Friday, April 5, 2019

❖የመከናወን ምንጭ፦

የመከናወን ምንጭ

ብዙዎቻችን ነገር እንዲከናወንልን፤ ኑሮ እንዲቀናልን እንፈልጋለን፡፡ ዛሬ የክንውንን ምንጭ እንመለከታለን፡፡ ዳዊት “ምስጉን ነው በክፉዎች ምክር ያልሄደ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ፥ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ። ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ (ቃል) ደስ ይለዋል፥ ሕጉንም (ቃሉንም) በቀንና በሌሊት ያስባል። እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።” አለ፡፡ መዝ 1፡1-3፡፡

እንዲከናወንልን ምርጫችንን (ዝንባሌያችንን) እንቀይር፡፡ በክፉዎች ምክር አንሂድ፤ በኃጢአተኞችም መንገድ አንቁም፤ በዋዘኞችም ወንበር አንቀመጥ፡፡ ሥራ ስንሰራ በጽድቅ እንስራ፡፡ ክፉዎች፣ ኃጢአተኞች እና ዋዘኞች የተባሉት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የማይሰሩ ናቸው፡፡ ምክር ወደ መንገድ ይመራል፤ መንገድ ወደ ወንበር ያደርሳል፤ ወንበር ደግሞ መድረሻን (ስኬትን) ያሳያል፡፡ የጽድቅም የአመጻም መንገድ ስኬት ይደርሳል፡፡ስለዚህ ዋናው ወደ ስኬት መድረስ ሳይሆን ወደ ስኬት ለመሄድ የመረጥነው መንገድ ነው፡፡ ብር ማግኘት ሳይሆን ያገኘንበት መንገድ መታየት አለበት፡፡ እንዲከናወንልን በእግዚአብሔር ሕግ (ቃል) እንጠቅለል፡- ደስታችን በሕጉ (በቃሉ) ይሁን፤ ቀንና ሌሊታችን ሕጉን (ቃሉን) በማሰብ፤ ለቃሉ በመታዘዝ መኖር ይሁን፡፡ ከዚያ ውጤቱ፡- በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ እንሆናለን፤ ወቅት ሳንጠብቅ እናፈራለን፡፡ የምንሰራው ሁሉ ይከናወንልናል፡፡

ወስብሀት ለእግዚአብሔር!!!

No comments:

Post a Comment