❖ኒቆዲሞስ፦
"ዳግም መወለድ"
የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት ኒቆዲሞስ ነው፡፡ ባለ ታሪኩ ኒቆዲሞስ የጌታ የማታ ተማሪ፥ የአይሁድ መምህር እና የሸንጓቸው አባል ነው፡፡ዮሐ 3:1-14 ተመልከቱ። ክርስቶስ በስውርም በግልጥም መማር ለሚፈልጉ አስተምሯል፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ ሊቅ ስለነበረ ከወገኖቹ ተሰውሮ በማታ ነበረ የተማረው፡፡ የማታ አእምሮ ሥራ የጨረሰ የተረጋጋ ነው፥ ለትምህርት እና ለጸሎት መልካም ጊዜ ነው፡፡ የቤተክርስቲያን አብዛኛው የቃልና የዜማ ትምህርት በማታ የሚሰጥ ነው፡፡ የኒቆዲሞስ ሌሊት የተመስጦ፥ ቁጭ ብሎ መማሪያ፥ የሕይወትን መምህር ክርስቶስን መስሚያ ነበረ ፤ የእኛስ ሌሊት ምን እየሠራንበት ያልፋል ? በተመስጦ፣ በዝማሬ፣ በጸሎት፣ ከእግዚአብሔር ጋር ነው የምናሳልፈው ?
ኒቆዲሞስ መምህርም ሆኖ ይማራል፡ መምህር መማር አለበት፡ መማር ያቆመ መምህር ማስተማር ማቆሙ አይቀርም፥ እውቀት መጨመር ያስፈልጋል! እኛ አንድ ዘመን የተማርነውን ነው ስንናገር የምንኖረው ቁጭ ብሎ መማር ውርደት ይመስለናል፡፡ መማር አያሳፍርም፤ የሚያፍር ካለ ተሰውሮም ቢሆን ይማር፡፡ የተማርነውን በጥናት በምንባብ አናሰፋም። ኒቆድሞስ የእግዚአብሔርን ቃል ለመማር ጊዜ የለንም ለምንል ሰዎች አስተማሪ ነው። ጌታ ለኒቆዲሞስ የዳግም ልደት ትምህርት ነው ያስተማረው፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ለመሆን ዳግም መወለድ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ልደት ረቂቅ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የምንዛመድበት መንፈሳዊ ልደት ነው፡፡ ዳግም መወለድ ወደ እናት ሆድ ተመልሶ መግባት አይደለም፡፡ ዳግም ልደት ላመነ ሰው በመንፈስ ቅዱስ አሠራር የሚከናወን ሰማያዊ ልደት ነው፡፡
ዳግም ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፡፡ስለተወለድን የመለኮት ክብር ተካፋዮች ሆነናል፡፡ ስለተወለድን እግዚአብሔርን አባት ስንለው ልጅነት ይሰማናል። ስለተወለድን የልጅነት ስልጣን አለን።
ኒቆዲሞስ በክርስቶስ ላይ ከንቱ ክስ ሲነሳ ወገኖቹን ተከራክሯል፥ ሁሉ በሸሸበት ሰዓት የጌታን ቅዱስ ሥጋ በክብር የቀበረ ወዳጅ ነው! በስውር ቢማርም በሕይወት ተገልጧል፡፡ የቁርጥ ቀን ወዳጅ ነው፡፡አንድ ቀን ለእግዚአብሔር እንኳን መኖር መታደል ነው! ከመስቀል ልናወርደው መቼ ነው የምንመጣው ? መቼ ነው ለክብሩ ቀንተን ተገልጠን የምንናገርለት ? መቼ ነው ለእርሱ መቆጠርን የማናፍርበት?
ከመንፈስ እንደ ተወለደ መንፈሳዊ ሰው ኖረን መንፈሳዊውን ዓለም በክብር ለመውረስ ያብቃን!!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
===●===●===●===
No comments:
Post a Comment