጁ ነው፥ የገነት ቁልፍ በእጁ ነው፥ የስኬት ቁልፍ በእጁ ነው፡፡
ለሁሉ የከፈተ እርሱ እንዴት ደጅ ይዘጋበታል? መኳንንት ሆይ ክፈቱ! ሁሉም በተሾመበት ነገር ባለስልጣን ነው ፥በሀብት በእውቀት በውበት በስልጣን ተሹመን ይሆናል እንዳንከፍት እነዚህ ነገሮች አጥምመውን ይሆን ? አታለውን ይሆን? በሚያልፈው ታምነን ከማያልፈው እንዳንጎድል የልባችንን ደጅ እንክፈት፡፡
     
        7/☞እርሱ ይኑርብን፦

     አህያዋ እርሱን በመሸከሟ ተከበረች፡፡ በልዩ አጀባው ውስጥ ተራመደች፡፡ እርሱ ያለው ሞገስ አለው፡፡ በተለይ በሰማይ የበለጠ ክብር ይጠብቀዋል፡፡ ልባችን የእርሱ ዙፋን ከሆነ መክበር አለ፡፡እርሱን እያሳየን እንዙር፡፡ " የኢየሱስ ሕይወት ደግሞ በሥጋችን ይገለጥ ዘንድ ሁልጊዜ የኢየሱስን መሞት በሥጋችን ተሸክመን እንዞራለን።" (2ኛ ቆሮንቶስ 4:10)።
   
      8/☞ለሰላማችን የሚሆነውን አንግፋ፦

  "ለሰላምሽ የሚሆነውን በዚህ ቀን አንቺስ ስንኳ ብታውቂ፤ አሁን ግን ከዓይንሽ ተሰውሮል::ወራት ይመጣብሻልና፥ጠላቶችሽም ቅጥር ይቀጥሩብሻል ይከቡሻልም በየበኵሉም ያስጨንቁሻል፤አንቺንም በአንቺም ውስጥ የሚኖሩትን ልጆችሽን ወደ ታች ይጥላሉ፥ በአንቺ ውስጥም ድንጋይ በድንጋይ ላይ አይተዉም፥ የመጐብኘትሽን ዘመን አላወቅሽምና።" (ሉቃ 19:42-44)
  ክርስቶስ የሰላም አለቃ ነው፡፡ እርሱ የሌለው ሰላም የለውም፡፡ እርሱ የልብ ሰላም፣ ዕረፍት እና መድኃኒት ነው፡፡ለሰላማችን የሚሆነው ክርስቶስ ነው፡፡ ለእርሱ ደጅ አንዘንጋ፡፡ለእርሱ ጀርባ አንስጥ፡፡ ሰላሙን ለመጠቀም ልባችንን ክፍት አድርገን እንጠብቀው፡፡               

               የእግዚአብሄር ጸጋና ሰላም ከሁላችን ጋር ይሁን!!!
                            ===●===●===●=== 

Friday, April 12, 2019

❖ኒቆዲሞስ፦

❖ኒቆዲሞስ፦
    "ዳግም መወለድ"
የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት ኒቆዲሞስ ነው፡፡ ባለ ታሪኩ ኒቆዲሞስ የጌታ የማታ ተማሪ፥ የአይሁድ መምህር እና የሸንጓቸው አባል ነው፡፡ዮሐ 3:1-14 ተመልከቱ። ክርስቶስ በስውርም በግልጥም መማር ለሚፈልጉ አስተምሯል፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ ሊቅ ስለነበረ ከወገኖቹ ተሰውሮ በማታ ነበረ የተማረው፡፡ የማታ አእምሮ ሥራ የጨረሰ የተረጋጋ ነው፥ ለትምህርት እና ለጸሎት መልካም ጊዜ ነው፡፡ የቤተክርስቲያን አብዛኛው የቃልና የዜማ ትምህርት በማታ የሚሰጥ ነው፡፡ የኒቆዲሞስ ሌሊት የተመስጦ፥ ቁጭ ብሎ መማሪያ፥ የሕይወትን መምህር ክርስቶስን መስሚያ ነበረ ፤ የእኛስ ሌሊት ምን እየሠራንበት ያልፋል ? በተመስጦ፣ በዝማሬ፣ በጸሎት፣ ከእግዚአብሔር ጋር ነው የምናሳልፈው ?

ኒቆዲሞስ መምህርም ሆኖ ይማራል፡ መምህር መማር አለበት፡ መማር ያቆመ መምህር ማስተማር ማቆሙ አይቀርም፥ እውቀት መጨመር ያስፈልጋል! እኛ አንድ ዘመን የተማርነውን ነው ስንናገር የምንኖረው ቁጭ ብሎ መማር ውርደት ይመስለናል፡፡ መማር አያሳፍርም፤ የሚያፍር ካለ ተሰውሮም ቢሆን ይማር፡፡ የተማርነውን በጥናት በምንባብ አናሰፋም። ኒቆድሞስ የእግዚአብሔርን ቃል ለመማር ጊዜ የለንም ለምንል ሰዎች አስተማሪ ነው። ጌታ ለኒቆዲሞስ የዳግም ልደት ትምህርት ነው ያስተማረው፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ለመሆን ዳግም መወለድ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ልደት ረቂቅ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የምንዛመድበት መንፈሳዊ ልደት ነው፡፡ ዳግም መወለድ ወደ እናት ሆድ ተመልሶ መግባት አይደለም፡፡ ዳግም ልደት ላመነ ሰው በመንፈስ ቅዱስ አሠራር የሚከናወን ሰማያዊ ልደት ነው፡፡

ዳግም ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፡፡ስለተወለድን የመለኮት ክብር ተካፋዮች ሆነናል፡፡ ስለተወለድን እግዚአብሔርን አባት ስንለው ልጅነት ይሰማናል። ስለተወለድን የልጅነት ስልጣን አለን።

ኒቆዲሞስ በክርስቶስ ላይ ከንቱ ክስ ሲነሳ ወገኖቹን ተከራክሯል፥ ሁሉ በሸሸበት ሰዓት የጌታን ቅዱስ ሥጋ በክብር የቀበረ ወዳጅ ነው! በስውር ቢማርም በሕይወት ተገልጧል፡፡ የቁርጥ ቀን ወዳጅ ነው፡፡አንድ ቀን ለእግዚአብሔር እንኳን መኖር መታደል ነው! ከመስቀል ልናወርደው መቼ ነው የምንመጣው ? መቼ ነው ለክብሩ ቀንተን ተገልጠን የምንናገርለት ? መቼ ነው ለእርሱ መቆጠርን የማናፍርበት?
ከመንፈስ እንደ ተወለደ መንፈሳዊ ሰው ኖረን መንፈሳዊውን ዓለም በክብር ለመውረስ ያብቃን!!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
===●===●===●===

Friday, April 5, 2019

❖ላከበረን መኖር፦

ላከበረን መኖር

ኢየሱስ ክርስቶስ ለኃጢአታችን እንደ ሞተ እና እኛን ስለማጽደቅ እንደ ተነሳ ካመንን እና በዚህ እምነት የተቀበልነውን ስልጣን መጠቀም ከጀመርን የሚጠበቅብን ላከበረን ክብር መኖር ነው፡፡ እኛ እንድንከብር የተዋረደ አለ፤ እኛ በነፃ እንድንለቀቅ የታሰረ አለ፤ እኛ እንድንለብስ የተራቆተ አለ፤ እኛ እንድናርፍ ያቃሰተ አለ፡፡ እርሱም፡- ጻድቅ የሆነው ኢየሱስ ነው፡፡ እንዲህ ሆኖ ላከበረን ለእርሱ መኖር አለብን፡፡
እኛ የራሳችን አይደለንም፤ በደም ዋጋ የገዛን አለ፡፡ 1ቆሮ 6፡20፡፡ ላከበረን መኖር መጀመር አለብን፡፡ “በሕይወትም ያሉት ስለ እነርሱ ለሞተውና ለተነሣው እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው እንዳይኖሩ ስለ ሁሉ ሞተ።” እንደተባለ፡፡ 2ቆሮ 5፡15፡፡ እኛ እና ዓለማችን ለክብሩ መንበርከክ አለብን፡፡ በእኛ ላይ በሚሰራው የእግዚአብሔር ኃይል በዙሪያችን መልካም ተጽዕኖ ማምጣት አለብን፡፡
የራሳችንንም የሌሎችንም ሕይወት ውብ በማድረግ አባታችንን እናስከብር፡፡ መብላታችን እና መጠጣታችን አንኳን ሳይቀር ለክብሩ እዲሆን ይፈለጋል፡፡ “እንግዲህ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትሆኑ ወይም ማናቸውን ነገር ብታደርጉ ሁሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት።” 1ቆሮ 10፡31፡፡ እያንዳንዱ የኑሯችን ገጽ አዳኛችንን መተረክ አለበት፡፡ ለራሳችን የሮጥንበት ዘመን ይብቃ እና ደግሞ ላከበረን እንኑር፡፡

  ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

❖የዘለዓለም መኖርያ፦

የዘላለም መኖሪያ

"ይሹሩን ሆይ፥ በሰማያት ላይ ለረድኤትህ፥
በደመናትም ላይ በታላቅነት እንደሚሄድ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማንም የለም። መኖሪያህ የዘላለም አምላክ ነው፥  የዘላለምም ክንዶች ከአንተ በታች ናቸው፤" ዘዳ 33:27

የሰው መሠረታዊ ፍላጎቶች ምግብ፥ መጠለያ፥ ልብስ ናቸው።ልብስ እና ምግብ ኖሮን በኪራይ መኖሪያ ተጠልለን እንኖራለን።አንዳንዶች ይህንም ስላልቻሉ በየጎዳናው ያድራል።ቃሉ ለሁሉ የሚበቃ የዘላለም መኖሪያ እግዚአብሔር እንደሆነ ይነግረናል።ከእርሱ ርቃን በደጅ ያለን፥ ከፍቅሩ ተለይተን ራሳችንን በስቃይ የምንጎዳ፥ ያለ እርሱ ወጥታን ባክነን  የምንመለስ፥ ያለእርሱ ዘምተን የተሸነፍን ፥ ያለ እርሱ ሮጠን ያልቀደምን ፥ ያለ እርሱ በልተን ያላማረብን፥ ያለ እርሱ ለብሰን የበረደን፥ ያለርሱ ሰብስበን የተበተነብን ሁሉ ወደ ሕያው እግዚአብሔር ዘወር እንበል  ብለን እንማልዳችኋለን።ወደ የዘላለም መኖሪያ ከተን ገብተን እንረፍ።ስለሚፈርስ ቤት፥ ዝናብ እና ነፋስ ስለሚያስገባ ቤት አይደለም የማወራችሁ።ከመከራ እና ከጉዳት የሚጠብቅ የዘላለም መጠለያ ስለሆነው አምላክ ነው።
ቃሉ እንዲህ ይለናል፦ "በልዑል መጠጊያ የሚኖር ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ ያድራል። እግዚአብሔርን። አንተ መታመኛዬ ነህ እለዋለሁ፤ አምላኬና መሸሸጊያዬ ነው፥ በእርሱም እታመናለሁ።እርሱ ከአዳኝ ወጥመድ ከሚያስደነግጥም ነገር ያድንሃልና።" መዝ 90:2 ይህ የዘላለም መኖሪያ የዘላለም አምላክ ነው።በመከራ ጊዜ መሸሸጊያ ነው።ከክፉ መዳኛ ነው።ወደ እርሱ የገቡ በውጭ ያለው የዓለም ነገር ያንስባቸዋል። እንደ እርሱ የለም።እግዚአብሔር ካለን ምንም አልጎደለን፥እርሱ ከሌለን ምንም የለንም፤ እኛም እንዳለን አንቁጠረው።ሕይወት በእርሱ መገኘት ውስጥ ስትሆን ነው በደስታ እና በባርኮት የምትጎበኘው።
የእስራኤል መኖሪያ ከነአን አይደለም።መኖሪያቸው የበረሀው ገነት እግዚአብሔር ነው።ዓለም ጭንቅ እየናጣት እኛ በደስታ የተሞሸርንበት የደስታ እልፍኝ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ትውልድ በርኩሰት ሲነድድ የእግዚአብሔር ልጆች መጠለያ መንፈስ ቅዱስ ነው።ተንከራታቾች ሆይ ወደ ዘላለም መኖሪያ ወደ ዘላለም አምላክ እንሰብሰብ።

   ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

❖የእግዚአብሔር ጸጋ፦

የእግዚአብሔር ጸጋ

የእግዚአብሔር ቃል "ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገልጦአልና፤ ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤" ይላል፡፡ወደ ቲቶ 2:11 የተገለጠው የእግዚአብሔር ጸጋ፡-
1/ ዘር ሳይለይ ሰዎችን ሁሉ ያድናል!
2/ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ያስክዳል!
3/ የተባረከውን ተስፋችንን የኢየሱስን መገለጥ ያስጠብቃል!
4/ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል እንድንኖር ያስተምረናል!

የእግዚአብሔር ጸጋ የተገለጠው ኢየሱስ በሥጋ ሲገለጥ ነው፡፡ ቃሉ "ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።" እንደሚል፡፡          ዮሐንስ 1:14 የተገለጠዉ ጸጋ ለዓለም ህዝብ ሁሉ ይበቃል፡፡ ሁሉንም ለማዳን በቂ የሆነ ጸጋ ነዉ፡፡ በጸጋው ለመዳን ፈቃደኝነት እና እውነተኛ እምነት ያስፈልጋል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል “ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም” ይላልና፡፡ መዳን በነፃ ነው፤ ሰው ምንም ዋጋ አይከፍልበትም፡፡ ስላልከፈልንበት መዳናችን ዋጋ አልተከፈለበትም ማለት አይደለም፡፡ እርሱ ከፍሎልን ለእኛ ግን ስናምን እንዲያው (Freely) በነፃ ሰጠን፡፡ “"በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ።" ሮሜ 3:24 እምነቱ እንኳን ከእኛ ነው ብለን እንዳንሞግት “የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም” አለን፡፡ እንዲያው የእርሱ ሥራ ይደንቃል፡፡ አሜን ብለን እንስማማ!! እግዚአብሔር ሰዎችን ሁሉ ሊያድን እጁን በጸጋ ዘርግቷል፤ እኛም የልባችንን እጅ በእምነት እንዘርጋ።
  
ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

❖የመከናወን ምንጭ፦

የመከናወን ምንጭ

ብዙዎቻችን ነገር እንዲከናወንልን፤ ኑሮ እንዲቀናልን እንፈልጋለን፡፡ ዛሬ የክንውንን ምንጭ እንመለከታለን፡፡ ዳዊት “ምስጉን ነው በክፉዎች ምክር ያልሄደ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ፥ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ። ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ (ቃል) ደስ ይለዋል፥ ሕጉንም (ቃሉንም) በቀንና በሌሊት ያስባል። እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።” አለ፡፡ መዝ 1፡1-3፡፡

እንዲከናወንልን ምርጫችንን (ዝንባሌያችንን) እንቀይር፡፡ በክፉዎች ምክር አንሂድ፤ በኃጢአተኞችም መንገድ አንቁም፤ በዋዘኞችም ወንበር አንቀመጥ፡፡ ሥራ ስንሰራ በጽድቅ እንስራ፡፡ ክፉዎች፣ ኃጢአተኞች እና ዋዘኞች የተባሉት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የማይሰሩ ናቸው፡፡ ምክር ወደ መንገድ ይመራል፤ መንገድ ወደ ወንበር ያደርሳል፤ ወንበር ደግሞ መድረሻን (ስኬትን) ያሳያል፡፡ የጽድቅም የአመጻም መንገድ ስኬት ይደርሳል፡፡ስለዚህ ዋናው ወደ ስኬት መድረስ ሳይሆን ወደ ስኬት ለመሄድ የመረጥነው መንገድ ነው፡፡ ብር ማግኘት ሳይሆን ያገኘንበት መንገድ መታየት አለበት፡፡ እንዲከናወንልን በእግዚአብሔር ሕግ (ቃል) እንጠቅለል፡- ደስታችን በሕጉ (በቃሉ) ይሁን፤ ቀንና ሌሊታችን ሕጉን (ቃሉን) በማሰብ፤ ለቃሉ በመታዘዝ መኖር ይሁን፡፡ ከዚያ ውጤቱ፡- በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ እንሆናለን፤ ወቅት ሳንጠብቅ እናፈራለን፡፡ የምንሰራው ሁሉ ይከናወንልናል፡፡

ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

❖የአለማወቅ ጥፋት፦

አለማወቅ የደገሰው ሞት

እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን አለማወቅ የጥፋት ሁሉ ምንጭ እንደሆነ ተናግሯል፡፡ "ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል፤ አንተም እውቀትን ጠልተሃልና እኔ ካህን እንዳትሆነኝ እጠላሃለሁ፤ የአምላክህንም ሕግ ረስተሃልና እኔ ደግሞ ልጆችህን እረሳለሁ" ሆሴዕ 4:6 ሰው የሳተው ትልቅ እውቅት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡
በአዲስ ኪዳን ደግሞ ጳውሎስ እግዚአብሔርን ለማወቅ አለመፈለግ ወደ ሞት እንደሚያደርስ ተናግሯል፡፡ “እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ዓመፃ ሁሉ፥ ግፍ፥ መመኘት፥ ክፋት ሞላባቸው፤ ቅናትን፥ ነፍስ መግደልን፥ ክርክርን፥ ተንኰልን፥ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፤ የሚያሾከሹኩ፥ ሐሜተኞች፥ አምላክን የሚጠሉ፥ የሚያንገላቱ፥ ትዕቢተኞች፥ ትምክህተኞች፥ ክፋትን የሚፈላለጉ፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያስተውሉ፥ ውል የሚያፈርሱ፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ምሕረት ያጡ ናቸው፤ እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም።” ሮሜ 1፡28-32 እነዚህ የተዘረዘሩት 21 ነውሮች እግዚአብሔርን ለማወቅ ባለመውደድ ለማይረባ አእምሮ በተሰጡ ሰዎች የተሠሩ ናቸው፡፡ወገኖቼ እውቀትን መጥላት የለብንም፡፡ እውቀት ካጣን እንጠፋለን፡፡ በተለይ እግዚአብሔርን ማወቅ አስፈላጊ ነው፡፡ ውስጣችን  እግዚአብሔርን ይጠማ፤ ፊቱን እንፈልግ፤ ሳንፈልገው የፈለገንን አምላክ እንፈልገው፡፡

ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

Thursday, April 4, 2019

❖ገብርሄር፦

ጸጋን ለሰጠን መታመን፦

ገብርኄር ማለት መልካም ፥ ቸር ፥ ለጋስ ፥ ታማኝ አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ መታመንን፥ ታማኝ አገልጋይነትን፥ የመታመንን ዋጋ፥ የአለመታመንን ቅጣት ያመለከተበት ምሳሌያዊ ታሪክ እንደሚከተለው ቀርቧል በማስተዋል እናጥናው፦

  "ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደ ሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና፤ለእያንዳንዱ እንደ ዓቅሙ፥ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ወዲያው ሄደ።አምስት መክሊትም የተቀበለው ሄዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ፤ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ። አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቈፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ።ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው።አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ። ጌታ ሆይ፥ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት አለ።ጌታውም። መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።ሁለት መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት አለ።ጌታውም። መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፥ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ።ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው። አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ፥ ካልዘራሁባት እንዳጭድ ካልበተንሁባትም እንድሰበስብ ታውቃለህን? ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር፥.....እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር።ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት አሥር መክሊትም ላለው ስጡት፤ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል። የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።"ማቴ 25:14-30

ይህ ታሪክ ምን አስተማረን? ራሳችንን አሳየን? ምንድነው የተቀበልነው ? ምን ያህል አተረፍንበት ? የጸጋ ስጦታችንን እናውቃለን? ድርሻችንን ተወጥተናል ? የኛ መክሊት ለሌሎች ምን ጠቀመ? በሌሎችስ መክሊት ምን ተጠቀምን ? በመክሊታችን ሰጭውን አከበርንበት ? እግዚአብሔር እንደ አቅማችን ማትረፊያ መክሊት ሰጥቶናል፡፡ የሰጠንን መቅበር አንችልም፡፡ በተሾምንበት ነገር ታማኝ መሆን አለብን፡፡ የተቀበልን ነን የተቀበለ ደግሞ ይሰጣል የተቀበለ ሰጪውን ያከብራል የተቀበለ እንዳልተቀበለ አይኩራራም፡፡የተሰጠንን ሳንሰጥ ከሄድን እንጠየቃለን፡፡ በተሰጠን መክሊት ራሳችንን እና ሌሎችን ለእግዚአብሔር ክብር ማትረፍ አለብን፡፡ ድርሻችንን መወጣት አለብን፡፡ በአቅማችን ከሠራን በተሰጠን ከታመንን እግዚአብሔር በዚህ ደስ ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር አለመታመንን ይጠላል፡፡በተሰጠን ታምነን ማትረፍ አለብን፡፡

ከምድር የጠፋ ትልቁ ሀብት ታማኝነት ነው፡፡ሰው እንኳን ሰውን ራሱን የሚያታልልበት፥ ለራሱ እንኳ መታመን ያልቻለበት ሁኔታ አለ፡፡እግዚአብሔር ሳይሰጥ አልጠየቀም። ለጋስነቱን እያመሰገንን በተሰጠን ልክ ታምነን መሥራት አለብን፡፡በተሰጠን በተሾምንበት በጥቂቱ ከታመንን እግዚአብሔር በብዙ ይሾመናል፡፡ ገብርኄር የአገልግሎቱ ባለቤት እግዚአብሔር ከአገልጋዮች የሰጠውን አደራ ሊቀበል እንደሚመጣም ያሳያል፡፡ አገልጋይ ጌታ ወይም አሠሪ አለው፡፡ አሠሪው ሁሉንም በአቅሙ ልክ ጸጋ ሰጥቶ ነው ያሠማራው፡፡እንደሰጠን መጠን በኋላ ዋጋ ይከፍላል፡፡ ስለዚህ አገልጋይ አትራፊ መሆን አለበት፡፡ በተለይ መንጋውን ማትረፍ አለበት፡፡ታማኝ አገልጋይ ወይም እረኛ ለበጎቹ ሕይወት ዋጋ ይከፍላል፡፡ የተበተነውን ይሰበስባል፤የወደቀውን ያነሳል ያዘነውን ያጽናናል፥ የተሰበረውን ይጠግናል፤ የራሱን ጥቅም አይፈልግም፤ በጎችን ለጥቅሙ አይሰዋም፤ ግን እረኝነት እንዲህ እየሆነ አይደለም።

እረኞች ሆይ ሕዝቡ ባለቤት አለው፥ በአግባቡ ምሩ። የሾማችሁ አንድ ቀን ወደ እናንተ ይመጣል፥ ያኔ ምን ልትመልሱ እንዳላችሁ አስቡ። ቃሉ እንደሚል "ጮማውን ትበላላችሁ ጠጕሩንም ትለብሳላችሁ፥ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፤ በጎቹን ግን አታሰማሩም። የደከመውን አላጸናችሁትም የታመመውንም አላከማችሁትም የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም የባዘነውንም አልመለሳችሁትም የጠፋውንም አልፈለጋችሁትም በኃይልና በጭቈናም ገዛችኋቸው።" የሚለው እየተፈፀመ ነው፡፡ ሕዝ 34:3።

እግዚአብሔር የጠፉበትን ከእርሱ ርቀው እንዲሞቱ የተፈረደባቸውን ነፍሳት ደም ከእረኞች እጅ ይፈልጋል፡፡ ታምኖ የሚሠራ አገልጋይ ከክብር ጋር ከሽልማት ጋር ነው ወደ ጌታ ደስታ የሚገባው፡፡  ታምኖ የማይሰራ ከመንጋው ጮማውን እየበላ፣ ጠጉሩን እየለበሰ፣ አጥንቱን እየቀለጣጠመ ራሱን የሚያሰማራ እረኝነቱ( ፀጋው) ይወሰድበታል። ሌላ ታምኖ የሚሰራ ይዘጋጃል ዘካ 11:15 ። ታምኖ የጠፋውን በመፈለገ ማዳን ፣ የዳነውንም መቀለብ የበጎ ታማኝ አገልጋይ መገለጫ ነው።
     ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!