Friday, April 26, 2019

❖እንደ ተሰቀለ...!

መስቀል ላይ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ይታዬን!

" የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?"
ገላትያ ሰዎች 3:1

እንኳን አደረሰን!! ዛሬ ነፃነታችን በደም የተገዛበት ዕለት ነው።
ዛሬ የፍቅር ጥግ የታየበት ጌታችን ነፍሱን ለወዳጆቹ አሳልፎ የሰጠበት ነው።
ዛሬ ለእኛ የሚገባውን መከራ ሁሉ ተቀብሎ ልጆች የተደረግንበት ነው።የሰማይና የምድር ንጉስ ልጅ ሆነን አንነስ እባካችሁ በልባችን ይታተም እንኑርበት ፣
ዛሬ ተርቦ እኛን ያጠገበበት ፣ተጠምቶ እኛን ያረካበት ፣ቆስሎ እኛን የፈወሰበት፣የማይገባውን ሞት ተቀብሎ የማይገባንን ሕይወት ለእኛ የሰጠበት ቀን ነው፡፡ይህ ሁሉ ለእኛ ነው።

ከዘመናት በፊት ጌታችን ኢየሱስ በዛሬው ዕለት ትውልድ ፊቱን አዞረበት( ዛሬም ከተፈጠርንለት አላማ ውጪ መኖር እርሱ ላይ ፊትን ማዞር እንደሆነ ይሰመርበት)።በአይሁድ ተገርፎ፥ በወዳጅ ተከድቶ ታመመ፡፡በገዥዎች ፊት በሐሰት ተከሶ ቀረበ፥ ያለ በደሉ ተፈረደበት፥ እርጥብ መስቀል ተሸክሞ ደከመ፥ በደላችንን ተሸክሞ ተራራ ወጣ፥ በክፉዎች መሀል ተሰቀለ፥ ውኃ ፈልጎ በቸርነት የሚሰጠው አጣ፥ የጭፍሮች መሳለቂያ ሆነ፡፡ይህን መከራ ኢሳይያስ እንዲህ ይተነትናል
" በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፤ እኛ ግን እንደ ተመታ በእግዚአብሔርም እንደ ተቀሠፈ እንደ ተቸገረም ቈጠርነው።እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ።ተጨነቀ ተሣቀየም አፉንም አልከፈተም፤ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፥ በሸላቶቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። " ኢሳ 53 ሙሉውን ያንብቡ! ይህን የታመነ ጌታ እንደ ተሰቀለ ሆኖ በፊታችን ተስሏልና ይታዬን፦ ብናየው አንለያይም፥ ብናየው አንከፋም፥ ብናየው አንሸነፍም፥ ብናየው ለእውነት እንታዘዛለን፡፡ ኢትዮጵያ የተሰቀለውን ስታይ ታርፋለቺ፣የችግሮች ሁሉ መንስኤ እርሱን አለማየት ነው፡፡አዚምን ቆርጦ እንድናየው ያግዘን።
 
  ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

No comments:

Post a Comment